Translate

Wednesday, October 24, 2012

ይህ ከአዲሳባ ወዳጆቼ ጋር የተጨዋወትኩት ጨዋታ ነው።


Abe Tokchaw
ኢህአዴግ አቅም እንደሌለው ግለሰብ እዚህም እዛም ደጋፊ ሁኑኝ እያለ ሰዎችን እያስቸገረ ነው አሉ!
ባለፈው ጊዜ አንዷ የመንግስት መስሪያ ቤት ሰራተኛ አለቃዋ መጥሪያ አንቃጭለው ጠሯት። እርሷም፤ “አቤት ጌታዬ ምን ልታዘዝ” ብላ ሄደች! ጌታዋ ግን “ኢህአዴግ ጌታ ነው! አሜን በይ!” አሏት። ነገሩ እንዲገጣጠምልኝ ብዬ እንጂ አባል መሆን እንዳለባት ሰበኳት ለማለት ፈልጌ ነው። “ገብቶኛል ባክህ…” ካሉኝ “ድሮም የገባዎት እኮ ኖት” ብዬ አቆላምጪዎ እቀጥላለሁ።
ልጅት ግን ነገሩ የሚያመጣው ጦስ ጥንቡሳት አልገባትም ነበርና “እምቢኝ” አለች። “ውድ አለቃዬ ይቅርታ ያድረጉልኝና ስብሰባ ምናምን ደስ ስለማይለኝ የኢህአዴግ አባል ለመሆን ፍላጎት የለኝም።” ብላ ለአለቃ በሚገባ ትህትና ነገረቻቸው። እሳቸውም “ይቻላል ጥርግ በይ!” ብለው አሰናበቷት።
ቀጥላ ጓደኛዋ ተጠራች። ጓደኛዋ ከመግባቷ በፊት በጆሮዋ ለምን እንደተፈለገች አንሾካሾከችላት… እርሷም “አረ ባክሽ…!  ደ…ፋር! በያቸው!” ብላ ገባች።
ተመሳሳይ ጥያቄ ቀረበላት ከጓደኛዋ ጋር ሆና “ደ….ፋር” ያለችውን ባትደግመውም ደፍራ ግን “እኔ እንዲህ አይነት ነገር አይመቸኝም ይቅርታ” አለቻቸው እና ወጣች። አለቅየው ተበሳጩ! “ተደፍረናል ተዋርደናል ብታምኑም ባታምኑም በቁም ሞተናል!” ሳይሉም አይቀሩም!
እነዚህ ሁለት ኮረዳዎች አባልነትን እምቢኝ ብለው በመስሪያ ቤታቸው ውስጥ አንገታቸውን አቀርቅረው ስራ ስራቸውን መስራት ቀጠሉ! ሰላማቸው ግን አልቀጠለም። በየሰበባ ሰበቡ ቅጣት በየሰበባ ሰበቡ እርከን ክልከላ ተከታተለባቸው።
ይህ በእንዲህ እንዳለ እኒያኛው ጠቅላይ ሚኒስትር ሞቱ! በስንተኛው ቀን “ሁሉም ሰራተኛ ጥቁር ለብሶ ይምጣ ለቅሶ እንደርሳለን” ብለው ቆፍጣናው አለቃ አዘዙ!
ታሪከኞቹ ሁለት ኮረዳዎች አንዷ ጥቁር ልብስ የለኝም ብላ፤ ሌላይቱ ደግሞ ከዚህ በፊት በደረሰብኝ የቤተሰብ ሀዘን በርካታ ጊዜ ጥቁር ለብሼ ስለነበር ከዚህ በኋላ ጥቁር እንዳትለብሺ ብለው ንስሐ አባቴ ገዝተውኛል። በሚል ጥቁር ሳይለብሱ ሄዱ! አሁንም አለቅዬ ተበሳጩ። (የእዚህ ልጆች ጥቁር አለመልበስ እርሳቸውን ስለሚያስጠቁራቸው ባይበሳጩ ነው የሚገርመው ብለው ማሰብ ይችላሉ!)
ይኸው ከዛች ቀን በኋላ እኒህ ሁለት የመንግስት ሰራተኞች ለመስሪያ ቤታቸው የእንጀራ ልጅ ሆነው እየኖሩ እንደሆነ አወጉኝ! አንዷማ በቅርቡ ለስንት አመት ቀጥ ለጥ ብላ የሰራችበትን የስራ መደብ፤ “አንዲት በአብዮታዊ ዲሞክራሲ የምትምል አዲስ ምልምል እንዳለማምዳት ተነገረኝ በስንተኛውም ጊዜ ላለማመድኳት ልጅ ረዳት ሁኚ ተባልኩ” ብላ ነገረችኝ!
ቀጣየቷ ልጅ ደግሞ በእስር ላይ ከሚገኙ ጋዜጠኞች የአንዳቸው ቤተሰብ ናት። የዝች ደግሞ አስገራሚ ነው። እርሷን እስካሁን ደረስ ማንም መጥቶ የተናገራትም የሰባካትም ያስቦካትም የለም። (ያስቦካት ማለት፤ “አስቦካሁ…!” እንዲል የአራዳ ልጅ ያስፈራራት ማለት ነው!)
ነገር ግን እስካሁን ድረስ ሶስት የግል መስሪያ ቤቶች ከቀጠሯት በኋላ ይቅርታ እየጠየቁ ከስራዋ አሰናብተዋታል። ለምን? ስላት፤ “ከመንግስት የተላኩ የደህንነት ሰዎች “ለመሆኑ አቅቀሃት ነው የቀጠርካት!? ለማንኛውም አስብበት ለራስህ ብለን ነው ልጅቷ የእንትና ዘመድ ናት ከእነ እንትና ጋር ግንኙነት አላት ስለዚህ አስብበት”” ብለው ለአስሪዎቿ “ሀርድ” ይሰጣቸዋል። እነርሱም በነጋታው “ይቅርታ ሌላ ስራ ፈልጊ!” ብለው ሲያሰናብቷት አሁን በቅርቡ ሶስተኛ መስሪያ ቤቷን ለቀቀች።
መንግስት በዝች ልጅ ላይ ያሰበው ነገር ምን እንደሆነ እንጃ…! ከጓደኞቿ ጋር ውላ ልክ ስትለያይ አብሯት የዋለው ገደኛዋ ከመንገድ ላይ ይጠራና “ከዝች ልጅ ጋር ያለህ ግንኙነት ምንድነው!? ለመሆኑ ማንነቷን ታውቃለህ…? እኛ ምን ቸገረን ለአንተው ብለን ነው ጥንቃቄ እንድታደርግ ለመምከር ነው!” ብለው የደህነንት መታወቂያ ካርድ አሳይተው ይሰናበቱታል።
ቢቸግረኝ ጠየኳት “አልገባኝም መንግስት የሚፈልግሽ ለፍቅር ነው እንዴ!?” አልኳት። እርሷ ሳቀች። እኔ ግን ግራ ገባኝ!

No comments:

Post a Comment