Translate

Wednesday, September 12, 2012

መለስን ማን ቀሰፈው? ስንብተ መለስ ወ-ስንብተ 2004 ዓ.ም


በወፉ
ዜና በጨዋታ፤ ኢህአዴግ መለስን ሳይተካ ስብሰባውን ቋጨመለስ ብዙ ነገሩ ዘሩ ውልደቱ እና ኑሮው ተደብቆ ኖረ፡፡ በድብቅ ሞተ፡፡ የመለስ የሞቱ ምክንያት አይተወቅም ወይንም በእውቀት ደብቀዉታል፡፡ ሌላው ተሸፋፍኖ የቀረው መለስ ይችን አለም መች እንደተሰናበተ ነው፡፡ በአንዳንድ መረጃዎች መሰረት መለስ ከሞተ ምናልባት ከአንድ ወር በኋላ ነው የተነገረው የሚለውን በእብዛኛው ይታመናል፡፡ የኢትዮጲያ ቴሌቪዥን ወይንም ታጋይ በረከት ስምዖን አለም ትገለባበጣለች እንጂ ተገለባብጦም ገለባብጦም በሞተ ማግስት የመለስን ዜና እረፍት ይናገራል ማለት በረከትን አለማወቅ ነው፡፡ ጓድ በረከት ስምዖን እንዳወጋን የሁለት ምርጫዎች  ወግ በሚለው መፅሃፉ እንዳሰፈረውም መለስ በረከትን በረከት ወይንም ጓዴ ብሎ አይጠራውም ሰውየው ( the man ) እያለ ነው የሚጠራው፡፡ ስለዚህ በረከት ምን የመሰለ የመለስ ጥይት እንደሆነ ህዝቡ አልተገነዘበውም፡፡ የእነ ስየን የበላይነት እየተከታተለ ትጥቅ ያስፈታ ተንኮሉ ነው፡፡ መለስ ሰውየው ያለው በተንኮሉ ከእሱ ስለማያንስ ነው፡፡ በረከት ፖለቲካዊ ጤንነትን (politically correctness ) መገንባት ብቻ ነው የሚያሳስበው፡፡ ሌላው አያሳስበውም አያስጨንቀውም፡፡
ስሙ ታማኝነቱ መወደዱ የመለስም ሞት ጭምር፡፡ ለማንኛውም መለስ መች ሞተ ለሚለው በረከትን (የኢትዮጲያ ቴሌቪዥን ሳይሆን )ሌላውን ሚዲያ ማመን ተገቢ ይመስላል ማለትም ቅምር እሳቦት( calculated thinking) ይሆናል፡፡
ሌላው የመለስን ሞቶ ሰንብቶ ከቆየ በኋላ በዜና መነገሩን የሚያስረዳን የአንጋፋው ወያኔ የአባይ ፀሃዮ ንግግር ነው፡፡ አባይ የነገሩን መለስ ታሞ ሆስፒታል ከገባ በኋላ ወደ ሆስፒታል እየሄደ ይጠይቀው የነበረው ብርሃኔ ገብረ ክርስቶስ እና አዲሱ ለገሰ ከወ/ሮ አዜብ መስፍን ጋር ነበረ፡፡ የመለስ እሬሳ ወደ አዲስ አበባ በመጣበት ጊዜ ከወ/ሮ አዜብ በስተቀር ሁለቱም ማለትም ብርሃኔ እና አዲሱ እንባቸው ደርቆ ነበር፡፡ የዚህ ምክንያት ሲያለቅሱ ስለከረሙ ይመስለኛል(ይመስለኛል የምትለዋን ያዙልኝ)፡፡ ታዲያ የአዜብ እንደዚያ እያለቀሰች የታየችበት ምክንያት ትኩስ ሬሳ ስለሆነ ሳይሆን ለክብራቸው ሚነስተሮች ተሰባስበው በወታደሮች ታጅበው መለስ በዕብሪት አዜብ በክብሪት በዚያ ቀይ ምንጣፍ  እያስጎነበሱ እያሸበሩ የተራመዱባት ኤርፖርት ሬሳ ይዞ ከተፍ ሲል ህዝቡ ተናጋሪውን ባላቸውን ሳይሆን በድናቸውን ለመቀበል ተሰብስቦ ሲያዩ ተሸበሩ አዘኑ ሁሉ ነገር ትዝ አላቸው፡፡ ለቅሳቸው የትዝታ ነበር፡፡ ሁሉን ነገር ስትመለከቱት ትዝታ ነበር፡፡ ስለዚህም መለስ ከሞተ ቆይቶል የምትለዋ ልቤን ታማልላለች፡፡
መለስ መቼ ነው የሞተው የሚለው ምስጢር ሆኖ መሰንበቱ ፋይዳውን ለወያኔው ቡድን እንተዎው፡፡ ይኼ ምስጢር በመሆኑ ከማይከፉት ሰዎች ወስጥ አንዱ ነኝ፡፡ ምክንያቱም ለ21 ዓመት ሁሉን ነገር( ሁሉን ነገር ማለት ሁሉን ነገር ማለት ነው) ጠፍንጎ ይዞ የገዛው ጠቅል መለስ በድንገት ሲቀሰፍ (መቅሰፍት ላይሆንም ይችላል) ለኢህአዴግ መረጋጋት ሲሉ አድርገውት ከሆነ ብሶት የወለደው የኢህአዴግ ሰራዊት ፍርሃት የወለደው የኢህአዴግ ሰራዊት በመሆን ፖለቲካዊ ጨዋታ ጀምሮል በማለት ልለፈው፡፡ ይህችን ሃሳብ ልትመራመሩባ የምትሹ ልትመራመሩባት ትችላላችሁ፡፡ እንደ ብፃይ መለስ መንገዱን ጨርቅ ያድርግላችሁ በማለት መርቄያችሃለሁ፡፡
ወደ ዋናው የዚህ ፅሁፍ ሃሳብ ልምጣና መለስን ማን አከመው የት ታከመ እና የመሳሰሉት ነገሮች ወደፊት የእርሱን ታሪክ ለመፃፍ የወደደ ሊመራመርበት ይችላል፡፡ እኔ ግን ከጊዜው የፖለቲካ ፍጆታ ጋር የሚሄደውን መለስን ማን ቀሰፈው?  የሚለውን ለመጠየቅ እፈልጋለሁ፡፡በነገራችን ላይ በመለስ ሞት ምክንያት ላይ ብዙ መላምቶች አሉ፡፡ እነዚህን መላምቶች እንደፀባያቸውና እንደ ቁምነገራቸው ሚዛን ከቅለት ወደ ክብደት  ልንደርደር፡፡ እነዚህ ሁሉ የመለስ ሞት ምክንያቶች ከዝቅተኛው የህብረተሰብ ክፍል እስከ ከፍተኛው ፤ካልተማሩት እስከተማሩት የህብረተሰቦች ክፍሎች አቶ ሃይለማሪያም ደሳለኝ እንዳሉት በዝርዝር የተከበሩ የአንደኛ ደረጃ ት/ቤት መምህራን  የተከበሩ የሁለተኛ ደረጃ ት/ቤት መምህራን   የተከበሩ የሦስተኛ ደረጃ ት/ቤት መምህራን (ይህች የኔ ናት )  የተከበሩ የኮሌጅ መምህራን የተከበሩ የዩኒቨርስቲ መምህራን…የተከበሩ አሮጊቶች የተከበሩ ህፃናት የተከበሩ በሽተኞች የተከበሩ የአዕምሮ ህመምተኞች (ይህችም የእኔ ናት ) የተከበሩ የጎዳና ተዳዳሪዎችን ሁሉ ያጠቃልላል፡፡ የሞቱን ምክንያት ቅስፈተ ምክንያትበማለት ልዘርዝር፡፡ በነገራችን ላይ ከምክንያቶች ውስጥ ኤች አይ ቪ ኤድስ ነው የገደለው የሚለውን ከማንም ባለመስማቴ የኢትዮጲያ ህዝብ ጨዋነት አስተዋይነት እና ግመት የመስጠት ችሎታ ያስደንቀኛል፡፡ ለዚህም ለኢትዮጲያ ህዝብ ዝቅ እንላለን እጅ እንነሳለን፡፡ በመቀጠልም መለስ በዚህ ጉዳይ ለመታማት እንኳን በማያስችል ሁኔታ ቁጥብ በመሆኑ እና ከምንዝርና   ነፃ በመሆኑ እናመሰግናለን እጅ እንነሳለን፡፡ ከዚህ በኋላ የሚመጡት መሪዎችን በአንድ ሚስት እንዲወሰኑ ከመለስና ከመንግስቱ ኃይለማርያም ይማሩ ዘንድ እንመክራለን፡፡
የሞት ነገር ከተነሳ አፄ ቴዎድሮስ እና ዮሃንስ የሞቱበት ቀንም ምክንያትም ይታወቃል፡፡ ምኒልክ የሞቱት በቁርጥማት በሽታ ነው የሚሉ አሉ፡፡ አንዳንዶች መድሃኒት ተሰጣቸው ነው ይላሉ፡፡ ከተጥርጣሪው ውስጥ ጣይቱም አሉበት፡፡ ወሬ ነው፡፡ አፄ ኃይለ ስላሴ በምን ምክንት እንደሞቱ ከደርግ ውጭ ሁሉም የሚያምነው ደርግ መድሃኒት ሰጥቷቸው ነው፡፡ መንጌ እንዴት እንደሚሞት አይታወቅም፡፡ የመለስ ሞት ምክንያት በደንብ አልተገለፀም፡፡ አንዳንዶች መለስ በቅርቡ ሊያካሂድ ያለውን የፀረ ሙስና እቅድ ስላወቁ ሙሰኞች የተመረዘ ምግብ አብልተዋቸው ነው የሚሉ አሉ፡፡ ከሚጠረጠሩት ውስጥ ወ/ሮ አዜብ አሉበት፡፡ ይህ ግን እውነት አይመስለኝም፡፡ ወደ ሌላው ምክንያተ ቅስፈት እናዝግም፡፡
ቅስፈተ ምክንያት 1
የመለስ ሞት እንደተሰማ ኧረ እንዲያውም መታመሙ እንደተሰማ አካባቢህዝቡ የጋናውን ፕሬዜዳንት  መሞት ካየ በኋላ መሰለኝ በአዲስ አበባችን የተናፈሰው ይህ ወሬ፡፡ አንዳንዶች መለስ የታመመውና የሞተው አሜሪካ በጨረር መታው ነው ይላሉ፡፡ ይህን ያወጉኝ ሁለት ሰዎች ነበሩና እነዚህ ያልተማሩ ሰዎች ከፀሃይ ጨረር ወጭ ስለ መርዛማ ጨረር ምንም አያውቁም ግና አሜሪካ እንደገደለቻቸው በስፋት ያወጋሉ፡፡ ይህ እውነት አይደለም (አይመስለኝም) ምክንያቱም መለስን የመሰለ የአሜሪካ ታዛዥ ባሪያ በታሪክ የለም፡፡ ሶማሊያ ግባ ሲባል ዘሎ የሚገባ አገር ገንጥል ሲባል የሚገነጥል ታዛዥ የአሜሪካ ቦይ የለምና ይህ ሃሳብ ተቀባይነት የለም፡፡ ከዚሁ ጋር ግን ይህ ተራ ንግግር የሚጠቁሙንን ሃሰብ እንውሰድ 1ኛ አሜሪካ የአንድን አገር መሪ እንደሸንኮራ መጣ ከሸጨረሰችው በኋላ የምትጥል አገር ስለሆነች የሚመጣው መንግስት አገሩን ከአሜሪካ ጥቅም ማስቀደም ይኖርበታል የሚል ሲሆን 2ኛ ይህ ንግግር የሚያሳብቀው ጉዳይ መለስ ለሞት የሚያበቃውን ምክንያት ያገኘው በዴቪድ ካምፕ ስብሰባ አካባቢ መሆኑን ነው፡፡ አትርሱ በዚያን ጊዜ መለስ ላይ ጋዜጠኛ አበበ የጮኸበት ወቅት መሆኑን ፡፡ ያም ሆነ ይህ ሞቱ ድንገተኛ መሆኑን ያሳብቃል፡፡
ቅስፈተ ምክንያት 2
የመለስ ሞት በኢትዮጲያ ኦርቶዶክስ መናኒያን ላይ በወሰደው አቛምና ዋልድባን በመድፈሩ ነው የሚሉ አሉ፡፡ ይህን በተደጋጋሚ በአዲስ አበባም በውጭው አለምም  የሚናፈስ ምክንያት ነው፡፡ ይህን ምክንያት ጠንካራ እምነት ያላቸው የቤተክርስቲያኑ ምዕመናን በብዛት የሚያነሱት ሃሳብ ነው፡፡የአባ ጳውሎስም ሞት ከዚሁ ጋር ተዳምሮ ሲነሳ ሰምቻለሁ፡፡ ክርስቲያን ሁሉ ይህን ቢያምን አያስደንቅም፡፡እግዚአብሔር እርስቱን የመሰማሪያ በጎቹን ለማላገጫ አሳልፎ አይሰጥም ይላል ቅዱስ ቃሉ፡፡ ደግሞም በሌላ ቦታ ወደ ድሃ አደጉ እርሻ አትግባ ታዳጊያቸው ፅኑ ነው ይላልና ቃሉ አይሆንም አይባልም፡፡ ይሁን እንጂ በእኔ ምክንያት የለሽ ሃሳብ ተቀባይነት የለውም፡፡ ሆኖም ግን ይህ ንግግር ሁለት ሃሳቦችን ያሳብቃል 1ኛ መለስ የሃማኖት ነፃነትን ሰጥቻለሁ ብሎ በአንድ በኩል ሌላ የህገ መንግስት ጥሰት እየፈፀመብን ነው ሲሉ የክርስቲያኑ ማህበረሰብ ከመለስ ጋር ሆድና ጀርባ መሆናቸውን ነው፡፡ 2ኛ መለስ የዋልድባን ገዳም መዳፈር የጀመረበት ወቅትና ተቃውሞው የተካሄደው አስታውሱ ጋዜጠኛ አበበ በመለስ ላይ በኃይል ያምባረቀበት ወቅት ነበር፡፡ ያም ሆነ ይህ ግን ይህም ሃሳብ የመለስ ሞት ድንገተኛ መሆኑን ያሳብቃል፡፡
ቅስፈተ ምክንያት 3
የመለስ ሞት እንደ ተሰማ አንድ የተማረ በማህበራዊ ሳይንስ ጥናት ተቓም ውስጥ ተቀጥሮ የሚሰራ ሰው ያወጋኝ ሰዎች መለስ የሞተው ማርተኞች አᎂረተውበት ደጋሚዎች ድግምት አድርገውበት ጠንቛዮች ጥንቆላ ሰርተውበት ነው ይላሉ ብሎኛል፡፡ ይህ ለኔ ሚዛን አይደፋም፡፡ በነገራችን ላይ ሰይጣን እንዳለ ᎂርት እንዳለ ጥንቆላም እንዳለ አምናለሁ፡፡ እግዚአብሔር አለ ስላለ፡፡ ቅዱሱ ቃል የᎂርተኞችን ᎂርት አሳብዳለሁ ስለሚል፡፡ ሆኖም ግን ጠንቛዮች ታምራት ገለታን ጨምሮ ለምን መግደል ከቻሉ ቀደም ብለው አልገደሉትም ያስብላል፡፡ ባለምንበትም ይህ ንግግር ሁለት ነገሮችን  ያሳብቃል 1ኛ መለስ የሃይማኖትን ነፃነት ሰጥቻለሁ እያለ ( የማምለክም ያለማምለክም ነፃነት) በግለሰቦች የዕምነት ነፃነት ላይ ከፍተኛ ተፅዕኖ በማሳደር ከጠንቛዮች ጋር ሳይቀር ሆድና ጀርባ መሆኑን ሲሆን 2ኛ መለስ ጠንቛይ ጋር ተጣልቷል እየተባለ የተወራበትን ጊዜ ብናጠናው ለልማት መሬቱ ይፈለጋል እያለ የማምለኪያ አፀዳቸውን ያፈረሰበት ጊዜ ጋዜጠኛ አበበ ገላው በድምፀ ነጎድጋድ ኃይሉ ልቡን ያንቀጠቀጠው በዚያን ወቅት ነበር፡፡ ተረዱኝ መሬቱን ለምን አለማ አይደለም የእኔ ሃሳብ በመግባባት መፈጸም ለምን አልፈለገም ነው፡፡ ያም ሆነ ይህ መለስ ተራራውን አንቀጥቅጦ በአበበ ተንቀጥቅጦ የሞተው በድንገት ነው ወይንም የመለስ ሞት ድንገተኛ ነበር፡፡
ቅስፈተ ምክንያት 4
አንድ የትግራይ ክልል ተወላጅ ሙስሊም አዲስ አበባ እያለሁ ያወጋኝ ትዝ አለኝ፡፡ መለስ የሞተው በሙስሊሞች ዱአ ነው ብሎኛል፡፡ በርግጥ ይህ ወቅት የሙስሊሞች  የመከራ ጊዜ ነው፡፡ ሙስሊሞች  መፀለያቸው አይቀርም፡፡ መፀለያቸውም ተገቢ ነው፡፡ ነገር ግን የሙስሊሞች ዱአ ነው ሁለቱን መሪዎች የገደላቸው የምትለው ንግግር ሚዛን አትደፋም፡፡ እዚህ ጋ የሰው ዕምነት ለመንካት አይደለም ነገር ግን የሙስሊሙ ማህበረሰብ የመከራ ምክንያት የሆኑት ግለሰብ በህይዎት እየኖሩ የክርስቲያኑን ጳጳስ አላህ ቀሰፋቸው ሊባል አይችልም አላህ ሃጂውንም ስለማይፈራ፡፡ ቢያንስ ሁለቱ  ጳጳሱና የመጅሊሱ መሪዎች የተሾሙት በወያኔ መሆኑ ይታወቃልና ነው፡፡ ያም ሆነ ይህ ይህ ሃሳብ ሁለት ነገር ያሰብቃል፡፡1ኛ 99.9 በመቶ ህዝቡ ወዶ መርጦኛል የሚለው መለስ ከሙስሊሙ ማህበረሰብ ጋር ከባድ ግጭት እና መካረር መቃረን እነደነበረበት ነው፡፡ 2ኛ መለስ የሙስሊሙን መብት በሃይል የተጫነበትን ወቅት ብናጤነው ከፍተኛ ግርግር የነበረበት ነበር፡፡ ላስተዋለው ሰው መለስና የሙስሊሙ ማህበረሰብ በተፋጠጡበት ወቅት የኢትዮጲያ የቁርጥ ቀን ልጅ አበበ ገላው ለ21 ዓመት ያሸማቀቀንን መለስን ያሸማቀቀበት ወቅት ነበር፡፡ ያም ሆነ ይህ መለስ በአበበ ተሸማቆ የሞተው በድንገት ነበር፡፡ ድንገተኛ ሞት፡፡
ቅስፈተ ምክንያት 5
በአብዛኛው የመለስ ደጋፊ ወያኔና የኢህአዴግ ባለስልጣናት በተደጋጋሚ የሚናገሩት መለስ የሞተው አንባቢ በመሆኑና ለረጅም ጊዜ ሥራ ላይ ስለቆየ ነው ይሉናል፡፡ ይህ ትክክል አይመስለኝም፡፡ ምክንያቱም ከመለስ ጋደኛ በስራ ብዛት አንድም ሰው የሞተ የለም፡፡ ሁሉም ስራ ላይ ለረጅም ጊዜ ቆይተዋል፡፡ አባይ ፀሃዮ አለ ሥዩም መስፍን አለ አቦይ ስብሃትም አለ በሽተኛው ተፈራ ዋልዋም አለ አዲሱ ለገሰም በረከትም አሉ፡፡ ታዲያ መለስ ላይ ምን መጣ? ደግሞስ ስራ ከበዛበት ማን ያዘው? አይተዎዉም ነበር፡፡ ያም ሆነ ይህ ይህም ቢሆን ሁለት ነገር ያሻውካል ይህ ንግግር 1ኛ መለስ በአምባገነንነት ለረጅም ጊዜ በስልጣን ላይ ሁሉ ቦታ ውስጥ እያማሰለ ቆይቷል የሚል ሲሆን ከዚሁ ጋር እጁን አስረዝሞ ለ21 ዓመት የቆቅ ኑሮ የኖረ ደንጋጣ አምባገነን እንደነበረ እና በጊዜ ስልጣን ማስረከብ ተገቢ መሆኑን ሲሆን 2ኛ ለረጅም ጊዜ በስልጣን ተፈናጦ መቆየት ጣጣው በእንደ አበበ አይነቱ ምላስ ተገርፎ መውደቅ እንዳለ ነው፡፡ የመለስ ድንጋጤ የስንብት ድንጋጤ ሊባል ይችላል፡፡ ዞሮ ዞሮ መለስ በድንገት የአምባገነንነቱን ወንበርና ህይወቱን ያጣ መሆኑን መገንዘብ ተገቢ ነው፡፡
ቅስፈተ ምክንያት 6
መለስን የገደለው የረዥም ጊዜ ተፈጥሮአዊ (አዝጋሚ በሽታ) ነው ለዚህም የቆየ ካንሰር ነበረበት የሚሉም አሉ፡፡ ይህ ሊሆን አይችልም፡፡ ምክንያቱም ከባለስልጣናቱ አንደበት እንደሰማነው ፤ከመለስ የመኖር ዕቅድ እንደተመለከትነው ፤ከወያኔ-ኢህአዴግ ድንጋጤ ፤ከጳጳሱ ድንጋጤ(ግምታዊ) ተነስተን ትንታኔ ስንሰጥ የመለስ ሞት ድንገተኛ ነው፡፡ አባይ ፀሃዮ ሳንጠግበው ነው መለስ የሞተው ብሏል፡፡ ሳንሰነባበት መለያታችን ይቆጨኛል ብሏል፡፡ እንዲሁም መለስ ከብራዚል ሲመለስ ሰውነቱ ተለዋውጦ ስናየው መለስ ምን ሆነ አልን ብሏል፡፡ ስለዚህ ምንም ምስጢር ቢሆንም መለስ የሞተው በአዝጋሚ በሽታ አይመስለኝም፡፡ ይህ ንግገር የሚያሳብቀን ሁለት ነገር 1ኛ መለስ የሞተው በሂደታዊ ክስተት ሳይሆን በድንገተኛ ሞት መሆኑን ሲሆን ሁልጊዜ ተዘጋጅቶ በትህተናና በቅንነት መስራት ጥቅሙን ያሳያል፡፡ ሌላው ትምህርት የሚመጣው መሪ ይህንን እንዲያስብበት እንመክራለን 2ኛ መለስ የሰውነት ለውጥ ያሳየው ከብራዚል እንደተመለሰ ነው ያሉት አባይ  በዚያን ሳምንት እረሰተውት እንደሆነ አሊያም በእቅድ ተዘሎ ነው እንጂ በዚያው ሳምንት መለስ በአበበ በለው የልብ ድንጋጤ መድፌ የተወጋው እንደነበር ነው፡፡ ለ21 ዓመት የኢትዮጲያን ህዝብ በመሳሪያና በምላሱ አንገት ያስደፋው መለስ አንገት የደፋው ህዝቡን ያሸማቀቀው መለስ የተሸማቀቀው በዚያው ሳምንት ነበር፡፡ የመለስ ሞት ድንገተኛ ምክንያት አለው የምለው ለዚህ ነው፡፡
ቅስፈተ ምክንያት 7
ብዙ ሰዎች የመለስን ሞት ከሦስት ነገሮች ጋር ያገናኙታል፡፡ ከነዚህ ሦስት ነገሮች ማለትም በእግዚአብሔር  ቀኑ ደርሶ ሞተ የሚለው አንዱ ሲሆን ይህን ለእግዚአብሔር በመስጠት ወደ ሌላው ሁለት ቀሪ ጉዳይ እንግባ፡፡ አንዱ መለስ የሞተው በኢሳት ᎂርት ነው ብለው የሚያምኑ አሉ፡፡በመጀመሪያ የኢሳት ᎂርት መለስን ገደለው የሚለው የወያኔዎች ቁጭት ነው፡፡ ኢሳት መለስን በᎂርት ገደለው የሚለውን ብናምን አንድ ነገር በርገጠኝነት መናገር እንችላላን፡፡ የነፃውን ፕሬስ አቅም፡፡ በመሆኑም የነፃው ፕሬስ አምባገነን አፋኞችን እና የአምባ ገነን ምሰሶዎች እንደሚያንቀጠቅጥ ያሰየናል፡፡ የታወቀው ጀርመናዊው የማህበራዊ ሳይንስ ተመራማሪ ጃርገን ሃበርማስ ፋሽስታዊ ስርዓቶች ህዝቡን ለመጨቆን ሚዲያውን ተቆጣጥረው እና ነፃውን ፕሬስ አፍነው የተወናበደ  መረጃ (Distorted information) ለህዝባቸው ይሰጣሉ ብሏል ፡፡ መለስ ፋሽስታዊ እንደነበር የሚያሣየን ይህ ነው፡፡ በመሆኑም የኢሳት አቅም በወዳጅ ዘንድ ባይታወቅም የወያኔ የበርሃ ፕሮፓጋንዳ ሃላፊ የነበረው መለስ ነፃው ፕሬስ ምን አይነት አቅም እንዳለው ያውቃል ኢሳትን አጥብቆ ይጠላ ነበር፡፡ መለስ ኢሳትን እንደ እሳት ይፈራው ነበር፡፡ የኢሳት ጋዜጠኞች ንግግር ሲያደርጉ ᎂርት አይደለም ሲሉ መደመጥ ጀምረዋል፡፡ የኢሳት ᎂርት መለስን ገደለችው ወይንም ያᎂርታሉ የምትለዋ ሳትደርሳቸው አትቀርም፡፡ ኢሳት አምባገነን መሪዎችን በᎂርት የምተቀነጥስ ከሆነ ቶሎቶሎ ቀንጠስ ቀንጠስ አድርጊልኝ እንላለን፡፡ የኢሳት አስፈላጊነት ግን ገብቶናል፡፡
ሌላው በስፋት የሚወራው መለስን የገደለው የአበበ ምላስ ነው የሚለው ነው፡፡ የአበበ የምላስ ጨረር ብየዋለሁ፡፡ መለስ ምላስ ገደለው የሚለውን ሁሉም ይስማሙበታል፡፡ አንድ ልጅ ሳሎን ቤት የተቀመጡትን አባቱን ቧንቧ ሲፈነዳበት ጊዜ አባባ ቧንቧ ፈነዳ ቢላቸው ቦንብ ፈነዳ ያላቸው መሰሎአቸው ደረቀው እንደሞቱ ስለ አባቱ ሞት በሃዘን አውግቶኛል፡፡ ይህ እውነተኛ ታሪክ ነው፡፡ የአበበ የምላስ ጨረር ምን ያህል ሃይለኛ እንደነበር ከመለስ ውጭ እኛ ሁሉ አይተነዋል፡፡ መለስ ሲደነግጥ ከመታየቱ በላይ መለስ የታመመው ከብራዚል መለስ ነው የሚለው የአባይ ቃል ምስክር ሊሆን ይችላል፡፡ ይህ ብቻ አይደለም የህላዌ ዮሴፍ መታመሙን ሳንሰማ ማለቱ የአዲሱ ለገሰ በዚህ ሁኔታ እንዲህ ቶሎ ያመልጠናል ብየ አላስብም ማለቱ የአዜብ ተቀጣሁ ማለት የአᎂᎂቱ ፍጥነት  የኢህአዴግ አለመዘጋጀት እና  የሴኩቱሪ ንግግር ሁሉ መረጃ ነው፡፡
ጥያቄው የመለስ ጠባቂ አበበን ዝምብላችሁ ነው የምትጮሁት የሚለው ንግግር በእውነት እርባን የለው ይሆን? ያም ሆነ ይህ እርባን የሌለው ለመሰላችሁ ሁሉ የአበበ ምላስ መለስን እስከ ወዲያኛው አሰናብቶታል፡፡ በነገራችን ላይ የመለስ አጃቢ ዝምብላችሁ ነው የምትጮሁት ያለው አበበ ከመጮሁ በፊት ነበር፡፡ አበበ መለስን በጩኸት ካስደነገጠው በኋላ ግን ዝምብሎ ጩኸት ብቻ አለመሆኑ ሲገባው ደምህን እንጠጣዋለን /እንገድልሃለን ነበር ያለው፡፡ ይህ የሚያሰየው የሰላማዊ ተቃውሞን ጉልበት ነው፡፡ በጫጫታ የፈረሰ ከተማ የለም ከኢያሪኮ በስተቀር የሚሉን የወያኔ ደጋፊ ምሰሶዎች በአበበ ጫጫታ ከተማ ሳይሆን ህያው ቤት መለስ በድንጋጤ ሲፈርስ ታይታል፡፡ ታላቁ መፅኃፍ ታላቁ ካህን ኤሊ የኢስራኤል ህዝብና ታቦቱ በፍልሰጤማውያን መማረኩን ሲሰማ ወድቆ ሞተ ይለናል፡፡ ድምጸት፤ ጫጫታ፤ ሰላማዊ ትግል እና የተቃውሞ ቅመማ ቅመም ሃይል አለው፡፡ አሁን ታዲያ ውሻው ይጮሃል ግመሉ መንገዱን ቀጥሏል ትሉን ይሆን? ውሻው ይጮሃል ግመሉም ይወድቃል ሊባልም ይገባል፡፡ አበበ ይጮሃል መለስ መንገዱን ቀጥሏል የሚለው አሁን የለም፡፡ አበበ ግን አሁንም እየጮኸ ነው፡፡ አበበ ደጋግሞ ሊጮህ ነው አዲሱ ግመል ማስተዋል ይገባዋል ካፈለገ ግን እሱም ተዋርዶ ይወድቃል፡፡ ለማንኛውም 2004 ዓ.ምህረትም መለስም ላይመለሱ ተሰናብተዋል፡፡ እኛ ግን እንጮሃለን፡፡ እስራኤልም ጮኸ እግዚአብሔርም ሰማ ሊያድናቸውም ወረደ ይላልና ቃሉ፡፡

No comments:

Post a Comment