Translate

Friday, September 14, 2012

“የህወሓት የቀድሞ የፖለቲካ የበላይነት ከአቶ መለስ ጋር አክትሟል” በጎልጉል


ኢትዮጵያ ወደ ወታደራዊ አስተዳደር?!

ሰሞኑን ይፋ የተደረገው የከፍተኛ ወታደራዊ ሹመት ህወሓት የፖለቲካ የበላይነቱ ለመመናመኑ ምልክት መሆኑ ተጠቆመ። የጠቅላይ ሚኒስትር ጽ/ቤት የህግ ለውጥ ሳይደረግ በደህንነት ሹሞች የቅርብ ቁጥጥር ስር መዋሉም ተሰማ። የጎልጉል ምንጮች ያነጋገሩዋቸው ክፍሎች መለስ በህይወት እያሉ ሁሉንም ቁልፍ ይዘውት ስለነበር ህወሃት የፖለቲካ የበላይነቱ የተጠበቀና አስተማማኝ ስለነበር የጦር ኃይሉ በፖለቲካው ዘርፍ ቀጥተኛ ተሳታፊ ሲሆን አይታይም ነበር።
ኢትዮጵያን ወደ ፍጹም ወታደራዊ አስተዳደር ለማሸጋገር ደፋ ቀና ሲል የጠቅላይ ሚኒስትር መለስን ህልፈት ሲያስተባብል የቆየው ኢህአዴግ፣ በሳምንቱ መጀመሪያ ለሰላሳ አራት ከፍተኛ መኮንኖች የብርጋዲዬር ጄኔራልነት፣ ለሶስት ብርጋዲየር ጄኔራሎች ደግሞ የሜጀር ጄኔራልነት ማዕረግ መስጠቱን ምንጮቹ ያስታውሳሉ። በተለይም ሃያ ሶስቱ ተሿሚ ጄኔራሎች የትግራይ ተወላጅ እንዲሆኑ መደረጉን አጥብቀው ይኮንናሉ።

ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ሹመት በፊት በጥድፊያ የወታደራዊ ሹመት መቅደሙ የህወሓትን የፖለቲካ ሚዛን መናጋት እንደሚያሳይ ያመለከቱት ተቀማጭነታቸው አዲስ አበባ የሆነ የኦህዴድ ከፍተኛ አመራር፣ “ህወሃት አነስተኛ ቁጥር የሚወክል ድርጅት ሆኖ የፖለቲካ የበላይነቱን እንደ ቀድሞው መቆጣጠር ስለማይችል የጦር ኃይሉን በማጠናከር አመራሩን በወታደራዊና በደህንነት ሃይሉ ቁጥጥር ስር አድርጎ ከጀርባ መሪነቱን ለማጠናከር የወሰደው ርምጃ ከመለስ ሞት መሰማት ማግስት ሲሰራበት የቆየ ነበር” ብለዋል።
የህወሓት የቀድሞ የፖለቲካ የበላይነት ከአቶ መለስ ህልፈት ጋር እንዳከተመ የሚናገሩት ምንጮች መለስ ህይወታቸው ካለፈበት ጊዜ አንስቶ ኃይል የማሰባሰቡ ስራ ብዙም ስላልተሳካ ህወሓት የጦር ኃይሉን ከቀድሞው በተለየ ወደ ፖለቲካ ወሳኔ ሰጪነት ለማዛወር መወሰኑን አመልክተዋል።
“ሹመቱ የአገሪቱን የመከላከያ ኃይል ለማጠናከር ቢሆን መልካም ነበር። አሁን እየሆነ ያለው ግን ወታደራዊ መንግሥት በመትከል ክልሎችን በጣጥሶ በሃይል ለመቆጣጠር የሚደረግ ሩጫ ነው። ለዚህም ማረጋገጫው ሹመቱ የቀድሞውን ሳያካትት የአንድ ብሄር ታማኞች እንዲበዙበት መደረጉ ነው” የሚሉት ሌላው ምንጫችን “በቅርቡ የጄኔራል ማዕረግ የነበራቸውን መኮንኖች ቁልፍ በሆኑ ተቋማት ውስጥ በሲቪል የመንግሥት ሠራተኝነት ስም በከፍተኛ ሥልጣን ላይ (እስከ ሚኒስትር በሚደርስ) ለመመደብ ተዘጋጅቷል። ይህም የሚከናወነው በመተካካት ስም ነው” ብለዋል።
በህወሓት ዘንድ የተከሰተውን የሚዛን መዋዠቅ ፍርሃቻና የጉልበት መላላት ለማጠናከር የቀድሞ ታጋዮች መሰባሰብ መጀመራቸውም ተሰምቷል። መለስ እያሉ መሰረታዊ የህግና ህገ መንግስታዊ ጉዳዮች አንስተው ዳግም የተደራጁት የቀድሞ የህወሓት ታጋዮች ድርጅታቸውን ለመርዳት ተሰባስበዋል። ይሁን እንጂ ድርጅቱ ለሁለት በተከፈለበት ወቅት አቶ መለስን ወግነው አሁን ስልጣን ላይ ያሉትን እንደማይቀበሉ እየተሰማ ነው።
“ውህዳን” ተብለው ከህወሓት የተባረሩትን የሚደግፉ ክፍሎች ከመከላከያና ከደህንነት ባለስልጣናት ጋር ቀጥተኛ ግንኙነት ስላላቸው አንዳንድ የህወሓትና ሰርጎ ገብ የብአዴን አባላትን ማሳሰቡን የጠቆሙት ለጉዳዩ ቅርበት ያለቸው ክፍሎች፣ “ህወሓት አቶ አባይ ጸሃዬን የድርጅቱ ሊቀ መንበር ማድረግ የለበትም” የሚል አቋም እንደሚታይባቸው ጠቁመዋል። በሌላ ወገን ደግሞ አቶ አባይ ጸሃዬን የህወሓት ሊቀመንበር ለማድረግ የመለስ ታማኞች እየሰሩ መሆኑን ያመለከቱት እኒህ ክፍሎች፣ የመጀመሪያ ምርጫቸው ግን አቶ ደብረጽዮን እንደሆኑ አስረድተዋል። አቶ ደብረጽዮን ቁጥር አንድ የሚባሉ የመለስ ታማኝ፣ የክፍፍሉን ጊዜ መለስ ባሸናፊነት እንዲወጡ ከገጠር እስከ ከተማ የሰሩና ጭካኔ የሚጠይቁ ውሳኔዎች ላይ የማያቅማሙ ከፍተኛ የደህንነት ሰው መሆናቸውን ጠቅሰን በሌላ ዜና መዘገባችን ይታወሳል
በተመሳሳይ ዜና የጠቅላይ ሚኒስትር ጽ/ቤት በህግ ከሚያዘው ውጪ በደኅንነት አባላት ቁጥጥር ስር እንዲሆን መደረጉን የጎልጉል ምንጮች አስታውቀዋል። ይህ የተደረገበትን ምክንያት ሲያብራሩም “ድንገት የማፈንገጥና ከህወሓት ፍላጎትና እምነት ውጪ የሚወሰን ውሳኔ ቢኖር አፋጣኝ እርምጃ ለመውሰድ እንዲያመች ተብሎ የተደረገ ነው” ብለዋል።

ኢህአዴግ ፓርቲ ሊሆን ነው!!

ህዝባዊ ወያኔ ሓርነት ትግራይ (ህወሓት) ከመንገድ እየለቃቀመ ያቋቋማቸውን ድርጅቶች አሰባስቦ ራሱን ግንባር አድርጎ ላለፉት ሃያ አንድ ዓመታት በሥልጣን ላይ ቆየው ኢህአዴግ ከግንባርነት ወደ ኅብረብሔር ፓርቲነት የሚሸጋገርበትን ጊዜ ሊያፋጥን እንደሆነ ተሰማ። ግንባሩ ፓርቲ ሲሆን በውስጡ የተካተቱት ፓርቲዎች ይከስሙና አደረጃጀታቸው በአዲሱ ፓርቲ ጥላ ስር ይሆናል፡፡
የጎልጉል የኢህአዴግ ምንጮች እንደጠቆሙት ኢህአዴግ ወደ ኅብረብሔር ፓርቲነት እንዲሸጋገር ታስቦ የነበረው ከስድስት ዓመት በፊት ሃዋሳ ተካሂዶ በነበረው የድርጅቱ 5ኛ መደበኛ ጉባኤ ላይ ነበር። በወቅቱ የግንባሩ ወደ ኅብረ ብሄር ፓርቲነት የመሸጋገር ጥያቄ በቂ ጥናት ተደርጎበት ከሁለት ዓመት በኋላ ኦሮሚያ ጨፌ አዳራሽ በሚካሄደው ጉባኤ ላይ ይፋ እንደሚደረግ ከስምምነት ላይ ተደርሶ ነበር።
ቀደም ሲል ከጉባኤ ጉባኤ ሲተላለፍ የቆየው ኢህአዴግን ወደ ፓርቲ የማሳደግ አጀንዳ አሁን ተግባራዊ ለማድረግ የታቀደው ህወሓት በከፍተኛ የጦር ኃይልና የደኅንነት አቅም የበላይነቱን ካጠናከረ በኋላ “አገሪቱን አቅም ያላቸው ይምሯት” በሚል በከፍተኛ ደረጃ አመራሩን ለመቆጣጠር እንዲያስችለው ነው የሚል መላምት እየተሰጠ ነው። በሌላ በኩል ደግሞ ድርጅቶቹ ውህደት ከፈጠሩ የፓርቲዎቹ ንብረት ስለሚዋሃድ ይህ ሃሳብ ከህወሓት ሊመነጭ እንደማይችል ዜናውን ከሰሙ ጀምሮ የማይቀበሉት ወገኖች አሉ።
የጎልጉል ምንጮች እንደሚሉት ግን ዝርዝር ጥናቱን እጃቸው የገባ ባይሆንም ኢህአዴግን ከግንባር ወደ ኅብረብሔር ፓርቲነት የማሸጋገሩ ስራ በጥብቅ እየተሰራበት እንደሆነ እንደሚያውቁ አስረድተዋል። ስለ ህወሓት የቀድሞ ታጋዮችና በአገሪቱ ህዝብ ላይ ሱቅ በደረቴ ከፍተው የሚነግዱ ጥቃቅን መንግስታት የአገሪቱ የወደፊቱ የለውጥ ስጋቶች ስለመሆናቸው ጠቅሰው ቃለምልልስ የሰጡትን የኢህአዴግ ሰው ሙሉ ቃለመጠይቅ እዚህ ላይ ያንብቡ።

No comments:

Post a Comment