Translate

Wednesday, October 31, 2012

በኢህአዴግ ውስጥ በተፈጠረው አለመግባባት የተነሳ አቶ ሀይለማርያም ደሳለኝ ካቢኔያቸውን ሊመሰርቱ አልቻሉም


ኢሳት ዜና:-አንድ ስማቸው እንዳይጠቀስ የፈለጉ የኢህአዴግ ባለስልጣን ለኢሳት እንደተናገሩት  ኢህአዴግ የድርጅቱን አባላት የአመለካከት መዛባት ለማጥራት በሚል ከክልል ጀምሮ ግምገማ የጀመረ ሲሆን፣ ግምገማውን ወደ ወረዳ ለማድረስ ማቀዱም ታውቋል።

በአሁኑ ጊዜ የአባላቱ አመለካከት እየተጣራ ፣ አዲሱን የጠቅላይ እና ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሮች ሹመት አይቀበሉም የተባሉትን ለማግለል እንቅስቃሴ እየተደረገ ነው።

በድርጅቶች መካከል በተነሳው አለመግባባትም አቶ ሀይለማርያም ደሳለኝ እስካሁን ድረስ ካቢኔያቸውን ሊሰይሙ አልቻሉም። በተለይም የኦሮሞ ህዝብ ዴሞክራሲያዊ ድርጅትን የሚያረካ ስልጣን መጥፋቱ ፣ አቶ ሀይለማርያም ስልጣናቸውን ተጠቅመው ካቢኔያቸውን እንዳይሾሙ እንዳደረጋቸው ባለስልጣኑ ጠቁመዋል።


ይህ በእንዲህ እንዳለ አዲሱ ጠቅላይ ሚኒስትር   ባለፈው እሁድ  ከነ ቤተሰቦቻቸው ወደ ቤተ-መንግስት ገብተዋል።

እንደ ቪ.ኦ.ኤ ዘገባ፤ ጠቅላይ ሚኒስትር ሀይለማርያምና ቀዳማዊ እመቤት ሮማን ተስፋዬ ወደ ቤተ-መንግስት ሲገቡ አቀባበል ተደርጎላቸዋል።



ይሁንና አቶ ሀይለማርያም እስካሁን አቶ መለስ ዜናዊ ይጠቀሙበት የነበረውን ቢሮ መጠቀም አልጀመሩም።
ምንጮች እንዳሉት አዲሱ ጠቅላይ ሚኒስትር ሥራቸውን እያካሄዱ ያሉት፤ በጠቅላይ ሚኒስትሩ ጽህፈት ቤት ቅጥር ግቢ ውስጥ በተዘጋጀላቸው ጊዜያዊ ቢሮ ሆነው ነው።
ጠቅላይ ሚኒስትር  ሀይለማርያም  ደሳለኝ  ላለፉት አምስት ሣምንታት  ብስራተ-ገብርኤል ከሚገኘው  መኖሪያ ቤታቸው ወደ አራት ኪሎ  እየተመላለሱ ለመሥራት መገደዳቸው፤የብዙዎችን ትኩረት ስቦ መቆየቱ ይታወሳል።
ለዚህም ምክንያቱ የቀድሞዋ ቀዳሚት እመቤት አዜብ መስፍን ቤተመንግሥቱን ለቅቀው  ለመውጣት ፈቃደኛ አለመሆን እንደነበረ፤ በተደጋጋሚ መዘገባችን አይዘነጋም።



ዘግይቶም ቢሆን ወይዘሮ አዜብ ቤተ-መንግስቱን በመልቀቃቸው ጠቅላይ ሚኒስትር ሀይለማርያም ደሳለኝና ቀዳማዊ እመቤት ሮማን ተስፋዬ ከሦስት ሴቶች ልጆቻቸው ጋር  በ አቀባበል ታጅበው እሁድ ዕለት ቤተ-መንግስት ገብተዋል።

ከአስር ቀናት በፊት ቤተ-መንግስቱን የለቀቁት ወይዘሮ አዜብ መስፍንም  ወደተዘጋጀላቸው ጊዜያዊ መኖሪያ ቤት መግባታቸው  ተገልጿል።

No comments:

Post a Comment