Translate

Wednesday, September 19, 2012

እስክንድር ገና ‹‹17 ዓመት›› ይቀረዋል


በተመስገን ደሳለኝ
እስክንድር ገና ‹‹17 ዓመት›› ይቀረዋልእለቱ መስከረም አንድ፣ የአዲሱ ኣመት የመጀመሪያው ቀን ነው፡፡ ጋዜጠኛና የፖለቲካ ተንታኝ እስክንድር ነጋ ከታሰረ አንድ አመት ሊሞላው ሁለት ቀን ብቻ ይቀረዋል፡፡ ባለቤቱ ጋዜጠኛ ሰርካለም ፋሲል ልትጠይቀው በአስፈሪው ቃሊቲ ማረሚያ ቤት አውዳመትን ታሳልፍ ዘንድ ግድ ሆኖባታል፤ እናም በግቢው ተገኝታ ፖሊሶቹ ይጠሩላት ዘንድ ጠየቀች፤ አንድ ልጅ እግር ፖሊስም እስክንድር ከታሰረበት ‹‹ዞን ሶስት-ስድስተኛ ቤት›› ጠርቶ ከሚወዳት ባለቤቱ ጋር አገናኘው፡፡ ጥንዶቹ ጋዜጠኞችም ከደርባባ የናፍቆት ሰላምታ በኋላ ጥቂት አወጉ፤ ሆኖም ለእስክንድር የተፈቀደው የመጠየቂያ ደቂቃዎችም አለቁና ይሰነባበቱ
ዘንድ ግድ ሆነ፤ (በነገራችን ላይ እስክንድርን እንዲጠይቁ የተፈቀደላቸው ሰዎች ባለቤቱን ጨምሮ ሶስት ብቻ ሲሆኑ ደቂቃዎቹም የተገደቡ ናቸው) በመጨረሻም እንዲህም ተባብለው ተለያዩ:-

‹‹ጊዜው እንዴት ይሮጣል? ከታሰርኩኝ ከነገ ወዲያ አንድ ኣመት ይሞላኛል፤ በጣም ይገርማል! አስታውሳለሁ የታሰርኩት ናፍቆትን ከትምህርት ቤት ሳመጣ ነው፡፡ እንግዲህ አሁን እዳው አንቺ ላይ ወድቋል፤ ጠዋት ትምህርት ቤት መውሰድ፣ ለእኔ ስንቅ ማመላለስ፣ ማታ ደግሞ ናፍቆትን ከትምህርት ቤት መመለስ፡፡ መቼስ ምን ይደረግ? ለማንኛውም መልካም በዓል ይሁንልሽ፤ ለሀገሬም መልካም ቀን እንዲመጣ እመኛለሁ››
‹‹ለአንተም መልካም በዓል ይሁንልህ፣ መልካም አዲስ አመት››
እስክንድርም ከተፈረደበት 18 ኣመት ውስጥ የጨረሰው አንድ አመቱን ነውና ቀሪውን 17 ዓመት በእስር ይጨርስ ዘንድ ወደመከራ ክፍሉ ተመለሰ፡፡ ለአስራ ሰባት ዓመት ያህል በዱር በገደል ‹‹በህዝብ ስም›› የታገለ ሀይል ለስልጣን ሲበቃ ህዝብን መልሶ 17 ዓመት ማሰሩ እየቆጠቆጠው፣ በበረሃ መስዋዕትነትን የከፈሉ ታጋዮች ደም ደመ-ከልብ ሲሆን እየተሰማው…
…ግልጽ ነው አቶ መለስ ዜናዊ በዚህ አይነት መልኩ ከስልጣናቸው በመለየታቸው አዝነናል፤ ይህ ማለት ግን በዘመናቸው የለየላቸው አምባገነን መሆናቸውን ሊቀይረው አይችልም፤ በአፋኝ አገዛዛቸውም ብዙ ንፁሀን ወንድሞቻችን ለግፍ እስር ተዳርገዋል፣ ሞተዋልም፤ ምንአልባትም ይህ አይነቱ ህመም የማይሰማቸው አድናቂዎቻቸው አሁንም የጠቅላይ ሚኒስትሩ ሀዘን አልወጣላቸው ይሆናል፡፡ እኛ ነቃፊዎቻቸው ግን ለ21 አመት በሳቸው ህገወጥ አመራር ስናዝን ነበር፤ ዛሬም ከሀዘናችን አልተላቀቅንም፤ እናም እሳቸውን የተካችሁ የአመራር አባላት ንፁሀን ወንድሞቻችንን ፍቱልን፤ መላው የኢህአዴግ አባላትም ሀዘናችሁን ላስተዛዘናችሁ ህዝብ ስትሉ ወንድሞቻችን ይፈቱ ዘንድ በመሪዎቻችሁ ላይ ጫና አድርጉ፡፡
አዎን! እስክንድር ነጋን ልቀቁልን፣ አንዱአለም አራጌን ልቀቁልን፣ በቀለ ገርባን ልቀቁልን፣ ሁሉንም የፖለቲካ እስረኞች ልቀቁልን፣ በኦነግ ስም የአሰራችሁአቸውን ብዙ ሺህ ወንድሞቻችንን ልቀቁልን፣ በፀረ-መጅሊስ እንቅስቃሴ ላይ ንቁ ተሳትፎ የነበራቸውን ሙስሊም ወንድሞቻችንን ልቀቁልን…

No comments:

Post a Comment