Translate

Wednesday, July 2, 2014

የየመን ኩባንያ የትምባሆ ድርጅት ከፍተኛ የአክሲዮን ባለድርሻ ሆነ

[ሽያጩ የተካሄደው በጠቅላይ ሚ/ር ጽ/ቤት ቀጥተኛ ትዕዛዝ ነው]

national tobacco e


የፕራይቬታይዜይሽንና የመንግሥት የልማት ድርጅቶች ተቆጣጣሪ ኤጀንሲ ውሳኔ መስጠት በተቸገረበት የብሔራዊ ትምባሆ ድርጅት ሽያጭ ጉዳይ ላይ፣ የጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት ባለፈው ሳምንት መጨረሻ ውሳኔ ሰጠ፡፡
የጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት የየመኑ ኩባንያ ሼባ ኢንቨስትመንት የብሔራዊ ትምባሆ ድርጅት 60 በመቶ ባለቤት እንዲሆን ወስኗል፡፡

የ70 ዓመት ዕድሜ ባለቤት የሆነው ብሔራዊ ትምባሆ ድርጅት 22 በመቶ የሚሆነው አክሲዮን ከ1991 ዓ.ም. ጀምሮ በየመኑ ሼባ ኢንቨስትመንት ሲያዝ፣ ቀሪው 78 በመቶ አክሲዮን ደግሞ በመንግሥት የተያዘ ነበር፡፡
የጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት በወሰነው አዲስ ውሳኔ ሼባ ኢንቨስትመንት ተጨማሪ 38 በመቶ አክሲዮን ከመንግሥት ላይ እንዲገዛ የሚፈቅድ በመሆኑ፣ ሼባ ኢንቨስትመንት በብሔራዊ ትምባሆ ድርጅት አክሲዮን ላይ አንበሳውን ድርሻ 60 በመቶ ሲይዝ፣ መንግሥት ደግሞ 40 በመቶ ድርሻ ይዞ ይቀጥላል፡፡
ሼባ ኢንቨስትመንት እንዲገዛ ለተፈቀደለት 38 በመቶ አክሲዮን 1.3 ቢሊዮን ብር መክፈል እንደሚጠበቅበት የፕራይቬታይዜሽንና የመንግሥት የልማት ድርጅቶች ተቆጣጣሪ ኤጀንሲ ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ኃላፊ አቶ ወንዳፍራሽ አሰፋ ለሪፖርተር ገልጸው፣ ኩባንያው ይህንኑ ገንዘብ እንደከፈለ የስም ዝውውር እንደሚደረግ አስታውቀዋል፡፡
ብዙም ባልተመለመደ ሁኔታ የብሔራዊ ትምባሆ ድርጅት አክሲዮን ሽያጭ ላይ የፕራይቬታይዜሽን ኤጀንሲ የሥራ አመራር ቦርድ ውሳኔ ለመስጠት የተቸገረው በሁለት ምክንያቶች መሆኑን ምንጮች ይገልጻሉ፡፡ የመጀመርያው ድርጅቱ በሲጋራ ላይ ብቸኛ መብት (ሞኖፖሊ ራይት) ያለው በመሆኑ፣ ይህ የብቸኝነት መብት የየመኑ ኩባንያ ከፍተኛ ድርሻ በሚይዝበት ወቅት ምን መሆን አለበት? የሚለው ጉዳይ ላይ አቋም መያዝ ባለመቻሉ ነው፡፡ ሁለተኛው ጉዳይ ደግሞ ትምባሆ ድርጅት በተለያዩ የታክስ ዓይነቶች በየዓመቱ ከ1.3 ቢሊዮን ብር በላይ ለመንግሥት የሚያስገባ ከመሆኑም በተጨማሪ፣ ትርፋማ ከሆኑ የመንግሥት የልማት ድርጅቶች መካከል አንዱ በመሆኑ፣ ለመንግሥት ግምጃ ቤት ከፍተኛ ገንዘብ ፈሰስ የሚያደርግ ነው የሚለው ጉዳይ ቦርዱ በአክሲዮኑ ሽያጭ ላይ ለመወሰን እንዲቸገር ማድረጉ ነው፡፡
በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ማዕረግ የሲቪል ሰርቪስና የመልካም አስተዳደር ክላስተር አስተባባሪና የሲቪል ሰርቪስ ሚኒስትር በሆኑት ወ/ሮ አስቴር ማሞ የሚመራው የፕራይቬታይዜሽን ቦርድ በእነዚህ ጉዳዮች ላይ የመንግሥትን አቅጣጫ በግልጽ ባለመረዳቱ፣ የጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት አቅጣጫ እንዲሰጠው መጠየቁን መዘገባችን ይታወሳል፡፡ ነገር ግን የጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት ሁለቱም ጉዳዮች እንዳሉ ሆነው የአክሲዮን ሽያጩ እንዲከናወን በማዘዙ፣ ባለፈው ሳምንት ሐሙስ የተሰበሰበው የፕራይቬይታዜሽን ቦርድ የየመኑ ኩባንያ ከፍተኛ ባለድርሻ መሆን የሚያስችለውን ውሳኔ እንዲወስን ማድረጉን ምንጮች ገልጸዋል፡፡
ትምባሆ ድርጅት በተለያዩ አካባቢዎች የትምባሆ ልማት የሚያካሂድባቸው የእርሻ መሬቶች ባለቤት ነው፡፡ የድርጅቱ መሥርያ ቤት ከሜክሲኮ አደባባይ ወደ ሳር ቤት በሚወስደው መንገድ ከአፍሪካ ኅብረት ፊት ለፊት የሚገኝ ሲሆን፣ ለፀጥታ አመቺ አይደለም በሚል መሥርያ ቤቱ ከዚህ ቦታ ተነስቶ ወደ አቃቂ አካባቢ እንዲዛወር ተወስኗል፡፡ ምንጮቹ እንደገለጹት ድርጅቱ ቃሊቲ አካባቢ ከአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በተረከበው ቦታ ላይ የሚያካሂደውን ግንባታ ሲያጠናቅቅ፣ ለበርካታ ዓመታት ከነበረበት ቦታ ይነሳል ተብሏል፡፡  (ምንጭ፡ ሪፖርተር፤ ሰኔ22፤2006/June 29,2014 – ተመሳሳይ ዜና Capital በሰኔ16፣2006/June 23,2014 ዕትሙ ዘግቧል፡፡ ፎቶውንም ያገኘነው ከዚያው ነው)

No comments:

Post a Comment