Translate

Friday, June 30, 2017

ሌ/ጄነራል ጻድቃን፣ ህወሃት፣ ኤርትራ እና ቀይ ባህር (በነጻነት ቡልቶ – ክፍል ሁለት)

በነጻነት ቡልቶ
ክፍል ሁለት
ጀ/ል ጻድቃን ፣ የቀይ ባህር እና ኤርትራTsadkan Gebretensay and Eritrea
ጄነራል ጻድቃን “ኢትዮጵያ የቀይ ባህር ሀይል መሆን አለባት” የሚል አስገራሚ ሃሳብ አንስተዋል። “ኢትዮጵያ የቀይ ባህር ሀይል መሆን አለባት” የሚለው ማደናገሪያ  ሃሳብ ሕወሃቶች ያዳከሙትን የኢትዮጵያን ብሄረተኝነት ስሜት ለማነሳሳት ይጠቅመናል በሚል ስሌት በእነ ጄ/ል ጻድቃን በኩል ነገሮችን ለማጥናት እየሞከሩ ሊሆን እንደሚችል መገመት ይቻላል ። እንደሚታወሰው ቀደም ሲልም በአረብ ጸደይ (ኣረብ ስፕሪግ) ወቅት የአረቡን አለም ያናወጠው የለውጥ ማዕበል ወደ ኢትዮጵያ ይዛመታል የሚል ስጋት ውስጥ ገብቶ የነበረው ሟቹ መለስ ዜናዊ አባይን የመገደብ ፕሮጀክት በማስተዋወቅ የህዝብን ትኩረት ለማስቀየስ- ውሱን በሆነ መልኩም ቢሆን- አስተዋጽዖ አድርጎላቸው ነበር ። አሁን ደግሞ ስርዓቱ ከገባበት አጠቃላይ ቀውስ ለመውጣት ባለተራው “የቀይ ባህር ሀይል” ሆኖ የመውጣት ጥያቄን ማራገቡ ያዋጣል የሚል መደምደሚያ ላይ  ደርሰውም ሊሆን ይችላል። በዚህ “ገዢ ሃሳብ” የ”ህዝብ የአስተሳስብ አንድነት” ይመጣል ከሚል እሳቤ የተሰላ ይመስላል።  በተጻራሪው ከዚህ አመለካከትና ኣቋም የተለዩ ኢትዮጵያዊያን ሁሉ በግብጽ ወይንም ባጠቃላይ በአረብ  “ቅጥረኛነትና ተላላኪነት” ይፈረጃሉ  ማለት ነው፡፡ የደርግ ስርዓት ሻዕቢያን፣ ወያኔንና ሌሎች ተቃዋሚዎችን በዘመኑ ከፈረጀው ጋር ተመሳሳይነት ባለው መልኩ ማለት ነው። ደርግና ሕወሃት በዚህ ተቃዋሚዎችን ከመክሰስና ከመፈረጅ አኳያ ተመሳሳይነት እንዳሏቸው ማጤን ያስፈልጋል።

ብሔራዊ ጥቅም ወይንም “ናሽናል ኢንተረስት”  ከሚለው መርህ በመነሳት የኢትዮጵያ ብሄራዊ ጥቅምና ብሄራዊ ደህንነት ሊጠበቅ የሚችለው” የቀይ ባህር ሃይል መሆን ሲቻል ነው” የሚለውን ኣዲስ መዝሙር በማስተዋወቅ  እንደ ጄ/ል ጻድቃን አገላለጽ “የህዝብን የኣስተሳሰብ አንድነት’’ እናመጣለን ፣ የህዝቡንም ትኩረትና የሚጠይቃቸውን መሰረታዊ የፍትህ፣ የነጻነት፣ የህግ የበላይነት፣ የሃቀኛ ዴሞክራሲያዊ ስርአት ምስረታ፣ እንዲሁም የስርአት ለውጥ ጥያቄዎች ወደ በስተኃላ መቀመጫ ይገባሉ ማለት ነው። በዚህም ስሌት የኢትዮጵያ ህዝብ ስርዓቱ የወለዳቸውን ዘርፈ ብዙ  የፓለቲካ ችግሮቹን ወደ ጎን ትቶ ቀይ ባህር ላይ  እንዲያንጋጥጥ ልናደርገው እንችላለን በማለት ሊሄዱበት እየተዘጋጁ ሊሆን ይችላል። የዚህ አመለካከትና ሂደት ዋነኛ ግብም  በህወሃት ስር የምትገኘው ኢትዮጵያ የአካባባዊ ሃይል የምትሆንበትና ህወሃት ያንሰራፋው የትግራይ የበላይነት  የስልጣን እድሜ የሚቀጥልበትና  የሚረጋገጥበትን ስርዓት ማጠናከር ነው። ይህንኑም እውን ለማድረግ የኢትዮጵያን የፖለቲካ ችግሮች ሊፈቱ የሚችሉ ማናቸውም ተቃዋሚ የፖለቲካ ሀይሎች  የሚመቱበት፣ እንደ ጄኔራሉ አገላለጽም በመንግስት “ቁጥጥር ስር የሚውሉበት”፣ እነዚህን ሀይሎች ይደግፋል በሚል የሚከሰሰው “የኢሳያስ ኣፈወርቂ  የኤርትራ መንግስት” የሚወገድበት ሁኔታ ይመቻቻል ማለት ነው።
ለመሆኑ የሕወሃት አገዛዝ የቀይ ባህርንና የባህር በርን ጉዳይ ለማሳካት ጀ/ል ጻድቃን እንደሚለው በወታደራዊ መንገድ ኤርትራን ለማጥቃትና ያለውን መንግስት ለማስወገድ ወታደራዊ ብቃቱና አቅሙ አለውን?
በዚህ ጥያቄ መነሻነት የተወሰኑ ነጥቦችን አፍታተን ብናየው መልካም ይመስለኛል።
ህወሃት ስትራቴጂክ አመራር ሊሰጥ የሚችል ወታደራዊ አዛዦች የለውም። የሕወሃት ጄነራሎች መከላከያውን ባለፉት ሀያ አመታት 95 በመቶ፣  ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ደግሞ ከ70 በመቶ በላይ በስትራቴጂክና ከዚያም በታች ባሉ እርከኖች በአመራርነትና በአዛዥነት ለ26 አመታት ተቆጣጥረውታል። የመከላከያ ሰራዊት አዛዦች አሁን ያሉበትን የስልጣን ቦታ የያዙት በብቃት፣ በእውቀትና በክህሎት መስፈርቶች ሳይሆን በፓለቲካና በመጡበት የትግሬ ብሄር ተወላጅነታቸው ወይንም የሕወሃት ታጋዮች በመሆናቸው ብቻ መሆኑ የሚያከራክር አይደለም። መሰረታዊ በሚባል ደረጃ አለም አቀፍ ደረጃዉን የጠበቀ የመደበኛ ሰራዊት ማለትም የምድር፣ የአየርና ልዩ ልዩ ሃይሎችን አስተባብረውና አቀናጀተው ለመምራት የሚያስችል እውቀትም፣ ትምህርትም ሆነ ክህሎት እንደሌላቸው በድፍረት መናገር ይቻላል። ይህንንም ሃቅ ጄነራሉ ጠንቅቀው ያውቁታል።
የወያኔ ሰራዊት ሞራል በጣም የዘቀጠ መሆኑን ጄ/ል ጻድቃን የሚጠፋቸው አይመስለኝም። ሰራዊቱ በብሄር እንዲያስብና እንዲከፋፈል መደረጉ ከፍተኛ ለሆነ የስነ ልቦና ክስረት ዳርጎታል። የሰራዊቱ ጓዳዊ ግንኙነት በጣም የላላና በጎሪጥ የሚተያይ ሆኗል። ከላይ እሰከ ታች ማለትም ከስትራቴጂክ እዝ እስከ ታክቲካል የሚንቀሳቀሰው በወታደራዊ ዕውቀት፣ ብቃትና ክህሎት ሳይሆን በፓለቲካዊ ታማኘነትና በህወሃት ትግሬነት የተደራጀ እዝና ቁጥጥር (Command and control) ባለበት ሁኔታ መሆኑም ያደባባይ ሚስጥር ነው። የመከላከያ ተቋሙ የሰራዊቱ አዛዦች በተለይም የህወሃት ምርጦች  የሰራዊቱን የስንቅ አቅርቦት በማጭበርበርና በኮንትሮባንድ ንግድ የሚከብሩበት (በተለይም በሶማሊያና በኦጋዴን)፣  ለሰራዊቱ ከውጭ የሚመጡ ልዩ ልዩ መሳሪያዎችን፣ አውሮፕላኖችንና  መለዋወጫዎችን በመሸጥ በኢትዮጵያ ህዝብ ኪሳራ እየደለቡ ያሉበትና በሙስና የተጨማለቁ አመራሮች የተሰገሰጉበት ሆኗል!  ሰራዊቱና የኢትዮጵያ ህዝብ ይህን ዕውነት በሚገባ እያወቀው፣ ሰራዊቱን ተማምኖ  በፈረንጆቹ በ2000 ዓ/ም እንዳደረገው የሕወሃትን የበላይነት በኢትዮጵያ ህዝብና በአካባቢው ሀገሮች ላይ ለማስቀጠል ኤርትራን በወታደራዊ ጡንቻ አዳክማለው ወይንም “የኢሳያስ እፈወርቂን መንግስት” አስወግዳለሁ ብሎ አጉል ቢጋበዝ  ለዳግም ለቅሶና ውርደት ሊዳርገው የሚችል አካሄድ መሆኑን ጄ/ል ጻድቃን ሊጠፋቸው  የማይችል ሃቅ ነው።
በአሁን ሰአት ጦርነት ቢነሳ በኤርትራ በረሃና ተራራማ ቦታዎች ውስጥ ዘልቆ ማዋጋት የሚችል ከፍተኛ የጦር አዛዦች የሉም። የሰራዊቱ የሰው ሃይል በጣም አነስተኛ ነው። በአሁኑ ሰአት የመደበኛ ተዋጊው ሃይል በጣም በዛ  ቢባል ከ120,000 አይበልጥም። በህወሃት ስር የሚገኘው ሰራዊት 18 ክፍለ ጦር ሲሆን ከዚህ ውስጥ 6ቱ ሜካናይዝድ ክ/ጦር ነው። የተቀረው 12ቱ እግረኛ ክ/ጦር ነው። በተለያዩ ምክንያቶች ሰራዊቱ ከመከላከያ እየከዳ መጥፋት የእለት ተእለት ክስተት ሆኖ በአዛዦች ደረጃም ጭምር የሚጠፉ የመከላከያ ሰራዊት አባላት እየተበራከቱ መጥተዋል። በአሁኑ ሰአት በአንድ እግረኛ ክ/ጦር ውስጥ ቢበዛ 6,000 ሰራዊት ነው ያለው። በሜካናይዝድ ክ/ጦር ደግሞ ቢበዛ ከ 2500 አይበልጥም። በዚህም መሰረት በሕወሃት ስር የሚገኘው ሰራዊት ሌላን አገር መውረር ቀርቶ ከሌላ አገር ጥቃት ቢሰነዘርበት እንኳ ያንን መመከት የሚችል የሰራዊት ብዛትም ሆነ አቅም በጭራሽ የለውም።
በኢትዮጵያ ውስጥ ያለው የህዝብ ተቃውሞ በተለይ በአማራና በኦሮሚያ አካባቢዎች ያለው ተቃውሞ በተፋፋመበት ሁኔታ ህወሃት ወደ  ኤርትራ ጦርነት ቢጀምር  መሃል አገሩ ክፍት ስለሚሆን ህወሃትን ለማስወገድ ወደ ኤርትራ ጦርነት መክፈቱ ለተቃዋሚዎች ትልቅ የምስራች ተደርጎ እንደሚወሰድ ህወሃት ራሱ ያውቀዋልና ድንበር አካባቢ ለማስቀየሻ  ካልሆነ  በስተቀር ህወሃት በኤርትራ  ላይ ሙሉ ጦርነት አይከፍትም። ነገር ግን በተስፋ መቁረጥ ስሜት ተቅበዝብዞ ሙሉ ጦርነት ከከፈተም የራሱን የመቃብር ጉድጓድ መቆፈር ይሆናል።
በኢትዮ- ኤርትራ ጦርነት (በፈረንጆቹ 1998-2000)  ወቅት ከመረጃ አንጻር ትልቁን ሚና ሲወጡ የነበሩት የቀድሞ የደርግ አገዛዝ ስር ያገለገሉ የሰራዊት አባላት ነበሩ። አብዛኛው የቀድሞ ሰራዊት በኤርትራ ውስጥ ለረጅም ጊዜ በግዳጅ የቆየ በመሆኑ የኤርትራን እያንዳንዱን አካባቢና ክፍል እንደ እጅ መዳፉ ያውቁ ነበር። በዚህም ሁኔታ በኢትዮ- ኤርትራ ጦርነት ወቅት እነዚህን የቀድሞ ሰራዊት አባላትን በመጠቀም ህወሃት የነበረበትን የመረጃ ክፍተት ጭምር ለመሙላት ጥሯል። ይህም በጦርነቱ ሂደት ተጠቅሞበታል።
አሁን ባለበት ሁኔታ ግን ህወሃት ኤርትራን በሙሉ  ልውረር ቢል የትኛው የህወሃት የጦር አዛዥ ነው የኤርትራን ተራራማ የውጊያ ቀጠናዎች በአግባቡ ሊያውቅ የሚችለው? እንደሚታወቀው አብዛኛዎቹ የህወሃት የጦር አዛዦች መሰረታዊ የሚባለውን የካርታ ንባብ እንኳን የማያውቁ ናቸው። ከመረጃ ጋር ተያይዞ  ህወሃት በኤርትራ ውስጥ ስላለው አጠቃላይ ሂደት አንድን ጦርነት ለማከናወን የሚያስችል በቂ መረጃ እንደሌለው በመከላከያ የወታደራዊ መረጃ ውስጥ የሚሰሩ አካላት ሁሉ የሚያውቁት እውነታ ነው።
ህወሃት ኤርትራ ላይ ሙሉ ወረራ እፈጽማለው ቢል እንኳን እኔ ባለኝ ግርድፍ ግምት በትንሹ 200,000 መስዋዕት የሚሆን ሰራዊት ያስፈልገዋል ። ሙሉ ወራራ ከታቀድም  ቢያንስ ቢያንስ 3 እጥፍ በትንሹ  ከ 600,000 በላይ ሰራዊት ማሰለፍ ሊኖርበት  ከዚህ ውስጥም ቢያንስ 200,000 ሰራዊት ጭዳ፣ ፈንጂ ረጋጭ፡ የጥይት ማገዶ በማድረግ ነው አስመራ ሊገባ  የሚችለው። እኔ እስከሚገባኝ ዋናው የጦርነት ቀጠና ደግሞ አስመራ አይደለም። ደርግ 17 አመት ለፍቶ ናቅፋን መያዝ ያልቻለውን ህወሃት ከአስመራ፣ ከረን እስከ ናቅፋ የተዘረጋውን ሰፊ  የጦርነት ቀጠና ለመወጣት ምን ያህል ሰራዊት ያስፈልገዋል ስንል ጉዳዩ ምን ያህል ውስብስ እንደሆነ እንረዳዋለን። በተለያየ ምክንያት ይህን ያህል ቁጥር ሰራዊት ማሰባሰብ ቢቻል እንኳን ከስትራቴጂክ ጉዳዮች እስከ ታክቲካል ደረጃ ያሉ የውጊያ ሂደቶችን መምራት የሚችሉ የጦር አዛዦች የሉም። ይሄ ማለት ጄኔራል ጻድቃን ያሰቡት ጦርነቱ ሳይጀመር በሽንፈት መጠናቀቁን የሚያሳይ ይሆናል።
ሌላ ትልቅ ነጥብ እናንሳ። በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ኢትዮጲያዊያን በኢትዮ-ኤርትራ (ከፈረንጆቹ 1998-2000) እነ ጀ/ል ጻድቃን በመሩት ጦርነት ህይወታቸውን ገብረዋል። እኔ ባለኝ መረጃ በጦርነቱ 92,450 በላይ የኢትዮጵያ ውድ ልጆች ህይወታቸውን መሰዋት አድርገዋል። ለከባድ እና ቀላል የአካል መቁሰል የተዳረጉ በብዙ ሺ የሚቆጠሩ ኢትዮጵያውያን ቤት ይቁጠራቸው። እንግዲ ይህ ሁሉ ጉዳት የደረሰው ድንበር አካባቢ በተደረገ የአውደ ውጊያ ቀጠና ነው። ወደ ኤርትራ ውስጥ እየዘለቁ የሚኬድ ቢሆን ኖሮ የጉዳቱ መጠን ምን ያህል ሊሆን እንደሚችል መገመት አያዳግትም። በኢትዮጵያውያን ላይ እንደደረሰው ጉዳት ሁሉ ያ ጦርነት በብዙ ሺ የሚቆጠሩ የኤርትራ ወጣቶችን ህይወትም የቀጠፈ ጦርነት ነበር። በኤርትራ ምድር ልጁን ያላጣ አካባቢ መኖሩ ያጠራጥራል። በኤርትራ ምድር ለሚሰማው ሀዘን፣ ቁጭትና፣ ከፍተኛ ምሬት ለጦርነቱና ለተከፈለው የህይወትና የንብረት ውድመት ኪሳራ ተጠያቂ የሚያደርጉት ህወሃትን ነው። እንዲያውም ወረድ ሲል በኣንዳንድ አካባቢዎች እነዚህ  “ትግሬዎች” በደርግ ዘመንም ሰላዮች ሆነው ልጆቻችንን  ሲያሳስሩ፣ ሲያስገርፉና  ሲያስገድሉ ነበር የሚል ሮሮ የሚሰማ ሲሆን አሁንም የልጆቻቸውን ህይወት የቀጠፈውን የኢትዮ ኤርትራ ጦርነት  በተመሳሳይ መንገድ የሚተረጉሙ በሚልዮኖች እንዳሉ መታወቅ ይኖርበታል። ጦርነቱን ተከትሎ ለትግራይ ማህበረሰብ ያለው ጥላቻ እንዲ በቀላሉ የሚታይ አይመስለኝም። በመሆኑም የህወሃትን ወረራ ደግፎ በእልልታ የሚቀበል ኤርትራዊ ለማገኘት ለህወሃት ትልቅ አቀበት እንደሚሆንባቸው የሚያጠራጥር አይደለም፡፡ በሽምቅና በደፈጣ ውጊያም ይሁን በመደበኛ ጦርነት  የህወሃትን ወረራ ሊመክት የሚችል በርካታ ቁጥር ያለው ኤርትራዊ እንደሚሳተፍና እስከመጨረሻው የደም ጠብታው እንደሚፋለማቸው  ጄ/ል ጻድቃንም ሆነ ሌሎቹ የህወሃት የጦር አበጋዞች በትዕግስት ሊያጤኑት የሚገባ እውነታ ነው።
“የአይናቸውን ቀለም ካላማረን እናባርራለን” በሚል ትብኢት  መለስ ዜናዊ ለዘመናት ከኖሩበት አካባቢዎች በግፍ እንዲባረሩ የተደረጉት ኤርትራዊያን ከዚያም በኋላ በህወሃት ትግራዮች ሀብት ንብረታቸውን ተቀራምተውታል። ከኢትዮጵያ ወደ ኤርትራና ልዩ ልዩ ሀገሮች እንዲሰደዱ የተገደዱት እነዚህ  በመቶ ሺ የሚቆጠሩ ኤርትራውያን የህወሃትን የኤርትራ ወረራ  አቅፈውና  እልል ብለው የሚቀበሉ ናቸው ብሎ ማሰብ “የወጋ ቢረሳ ፣ የተወጋ አይረሳም” የሚለውን ብሂል መርሳት እንደሚሆን በወቅቱ የጦር ሃይሎች ኤታማዦር ሹም የነበሩት ሌ/ጄነራል ጻድቃን የሚጠፋቸው አይመስለኝም።
ባለፈው ጦርነት የሃይል ሚዛኑ በ11ኛው ሰኣት ወደ ኢትዮጵያ እንዲያጋድል ያደረጉት ዋና ዋና ምክንያቶችን በማንሳት ጄነራሉን ማስታወስ ጠቃሚ ይመስለኛል ።  1ኛ) ሲንኳስሰ የነበረውን የኢትዮጵያን ብሄረተኝነት ስሜት ለህዝቡ “ሀገራችን ተጠቃች ተወረረች” በሚል የህወሃት አገዛዝ  ራሱን በኢትዮጵያዊነት ካባና ሰንደቅ አላማ ስር በመወሸቁና  ቀደም ሲል በህወሃት ስርአት ላይ ከፍተኛ ጥላቻ የነበረውን በውስጥም ሆነ በውጭ ሀገራት የነበረውን ኢትዮጵያዊ በተወሰነም ደረጃ ቢሆን በማጭበርበሩና ከጎኑ በማሰለፉ የተገኘ ነበር። 2ኛ) ለውርደትና ለችግር የዳረጋቸውን የቀድሞ ከፍተኛ የጦር መኮንኖች፣ የአየር ሃይል አብራሪዎች፣ የመስመር መኮንኖችና ልዩ ልዩ የጦር ስልትና ቴክኒክ ባለሙያዎች እየለመነ በገፍ ስላስገባቸው እንጂ እንደ ጅምሩ በሕወሃት ኮነሬሎችና ጄኔራሎች የተመራው ጦር በበርካታ ዙር ውጊያዎች ላይ ከፍተኛ የሕይወትና የሞራል ውድቀት ደርሶበት እንደነበርና በወቅቱ የጦር ኃይሎች ኤታ ማጆር ሹም የነበሩትን ሌ/ጄነራል ጻድቃንን ለለቅሶ እንደዳረጋቸውም ጄኔራሉ የሚያስታውሱት ይመስለኛል። በወቅቱ አብረዋቸው የነበሩና በህወሃት ስርአት ተማረው ስርአቱን የከዱ  ከፍተኛ የጦር መኮንኖች ይህንን ሚስጥር አጋልጠዋል።
ሌላም ማሳያ  እንመልከት።  በ1969 የሶማሊያ ጦርነት ወቅት የኢትዮጵያ አየር ሃይል 25 የሶማሊያ ሚግ 21 ጀቶችን በአየር ላይ ዶግ አመድ አድርጓል። በተቃራኒው ከመሬት በተተኮሰ ተወንጭፊ ሚሳኤል ኢትዮጵያ የወደሙባት ጄቶች ሁለት ብቻ ነበሩ ። ከ 1998 – 2000 በተደረገ የ“ኢትዮ ኤርትራ” ጦርነት ወቅት በህወሃት ሙሉ ቁጥጥር ስር የሚገኘው አየር ሃይል በጎረቤት ሀገሮች በስደት ይኖሩ የነበሩና ሀገር ውስጥ ለእስር፣ እንግልትና ውርደት ህወሃት ዳርጓቸው የነበሩ የቀድሞ ስርዓት አብራሪዎችንና ቴክኒሻኖችን በልመና አስገብቶ ነው በተወሰ ደረጃም ቢሆን  በአየር ኃይሉ ላይ ነፍስ የዘራበት።  እንዲያም ሆኖ ጦርነቱና ከጦርነቱ ጋር በተያያዘ 25 አይሮፕላኖችና ሄሌኮፕተሮች ወድመዋል። በርካታ ድንቅዬ አብራሪዎችም ተሰውተዋል። በህወሃት ሙሉ ቁጥጥር ስር የነበረው የመከላከያ  ሰራዊት በታጠቀው  የአየር መቃወሚያ ሚሳኤል የተመቱ የወገን አይሮፕላኖችም ነበሩ። ለምሳሌ መ/አ እንደገና ታደሰ  የሚያበረው ጄት ሁለት ጊዜ በወገን የአየር መቃወሚያ ሚሳኤል ተመትቶ ነበር። መጀመሪያ የሚያበረው ሚግ 21 ጄት ቢመታም በፓራሹት ወርዶ ሊተርፍ ቢችልም ሁለተኛ ጊዜ የሚያበረው L 39 የተባለ  ተመትቶ መስዋዕት ሆኗል። በኤርትራ  በኩል 2 ሚግ 29 ጄቶች የተመቱ ሲሆን እነዚህን ጄቶች የጣሉትም የኢትዮጵያ አብራሪዎች ሳይሆኑ የራሺያና የዩክሬን ቅጥረኛ ነበሩ ኦሌግ እና አሌክስ የተባሉ አብራሪዎች ናቸው።
አሁን የማዕከላዊ አየር ምድብ አዛዥ የሆነው ኮ/ል ሰለሞን ገ/ስላሴ አንድ ጆሮው የማይሰማ ከመሆኑም በላይ ከዚህ በፊት በድሬዳዋ ኤል 100 ( L – 100 ) የተባለ ግዙፍ የእቃ ማመላለሻ አይሮፕላን ከስክሷል። በአንድ ስልጠና  ላይ የእስራኤል አብራሪዎች በሚያሰለጥኑበት ጊዜ አይተውት አንተ እንኳን ማብረር አይሮፕላን ውስጥም መግባት የለብህም ብለውት እንደነበር ይታወሳል። እንደዚህ አይነት አብራሪዎችን ይዞ ጦርነትን ማሰብ እብደት ካልሆነ በስተቀር ሌላ ምንም አይባልም። አሁን ያሉት የህወሃት አብራሪዎች የአየር ላይ ጦርነት የማድረግ ምንም ልምድና ብቃት የሌላቸው ስለመሆናቸው በቂ መረጃዎች አሉ ። በአሁኑ ሰአት የአየር ሃይል ዋና አዛዥ የሆኑት ሌ/ጄነራል አደም መሃመድ እና ም/ል አዛዥና የኦፕሬሽን ሃላፊ የሆኑት ብ/ጄነራል ማዕሾ ሃጎስን ጨምሮ በኢትዮ- ኤርትራ ጦርነት ላይ ምን አይነት ተሳትፎ ያልነበራቸው ናቸው። በተቃራኒው ስልጣን እና ማዕረግ በላይ በላዩ  የሚደርቡት ግን እነርሱ ናቸው። ምክንያቱም አየር ኃይሉም ሆነ ጠቅላላ ስርዓቱ በብቃትና በእውቀት ላይ የተገነባ ሳይሆን በዘርና በፓለቲካ ታማኝነት ላይ የተመሰረተ በመሆኑ ነው።  በኢትዮ -ኤርትራ ጦርነት ላይም በዋናነት የተሳተፉት የቀድሞ አየር ሃይል አባላት ናቸው። እነዚህ አብራሪዎች ከጦርነቱ በኃላ በተለያየ  መንገድ ከአየር ሃይሉ እንዲባረሩ በመደረጉ በአሁን ሰአት ጦርነት ቢነሳ ብቃት ባለው ሁኔታ አየር ሃይሉ ምንም አይነት ምላሽ የሚሰጥበት ሁኔታ ላይ አይደለም ያለው። በአሁን ሰአት ሃገሪቷ እየተጠበቀች ያለችው በራሺያና እና በዩክሬን ቅጥረኞች ነው። እነዚህም ሱ 27 ( SU 27 ) የሚያበሩ ሲሆኑ ከኢትዮጵያ አየር ክልል ወጥተው ጥቃት መሰንዘር አይችሉም። የተዋዋሉት ውል በሃገር ውስጥ ብቻ ለመብረር ነው። ከኢትዮጵያ አየር ክልል ወጥተው ለመብረርና ጥቃት ለመሰንዘር የመጡበት ሃገር ህግ አይፈቅድላቸውም።
ኢትዮጵያ በአሁን ሰአት ካሏት MI 35 ሂሊኮፕተር ውስጥ ግዳጅ መውጣትና መስራት የሚችሉት 5 ብቻ ናቸው። እንዲሁም MIG 23 ቦምብ ጣይ ጄቶቹም ያረጁና በአግባቡ ጥቅም ላይ የሚውሉ አይደሉም። ለደህንነትም ( Safety )  አስተማማኝ አይደሉም። በብልሽት ምክንያት በተደጋጋሚ ሲከሰከሱ ተስተውለዋል። እንዲሁም ከ17 ሱ 27 ወሰን ተከላካይ ጄቶች ( SU 27 Intercepters)  ውስጥ በሚገባ አገልግሎት መስጠት የሚችሉት ሰባቱ ብቻ ናቸው። ካሉት 3 ሱ 25 ( SU 25 ) ጄቶች ውስጥ በሚገባ መስራት የሚችለው አንዱ ብቻ ሲሆን ይህንንም አይሮፕላን በሚገባ የሚያበረው የለም። አየር ሃይሉ በመለዋወጫ ድርቅ ከተመታ ቆይቷል። በቅርብ ጊዜ የሱ 27 ጀት መለዋወጫ ለመግዛት ተኪዶ ሃገሪቷ የሌላት የሚግ 29 ጀት መለዋወጫ ተገዝቶ መምጣቱና የሃገር ሃብት መባከኑ የአየር ሃይል አባላት በቁጭት የሚያነሱት ጉዳይ ነው። ላሉ አይሮፕላኖች መለዋወጫ እንኳን በአግባቡ መግዛት የማይችል ተቋም በምን ሁኔታ ውጊያዎችን አቅዶና በተግባር አውሎ ጦርነትን ማሸነፍ እንደሚችል ጄነራል ጻድቃን የሚጠፋቸው አይመስለኝም። ጄነራል ጻድቃን ስለአየር ሃይል ለማወቅ ከፈለጉ ወደዚያ ጎራ ብለው ቢያዩት ሃገሪቷ አየር ሃይል የሚባል እንደሌላት በቀላሉ መረዳት ይችላሉ ብዬ አምናለሁ።
አየር ሃይሉን በአመራርነት እየመሩ ያሉ ከፍተኛ አዛዦች የአየር ሃይል የውጊያ ዘመቻዎችን በአግባቡ መምራት የሚችሉ አይደሉም። የኢትዮ- ኤርትራ ጦርነትንም በዋናነት ሲያስተባብሩና በሙያዊ ብቃታቸው ውጤት ያስመዘግቡ የነበሩት  አለም የመሰከረላቸውና ያደነቃቸው የቀድሞ አየር ሃይል አባላት ነበሩ። እነዚህ ከፍተኛ ብቃት ያላቸው የቀድሞ አየር ሃይል አባላት በአሁኑ ሰአት በአየር ሃይል ውስጥ የሉም።
ለመሆኑ እንደዛም ሆኖ ለኢትዮ- ኤርትራ ጦርነት በድንበር አካባቢ ብቻ በተደረጉ ውጊያዎች ከዘጠና ሁለት ሺ አራት መቶ ኣምሳ (92,450) በላይ ኢትዮጵያውያን ህይወታቸውን ገብረው ምን ተገኘ? ጦርነቱ ምን ፈየደ? መልሱ ምንም ነው!  የህወሃትን እድሜ ከማስቀጠልና የኢትዮጵያዊያንን ስቃይ ከማራዘም በስተቀር ለኢትዮጵያና ለሕዝቧ አንዳች የፈየደው ነገር የለም። ጸረ ኢትዮጲያዊው የህወሃት ቡድን በተወሰነ ደረጃም ቢሆን ሲያብጠለጥለውና ሲዘልፈው በነበረው ኢትዮጵያዊነት ካባና ሰንደቅ አላማ ስር መደበቁና ህዝቡንም በዚህ ብልጣ ብልጥ ስልቱ ማጭበርበሩ ረድቶታል።  በእነ ጄ/ል ጻድቃን አመራር በተካሄደው በዚህ ጦርነት ውስጥ በአብዛኛው ምናልባትም አለማጋነን  95 በመቶ  የሚሆነውና የተቀበረ ፈንጂ እየረገጠ የፈንጂ አምካኝ እንዲሆን የተፈረደበት የሌላ ብሄር ተወላጅ ሆኖ ሳለ ጦርነቱን ይመሩና ትዕዛዝ ይሰጡ የነበሩት ግን 95 በመቶው ከወታደራዊ ሳይንስ ጋር የማይተዋቁና መደበኛ ጦርነት እንዴት መምራት እንዳለባቸው ምንም እውቀቱ የሌላቸው የሕወሃት ጄኔራሎች ነበሩ ። እሁንም በኤርትራ ላይ የጠነሰሰው ወታደራዊ ጥቃት እነዚሁ በችሎታና በብቃት ሳይሆን በፖለቲካ ታማኝታቸውና በትግሬነታቸው ለ26 አመት የሰራዊቱን ላብና ደም እየጠጡ ራሳቸውን ትላልቅ ባለሀብት ያደረጉ የህወሃት ጄኔራሎች የሚመራ እንደሆነ እሙን ነው። ነገር ግን ተዋጊውና ለመትረየስ አጨዳ የሚጋለጠው ብሎም የፈንጂ አምካኝ ሆኖ አሰቃቂና ከንቱ ሞት እንዲሞት የሚፈረድበት የሌላው ብሄር ተወላጅ  እንደሚሆን የህወሃት የቅርብ ታሪክ ደጋግሞ አሳይቶናል።
በዚሁ ከባድ መስዋዕትነትን ባስከፈለው የሁለት ዓመት ጦርነት ( 1998-2000) ውስጥ በርካታ ዙር አውደ ዉጊያዎች  ከለቅሶና ዋይታ አልፎ የህወሃትን ህልውና ራሱን ከባድ አደጋ ላይ ጥሎት እንደነበርና የስልጣን እድሜውንም የሚፈታተን ደረጃ አድርሶት እንደነበርም ይታወሳል። ይህ ያለፈ ክስተት ለዛሬው እውነት ትልቅ ትምህርት ሰጪ መሆኑን እነ ጄ/ል ጻድቃን በይፋ አይናገሩት እንጂ ከእነሱ የተሰወረ የሚሆን አይደለም። ለመሆኑ የመለስንና የህወሃትን የመጨረሻ ደረጃ መሰሪነትና ውለታ ቢስነት ጄ/ል ጻድቃን ያስታውሱት ይሆን?  ጄ/ል ጻድቃንን ጨምሮ ብዙ የህወሃት ድኩማን የጦር መኮንኖች በተደጋጋሚ በኤርትራ ጦር የደረሰባቸውን አዋራጅ ሽንፈቶች ተከትሎ ለቀጣዩና የመጨረሻ  የመልሶ ማጥቃት  ጦርነት ዝግጅት ወቅት በልመና ያመጧቸውን የቀድሞ ሰራዊት ምርጥ ጄኔራሎች፣ የመስመር መኮንኖችና በብዙ ሺ የሚቆጠሩ የሰራዊት አባላትን መለስ ዜናዊ “እነዚህ አባታቸው የሞተባቸውን ማን ነው ያመጣቸው? ይባረሩ!”’ በማለት ህወሃት ከኤርትራ ጋር ባደረገው የመጨረሻው መልሶ ማጥቃት ጦርነት ላይ  ከተጠቀመባቸው በኋላ  እንደ ቆሻሻ በገፍ እንዲባረሩ መደረጉን በጊዜው የመለስ ዜናዊን “አይናቸውን ማየት ኣልፈልግም” ትእዛዝ አስፈጻሚ የነበረው ኤታማጆር ሹሙ ጄ/ል ጻድቃን ሊዘነጋው አይችልም። ሁሉም ኢትዮጲያዊ በተለይ ለዳግም ውርደት  በህወኣት የተዳረጉትና በጦርነቱ ላይ ትልቅ ሚና የነበራቸው የቀድሞ ሰራዊት አባላት  ቤተሰቦች በቁጭትና በምሬት የሚያስታውሱት  የቅርብ  ታሪክ ነው! ባጭሩ “ የወጋ ቢረሳ የተወጋ አይረሳ” እንደማለት ነው።
ከኢትዮ-ኤርትራ ጦርነት በኃላም ቢሆን  ሌላ የህወሃትን መሰሪነትና በአካባቢው የደቀነውን  የሰላም ጠንቅነት በሚመለከት ህወሃት የሄደበትን ብዙ ርቀት እንመልከት። ከፈረንጆቹ 2006 ጀምሮ በሶማሊያ ደሙን ሲያፈስና የአልሻባብ እሳት ራት እየሆነ ለአመታት የዘለቀውና ህይወቱን በ10,000 ሺዎች በላይ የገበረው የመከላከያ ሰራዊት ከሌሎች የኢትዮጵያ ብሄሮች የመጣ  ሲሆን ኣሁንም በላዩ ላይ በአዣዥነት ተጭነውት እያዘመቱ  በአልሻባብ የሽብር ጥይት ያስቆሉት፣ ሬሳውን ክብር አሳጥተው መሬት ለመሬት ያስጎተቱትና ደመ ከልብ አድርገው ያስቀሩት  እነዚሁ በሶማሊያ ውስጥ በሚካሄድ የኮንትሮባንድ ንግድ የተዘፈቁና  በሙስና የተጨማለቁ  የህወሃት ትግራይ የጦር አበጋዞች መሆናቸው ጸሃይ የሞቀው ሐቅ ነው። በሶማልያ ውስጥ  በህወሃት ኮለኔሎችና ጀነራሎች አዝማችነት  በተሰነዘረው ወረራ የዛሬው በመከላከያ የወታደራዊ መረጃ ዋና መምሪያ ሃላፊ ሜ/ጀነራል  በወቅቱ ኮ/ል ገብሬ ዲላና በኮ/ል ወዲ አባተ (ሁለቱም የሕወሃት ትግሬዎች) ኣዛዥኝነት ስር ይመረሩ የነበሩት 43ኛና 44ኛ  ከፍለ ጦሮች በሶማሊያ ወስጥ በተደረጉ ጦርነቶች  ሙሉ በሙሉ በሚባል መልኩ መደምሰሳቸው ይታወቃል።
ሌላው አሳዛኝ ክስተት በMI 35 ተዋጊ ሄሊኮፕተር በሚወነጨፉ ሮኬቶች የሆነው የመከላከያ ሰራዊት በራሱ አየር ሃይል እየተድበደብ  በብዙ ሺ የሚቆጠር ሰራዊት ማለቁ ነው። ለዚህ ጥፋት ተጠያቂ ከሆኑት ውስጥ አንዱ የአየር ሃይል ም/ል አዛዥና የኦፕሬሽን ሃላፊ የሆነው ብ/ጄነራል ማዕሾ ሃጎስ ነው። ይህ የጦር አዛዥ ህወሃት በመሆኑ የሚነካው የለም። እንደውም ስልጣን በስልጣን ላይ እየጨመረ አየር ሃይልን እንደፈለጉ ከሚዘውሩ ሰዎች አንዱ ሆኗል። ጄነራል ጻድቃን ይህን እውነት አጠገቦ ካሉ የህወሃት ጄነራሎች ጠይቀው ማወቅ እንደሚችሉ በዚህ አጋጣሚ ልጠቁሞት።
በጣም የሚያሳዝነውና ለእነ ጄ/ል ጻድቃን አይነቶቹ እምብዛም የማያስጨንቃቸው ሶማሊያ ውስጥ ህወሃት ባደረገው ጣልቃ ገብነት ህይወታቸውን የገበሩ ከ10,000 በላይ የሌሎች ብሄር ተወላጅ የሆኑ የመከላከያ ሰራዊት አባላት መጨረሻው ምን እንደሆነ ለቤተሰቦቻቸው እንኳን እስካሁን አለመነገሩ ነው። አገዛዙ በሶማሊያ ኣስካሁን ባደረገው ጦርነት ምን ያህል ኢትዮጲያዊያን  እንደተሰው ለፓርላማ ተብዬውም ሆነ ለህዝብ የተገለጸ አለመሆኑን ከጄ/ል ጻድቃን የተሰወረ ነው የሚል ግምት አይኖርም። የህወሃት ስርዓት ለኢትዮጲያውያን ክብር፣ ለሰው ልጆች ህይወት ዋጋ የማይሰጥ መሆኑን ለማሳየት አንድ ሺ ኣንድ መገለጫና ማስረጃዎች ቢኖሩም ይህ የሶማሊያ ዘግናኝ ታሪክ ሌላው ማጠናከሪያ ምሳሌ ሆኖ መቅረብ ይችላል።
ይህ ብቻም አይደለም። ሙሉ በሙሉ በሚባል ደረጃ በህወሃት የጦር መኮንኖች አዝማችነት የተመራው መከላከያ ሰራዊት በፈረንጆች 2006 ወደ ሶማሊያ ሲገባ በየመንደሩ በየመስጊዱ እየገባ ባደረገው ጭፍጨፋ ሶማሌዎች ዘመን ሊሽረው የማይችል ጥላቻን በኢትዮጵያ ላይ እንዲኖራቸው አድርጓል። በአንጻራዊነት ለዘብተኛውን የእስላማዊ ኮርትን ጣልኩ ባለ አክራሪው አልሻባብ በአጭር ጊዜ ውስጥ በምድረ ሶማሊያ ተስፋፍቶ እንዲጠናከር ማድረጉ ህወሃቶች በኢትዮጵያ ላይ የፈጠሩት ትልቅ የደህንነት ስጋትና አደጋ ለመሆኑ የሚያጠራጥር አይደለም። ለዚህም ነው በኢትዮጵያ ውስጥ ብቻ ሳይሆን በሶማሊያና በደቡብ ሱዳን ውስጥ እየሰፋ ለመጣው ትርምስ የህወሃት አገዛዝ ትልቅ አሉታዊ ሚና ተጫውቷል በሚለው ድምዳሜ ብዙዎች የሚስማሙት። ይህም የመነጨው የህወሃት የማንነት መገለጫ ባህሪው መሰሪነት፣ ውንብድናና  ስግብግብነት ከመሆኑ የተነሳ ብቻ ሳይሆን ከአፍንጫው ስር በላይ የላውን ማየት የማይችል ከታክቲካዊ ስሌት ብቻ የሚነሳ በመሆኑ ነው።
በአንጻሩ ህወሃቶች ከእነሱ ሌላ ምንም ጥሩ ጎኖች እንዲሌላቸው በተደጋጋሚ የሚያብጠለጥሏቸው የቀድሞው የአጼ ሃይለ ስላሴና የኮ/ል መንግስቱ መንግስታት ከሶማሊያ የተቃጡ ሁለት ወረራዎች (1953 እና 1969) በአመርቂ ሁኔታ ከመከቱ በኃላ ወደ ሶማሊያ ምድር ዘልቀው ያሻቸውን ማድረግ ይችሉ ነበር። ከወታደራዊ አቅምና በወቅቱ ከነበረው የጦርነቱ ሂደት ሙቀት ( Momentum ) አኳያ በ 1953 ጄ/ል አማን አንዶምም ሆነ በ1969  የነበሩት ጄኔራሎች ሙላቱ ነጋሽ ፣ ደምሴ ቡልቶ፣ መስፍን ገብረ ቃል ኣንዲሁም ሌሎች ጀነራሎች ስትራቴጅካዊ እዝ ስር የነበረው የኢትዮጵያ ሰራዊት ሞቋዲሾን ከመያዝ የሚያግዳቸው እምብዛም ችግር አልነበረም። ነገር ግን የወደፊቱንና የሩቁን በማሰብ ሶማሊያ ውስጥ ገብቶ በሃይል ግዛቶችን መያዝ ለወደፊቱ የአካባቢያዊ ሰላም ጠንቅ ሊሆን እንደሚችል በሳል በሆነ የፓለቲካና  የዲፕሎማሲ  ስሌት በማሰባቸው ነበር ከዚህ የወረራ እርምጃቸው የተቆጠቡት።
ጄ/ል ጻድቃን ቀይ ባህርን የመቆጣጠር አባዜ ቢያንሰራራበትና ለጥቆም “የባህር በር ማጣት አልነበረብንም” በሚል ጸጸት በስተርጅና የመጣ ቢመስልም  እሱም ሆነ ድርጅቱ  ህወሃት ለዚህ የኢትዮጵያን ያለ ባህር በር መቅረት ሃላፊነቱን አንድ ጊዜም ቢሆን ወስደው አያውቁም። “መለስ ዜናዊ ስለ አሰብ መደራደር ይችል ነበር” በማለት ሀርማን ኮኸን በበርካታ መድረኮች ላይ ምስክርነቱን ሰጥቷል። በስትሪቴጂካዊ አስተሳሰብ ደደብነት፣ ርዕዮተ ዓለማዊ መደናበርና በተለይም ደግሞ  በሕወሃት ጸረ ኢትዮጵያዊ  ኣቋም ሳቢያ የመጣ ጉዳት ነው። የህወሃት መሪዎች ለዚህ ሃላፊነት ወስደው አያውቁም። “አሰብን ግመሉን ውሃ ያጠጣባት! ” ነበር ያለው መለስ ዜናዊ። ቀጠል አድርጎም “ወደብ እንደማንኛውም ሸቀጥ ነው” በሚል ነበር የተራቀቀው። የስትራቴጂካዊ  ድድብናውን በዓለም መድረክ ያረጋገጠው ብልጣ ብልጡ መለስ ዜናዊና እሱ የሚመራው ህወሃት የወሰዱት አቋም ይህ እንደነበር ጄ/ል ጻድቃን ለመቀበል ዝግጁ እንዳልሆኑ ግልጽ ነው።
ከላይ በተዘረዘሩት ምክንያቶች የተነሳ የሕወሃት አመራሮች ስለባህር በርና የቀይ ባህር ጥያቄን በማንሳትና  በማራገብ ህዝብን ለማጭበርበር አይችሉም። ስለዚህ ጉዳይ ለማንሳት  ምንም  አይነት የሞራል ልዕልና የላቸውምና! ህወሃት የባህር በር ጥያቄን አንስቶ መደራደርና ዘላቂና ሰላማዊ መፍትሄ ለማምጣት ያልቻለው በጸረ ኢትዮጵያ ኣቋሙ ነው። የኢትዮጵያ ህዝብና የቀደሙት መንግስታት የኢትዮጵያን የባህር ሃይልና የባህር ወደቦችን ለማቋቋምና ለማሳደግ በቢሊዮን የሚቆጠር የህዝብ ሃብት በኤርትራ ውስጥ አፍስሰዋል። የምጽዋንና የአሰብ ወደቦችን ለማዘመንና  ለማስፋፋት ብዙ ኢትዮጲያዊያን (ኤርትራውያንን ጨምሮ)  በጊዜው የዕውቀት፣ የላብ፣ የደምና የገንዘብ መስዕዋትነት ከፍለዋል። ከአሰብ 30 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ በምትገኘው  በሃሌብ ደሴት 3ኛ ወደብ፣ ዘመናዊ የጀልባ ፋብሪካ፣ በመጀመሪያ ዲግሪ በባህር ነክ ቴክኒክና ሌሎች ሙያዎች የሚያስመርቅ የባሕር አካዳሚ ( Marine Acadamy)፣ ዘመናዊ የመርከብ ማደሻ ግንባታዎች በጅምር የነበሩበት፣ ያለቁበትና የተገባደዱባቸው በርካታ ሌሎች ፕሮጄክቶችም በኤርትራ ምድር ተሰርተዋል። እነዚህም የኢትዮጵያ ህዝብ አንጡራ ሀብት የፈሰሰባቸው ነበሩ።
ኤርትራን በሚመለከት ብዙ ስህተቶችን በፈጸሙ ሁለት መንግስታት ስር ሰለባ ይሁን እንጂ በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ የኢትዮጵያ ጀግና ልጆች አይተኬ መስዕዋትነትን መክፈላቸው የሚካድና የሚለወጥ ሃቅ ኣይደለም። በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ “ኤርትራ የኢትዮጵያ አካል ነች” አንድ ኢትዮጵያ ብለው ህይወት፣ ደምና አጥንት በኤርትራ ምድር ገብረዋል። ይህ ነው ተብሎ የማይዘረዘር መስዋእትነት ከፍለዋል። የኢትዮጵያ እናቶች የደም ዕምባ እንደ ጎርፍ ፈሷል። እናት ኣባት ልጆቻቸውን ተነጥቀዋል። ሚስቶች ባሎቻቸውን፣ ልጆች ኣባቶቻቸውን በኤርትራ ምድር ላይ በተደረገ ከ30 አመታት በላይ በፈጀው ጦርነት አጥተዋል። ከ60ሺ በላይ ኤርትራውያን በ30 አመቱ ትግል ተሰውተዋል። በብዙ ሺ የሚቆጠሩ ኤርትራውያን ኣካለ ጎዶሎ ሆነዋል። ለስደት፣ ለእንግልት፣ ለእስርና ለሰቆቃም ተዳርገዋል።  ልክ እንደ ኢትዮጵያ እናቶች ሁሉ የኤርትራ እናቶችም ልጆቻቸውን በእሳት ተነጥቀው የደም እምባ አልቅሰዋል። ሚስቶች ባሎችቻቸውን፣ እህቶች ወንድሞቻቸውን፣ ልጆች አባቶቻቸውን አጥተዋል።
በኤርትራ ምድር ለተካሄደው ጦርነት፣ በሁሉም ወገን ለተከፈለው የህይወት መስዋእትነት፣ ይህ ነው ለማይባል የወደመ ንብረት፣ ለተገበረው ህይወት፣ ለተከሰከሰው አጥንት፣ እንደጎርፍ ለወረደው ደም፣ እንደ ዥረት ለፈሰሰው የሚሊዮኖች ዕምባ በዋነኛነት ተጠያቂዎቹ በጊዜው የነበሩ የኢትዮጵያ መንግስታት ናቸው። የአለም አቀፍ ህግን በመጣስ የኤርትራን ፌዴሬሽን ከማፍረስ (ባለራዪው የኢትዮጵያ ባለውለታ ጸሃፊ ትእዛዝ አክሊሉ ሃብተወልድ ቀጣይ የሚያመጣው ቀውስ ቀድሞ ታይቷቸው ፌደሬሽኑ እንዳይፈርስ ቢማጸኑም) ጀምሮ የኤርትራን ህዝብ በፊዴሬሽኑ ያገኛቸውን ልዩ ልዩ መብቶች እስከመግፈፍ፣ በቀጣዩም አመታት የህዝቡን ጥያቄ በአግባቡና በሰላማዊና ፍትሃዊ በሆነ መንገድ ለመያዝና  ለመፍታት አለመቻላቸው እንደነበር ሌላው ሊካድ የማይገባው የታሪክ እውነታ ነው።
ይህ ግን  የተዘጋ የታሪክ ምዕራፍ ነው። አሁን ኤርትራ ነጻና ሉዓላዊ ሀገር ናት። የኢትዮጵያ ህዝብ ከኤርትራ ህዝብ ጋር የሚኖረው የወደፊት ግንኙነት ይህን ሐቅ፣ ይህን እውነታ ከልብ በመቀበል ይጀምራል።  የኢትዮጵያ የባህር በር ጥያቄም ሆነ  ከቀይ ባህር ጋር የተያያዙ የኢኮኖሚ፣ የደህንነት፣ የወደብና ሌሎች ጥቅሞችም ሆኑ ስጋቶች ሊነሱና ምላሽ ሊያገኙ የሚችሉት የህወሃት አገዛዝ  በኢትዮጵያ ህዝብ ላይ የጫነው የአንድ ብሄር የበላይነት ኣፓርታይድ የፖለቲካ ስርአት ሲገረስስ ብቻ ነው!! ለሁሉም ብሄሮች ፍትሃዊ የሆነ፣ ለሁሉም ዜጎች ነጻነት፣ መብቶችና ጥቅሞች የሚቆም ሀቀኛ የዴሞክራሲያዊ ስርአት ሲመሰረት ብቻ ነው!! በውጭ ሀይሎች የአይዞህ ባይነትና የተላላኪነት ሚና፣ እንዲሁም በኢትዮጵያ ህዝብ ላይ አልፎም በአካባቢው ላይ ያለውን የበላይነት ለማስቀጠል የህወሃት አገዛዝ በሚፈጽማቸው ዘርፈ ብዙ  የመሰሪነትና የውንብድና ታክቲካዊ ስሌቶች ሳይሆን ዘመን ተሻጋሪ፣ ስትራቴጂካዊና ሁለንተናዊ  ግንኙነቶች ላይ የተማከሉ፣ የአካባቢውን ህዝቦች የጋራ ዘለቄታዊ ጥቅም የሚያረጋግጡ፣ በእኩልነትና በመከባበር መርሆዎች ላይ የተመሰረቱና  በአለም አቀፍ ህጎች አግባብ መሰረት የሰጥቶ መቀበል ውይይቶችና  ድርድሮች ሲደረጉና ሲፈቱ ብቻ ነው!!
የኢትዮጵያና የኤርትራ  ህዝቦች ዘላቂና ስትራቴጂካዊ ሽርክና “Partnership” የሚረጋገጠው በሰላማዊና የአለም አቀፍ ሕግን በተከተሉ ውይይቶች፣ ድርድሮችና ስምምነቶች ላይ በተመረኮዘ የጋራ ውሳኔ ላይ ሲደረስ ነው። ከዚህም ባሻገር በረጅም ዘመን ታሪክ ውስጥ ተገንብቶ የቆየውንና አሁን በሕወሃት ሳቢያ እየተሸረሸረ የመጣውን ጥልቅ የረጅም ዘመናት ታሪካዊ ተጋምዶ፣ ትስስሮችና ዝምድና የሚያንሰራራ፣ የሁለቱን ህዝቦች ወንድማማችነት የሚያጠናክር፣ የሁለቱንም  ሀገሮችና ህዝቦች  ስትራቴጂካዊ  ጥቅም  ባመከለ መልኩ  በሚከወን ግልጽና ፍትሃዊ ሂደት ብቻና ብቻ ነው።  በሰላምና በድርድር ሁሉንም ግዙፍ ጉዳዮች ማለትም የሁለቱንም ሀገሮች ህዝቦች ዘላቂ የሆኑ የደህንነት፣ የጋራ የኢኮኖሚ ብልጽግና ማሕበራዊና ሌሎች ትስስሮችን አጠናክሮ፣  ከባህር በርና ወደብ ጋር ተያይዞ የሚነሱትንም ጨምሮ  ለዘለቄታው የሚያስቀጥሉና የሚያረጋግጡ ድርድሮችና ስምምነቶች የማይስተናገዱበትና የማይፈቱበት ምክንያት ሊኖር አይችልም። ከሁለቱ ሀገሮች አልፎ የአፍሪካ ቀንድ ህዝቦችን የጋራና ዘለቄታዊ ሰላም፣ ደህንነትና እድገት ለማረጋገጥም ቢሆን አለም አቀፍ ሕግን የተከተሉ፣ ግልጽና ፍትሃዊ  አካሄዶችና የፖለቲካና  የፖሊሲ አቅጣጫዎች ሲቀመጡ ብቻ ነው። ለዚህ  ሁሉ ራዕይና ግብ በተግባር አለመተርጎም ትልቅ ጋሬጣ ሆኖ ያስቸገረው የህወሃት መሰሪና ዘረኛ አምባገነናዊ አገዛዝ ነው።
በሶማሊያና በደቡብ ሱዳን ለሚገኙ ችግሮችም ሆነ ከኤርትራ ጋር ላለፉት ረዥም አመታት የተደነቀረው ጦርነትም ሰላምም የሌለበት ሁኔታ “No war, no peace” ተጠያቂው የህወሃት ዘረኛና ዘራፊ አምባገነናዊ አገዛዝ ነው። ባጭር አነጋገር ሕወሃት ተቆርጦ መጣል ያለበት የምስራቅ አፍሪካ ካንሰር ነው! ከመቶ ሺ በላይ የድሀ ኢትዮጵያውያን  ልጆች ደም ከተገበረበት የኢትዮ ኤርትራ ጦርነት ማግስት በሄግ ላይ የተሰየመው የአለም አቀፉ ፍርድ ቤት ባድሜን ለኤርትራ  በይኖላት ሳለ በወቅቱ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር የነበረው ህወሃቱ አቶ ስዩም መስፍን  “ባድሜ ለኢትዮጲያ ተወስኗል” የሚል ያደባባይ ቅጥፈት ተናግሮ እንደነበር የሚረሳ አይደለም። ዛሬም ድረስ  ባድሜ ራሱ ህወሃት በተስማማበት የአልጀርሱ ስምምነትና የሄግ የድንበር ኮሚሽን የበየነውን “ባድሜ የኤርትራ ግዛት” መሆን አልቀበልም ብሎ የኤርትራን ግዛት በህይል ተቆጣጥሮ እስክአሁን ድረስ  አለም አቀፍ ሕግን ኣሻፈረኝ ያለው የህወአት አገዛዝ እንጂ “የአቶ ኢሳያስ አፈወርቂ መንግስት” እንዳልሆነ ህሊና ያለው ሁሉ መፍረድ የሚችለው ነው። ጀ/ል ጻድቃንም ሃቁ ይህ በመሆኑ ከኤርትራ ጋር ላለው No war , no peace “ ሁኔታ ተጠያቂና  የሰላም ነቀርሳ የህወሃት ኣገዛዝ መሆኑን መቀበል ባይፈልጉ አይፈረድባቸውም።  ህወሃትነታቸው አሁንም  ይጎትታቸዋልና።
በኢትዮጵያ ህዝብ ላይ ብሎም በአፍሪካ ቀንድ ላይ የበላይነትን ለማረጋገጥና  ለማስቀጠል ሲል ሕወሃት የሚያደርገውን ዘርፈ ብዙ መሰሪ ጥረቱን አምርሮ እንደሚገፋበትና ምናልባትም እስካሁን ያልታዩ የጭካኔና የውንብድና ተግባሮችን አጠናክሮ እንደሚቀጥልበት ማወቁና መዘጋጀቱ አዋቂነት ነው። የአለፈው ታሪኮቹ የሚመሰከሩበት ከዚህ ውጭ ሊያስብና ሊተገብር የማይችል እኩይ፣ እጅግ አደገኛ ሀይል መሆኑን ይመሰክሩበታልና። በመሆኑም የአብሮ መኖር፣ የደህነትና የሰላም ጠንቅ የሆነው ህወሃት ዘረኛ፣ አድሎአዊ፣  አፓርታይዳዊ አገዛዝ የስልጣን እድሜ በተራዘመ ቁጥር የኢትዮጲያ ህዝብ አብሮ የመኖሩ ጉዳይም ሆነ   የኢትዮጵያን ህልውና እንደሀገር የማስጠበቁ ጥያቄ ብሎም የአፍሪካ ቀንድ ሕዝቦች የደህንነትና  የዘላቂ ሰላም ዋስትና መፈጠር የሩቅ አለም ሕልም ሆኖ እንዳይቀር እጅግ ያሰጋል። በመሆኑም ይህንን ሕወሃት የሚባል የዘረኛ አፓርታይድ ካንሰር የማስወገድ ኃላፊነቱ ለነገ የማይሉት የመኖር ወይንም ያለመኖር አንገብጋቢ ጉዳይ ይሆናል!!!
ነጻነት ቡልቶን ቀጥሎ በተቀመጠው የኢሜልና ፌስቡክ አድራሻ ማግኘት ይቻላል።

No comments:

Post a Comment