Translate

Monday, July 14, 2014

የሕወኀትን ዕቅዶች እንዴት ማክሸፍ ይቻላል?

ለሕወኀት ቀኑ በፍጥነት እየጨለመ መሆኑ ግልጽ ቢሆንም እስካሁንም ምንም ዓይነት የማስተካከያ ርምጃም ሆነ የመለሳለስ አቋም ከማሳየት ይልቅ በተለመደው እብሪቱ የመቀጠሉ ምክንያት ሊሠራ የሚችል ዕቅድ አለኝ ብሎ ከማመን ነው። ከሰሞኑ አቶ አንዳርጋቸው ጽጌን ከየመን አግቶ እስከመውሰድ ድረስ የደፈረበት ድርጊት አገዛዙ የደረሰበትን የፍርኃት ደረጃ በግልጽ የሚያሳይ ቢሆንም ‘መውጫ ቀዳዳ አለኝ’ ብሎ የሚያስበው አስተሳሰብ ሥር የሰደደ መሆኑን የሚያመለክትም ጭምር ነው። ‘እነዚህን ዕቅዶች ብዙ ሠርቸባቸዋለሁ፣ ዝግጅቶቸን ወደማጠናቀቅ ደርሻለሁ፣ ከኢትዮጵያ ሕዝብ ጋር እየኖሩ ከመሥጋት እጅግ የተሻለ ዕቅድ ነው’ ብሎ ያምናል። ይህ ለሌሎችም እንዲተባበሩ ለሚጠየቁት/ ለሚገደዱት ቢያንስ ለሁለቱ ክልሎች (የቤንሻንጉል ጉሙዝና ጋምቤላ) እንደምክንያት የሚቀርብ ሐሳብ እንደሚሆን መገመት ይቻላል። ይሁን እንጂ ዕቅዱን ለማክሸፍ የሚቻልባቸው አያሌ መንገዶች አሉ። የሚከተሉት ጥቂቶቹ ናቸው። ሌሎች ቢጨምሩባቸውና ቢያዳብሯቸው ጥቅሙ ለሀገርና ለወገን ነው።

የሕወኀትን ዕቅዶች እንዴት ማክሸፍ ይቻላል?
የሕወኀት ዕቅድ በአብዛኛው እስካሁን ተሰውሮ የቆየው በመጀመሪያ በመሠሪነቱ ሊሆን ይችላል ተብሎ ሊታሰብ የማይችል ዕቅድ በመሆኑ ነው። በሁለተኛ ደረጃ ይህን ከአገር ጀምሮ በቅርብ ያሉትን ጎረቤት አገራትና በሩቅ ያሉትን ኃያላን አገራት ሳይቀር የሚጎዳ እብደት የተቀላቀለበት ዕቅድ አገዛዙ ደፍሮ ይወጥናል ብሎ ለማሰብ አስቸጋሪ ስለሆነ ነው። በሦስተኛ ደረጃ የሕወኀትን ብቃትና ተክለ ሰውነት የማይመጥን ከአቅሙ በላይ የተለጠጠ ዕቅድ ስለሆነ ነው። በዚህ ምክንያት አብዛኛው የዚህ መሠሪ ዕቅድ ማርከሻ መፍትሔ የሚገኘው በዚሁ ድክመት ውስጥ ነው። መፍትሔዎች ቀጥለው ተዘርዝረዋል፦
1. የሕወኀት ቁልፍ ባለሥልጣናት
የመጀመሪያው መፍትሔ የሚገኘው በአገዛዙ ቁልፍ ባለሥልጣናት እጅ ነው። ለአገዛዙ ቁልፍ ባለሥልጣናት ይህን መጠቆም ከመቸውም ይልቅ ዛሬ ውጤት የሌለው መስሎ እየታዬ ነው። በተከታዮቻቸው በኩል ግን የተዘረጋው እጅ ፍሬ ማፍራቱን አይተናል። ዛሬም እየተመለከትን ነው። ስለዚህ ይህን ማሳሰብ አስቸጋሪ የሆነበት ጊዜ ላይ ብንገኝም እውነቱንና መልካም የሆነውን መጠቆም ዛሬም አስፈላጊ ነው።
እስከዛሬ ድረስ ከልክ አልፎ የጦዘውን የዘር ፖለቲካ፣ በምናባቸው የሳሉትን የመጠራጠርና የፍርኃት መንፈስ አስወግደው፣ የተፈጸሙትን ጥፋቶች አምነውና አሁንም ሊፈጽሙት እየተዘጋጁ ካሉበት ከተጀመረ በኋላ ወደነበረበት መመለስ የማይችል፣ ለሕዝብ ለአገር እና ለምሥራቅ አፍሪካ ትልቅ አደጋ ከሚያስከትል ድርጊት ተቆጥበው ብሔራዊ እርቅ የሚከናውንበትን መድረክ ቢያመቻቹ የኢትዮጵያ ሕዝብ ይቅር እንደሚልና ከፍርኀት ወጥተው በአገራቸው እነርሱም ሆነ ልጆቻቸውና ቤተሰቦቻቸው በሰላም መኖር እንደሚችሉ ሊጠራጠሩ አይገባም። ይህን ለማለት የሚያስችሉ በቂ ምክንያቶች ስላሉ ነው። የአገዛዙ ቁልፍ ባለሥልጣናት ከነአቶ ገብሩ አሥራት፣ አቶ ስዬ አብርሃ፣ አቶ አስገደ ገብረሥላሴ ወዘተ የሚማሩት ነገር አለ። እነዚህ በስም የተጠቀሱ የቀድሞ የሕወኀት ታላላቅ ባለሥልጣናት ከሕወኀት ጋራ ለረጅም ጊዜ የቆዩ፣ በአብዛኛው የድርጅቱ ድርጊቶች የተሳተፉና በጠፉ ጥፋቶችም እኩል ተጠያቂዎች ናቸው። ከድርጅቱ ባለመስማማት ከተለዩ በኋላ አብዛኞቹ በአገር ውስጥ ከሕዝቡ ጋራ በሰላም መኖራቸውን እንደቀጠሉ ይገኛሉ። አንዳንዶቹ እነርሱ ጥፋት ላሏቸው ይቅርታ ጠይቀዋል። አንዳንዶች እዚያም አልደረሱም። አንዳንዶቹ በአመለካከታቸው ሕዝቡን መስለዋል። አንዳንዶቹ ደግሞ ገና ሕዝቡን አልመሰሉም። እንዲህም ሆኖ ክፉ ሥራቸውን ትተው ከሕወኀት መለየታቸውን ብቻ አይቶ ሕዝቡ ሁሉንም ይቅር ብሏቸዋል። ከሕዝቡ በኩል አንዳችም የደረሰባቸው ችግር እስካሁን አልተመዘገበም። አብዛኞቹ የተቃዋሚ ድርጅቶች መሪዎችና አባላት እንደመሆናቸው ሕወኀት ከጥቃት ይጠብቃቸዋል ብሎ ማሰብ አስቸጋሪ ነው። በውጭ አገር የሚኖረው ኢትዮጵያዊ እንኳን በነዚህ የቀድሞ የሕወኀት ቁልፍ ባለሥልጣናት ላይ ያለው ጥያቄ ይቅርታ ያልጠየቁት እንዲጠይቁ ከመገፋፋት ያለፈ አይደለም። በእውነቱ የኢትዮጵያ ሕዝብ የሰው አእምሮ ከሚመረምረው በላይ እጅግ አስተዋይና ይቅርታ አድራጊ ሕዝብ ስለመሆኑ ከዚህ የበለጠ ምስክር የለም።
በአንድ ወቅት አቶ ገብሩ አሥራት አሁን ስለሚሰማው ነፃነት እንዲህ በማለት ነበር የተናገረው፦
“ሕሊናዬን ሸጬ በአንዲት ብጣሽ ወረቀት ይቅርታ ብጠይቅ ኖሮ ከዓባይ ፀሐዬና ሀሰን ሽፋ የበለጠ ሥልጣንና ገንዘብ ላገኝ እችል ነበር፡፡ ‘ይቅርታ በልና ወደ ነበርክበት እንመልስህ’ ብለው ብዙ ሽማግሌዎች ልከውብኛል፡፡ በመኪና መሄድ መጠቀም ብፈልግ ኖሮ ይህ ለኔ በጣም ቀላል ነበር። ነገር ግን ለኔ ይህ አያስፈልገኝም ለእኔ ከሕንፃና ገንዘብ ይልቅ ነፃነቴ ነው የሚበልጥብኝ። አሁን እንደ ማንኛውም ኢትዮጵያዊ ዜጋ ያለምንም ሥጋት በታከሲና፣ በአውቶብስ እሄዳለሁ በማንኛውም ሆቴል አድራለሁ የሕዝብ መገናኛ ቦታዎች ሁሉ እገኛለሁ። በዚህም እጅግ በጣም ደስተኛ ነኝ”
አቶ ገብሩ አሥራት በዚህ ንግግሩ በሥልጣን ላይ እያለ ይሰማው የነበረውን የነፃነትና የሰላም ማጣት ስሜት በተዘዋዋሪ ገልጾታል። ያ ብቻም አይደለም። አሁን የሚሰማውን ሰላምና ነፃነት በሥልጣን፣ በገንዘብ፣ በሀብትና በምቾት እስከማይቀይረው ድረስ ደስተኛ ነው። እውነተኛ የነፃነት ስሜት ይህን ይመስላል። ለሌሎችም ይህ ነፃነት፣ ይህ ሰላምና ደስታ ዛሬም በእጃችው እንደሆነ ሊጠራጠሩ አይገባም።
2. የኢትዮጵያ ሕዝብ
የኢትዮጵያ ሕዝብ በአንድነት መቆም ለዚህ ዕቅድ መክሸፍ ዋና መፍትሔ መሆኑ የሚያሻማ አይደለም። ይልቁንም ለአማራውና ለኦሮሞው መብትና ነፃነት ቆመናል የሚሉ ግለሰቦችና ድርጅቶች ሁሉ ከጊዜያዊ ጥቅምና ራዕይ ከማጣት ተመልሰው እርስ በርስ የሚያደርጉትን የጭቃ ውርወራ በማቆም በወንድማማችነትና በእህትማማችነት በአንድ ላይ በመቆም ሕወኀትን መቃወምና ይህ አገሪቱን ወደ ደም ማፋሰስ የሚወስድና አገር የሚበትን ዕቅድ እንዳይሳካ ከመቸውም ጊዜ ይልቅ በመተባበር መሥራት ይጠበቅባቸዋል።
በውጭ ሆነው እሳቱ አይነካንም በማለትና ይህ የእርስ በርስ ግጭትና የኢትዮጵያ መበታተን “ለእኔ ወይም ለጎሳዬ ይጠቅማል” ከሚል ስሌት የሚንቀሳቀሱ የመገንጠልን ሐሳብ የሚያቀነቅኑ አክራሪዎች እንደሚኖሩ ይታመናል። በሀይማኖቱም እንዲሁ። ሆኖም ከኢትዮጵያ ሕዝብ ጉዳት ውስጥ ‘የእኔ ጎሳ ወይም ሀይማኖት ይጠቀማል’ በማለት ከሕወኀት ጋራ በመቆም በገሀድ ማንነታቸውን የሚያጋልጡ ወገኖችን የኢትዮጵያ ሕዝብ በሚገባ እንዲያውቃቸው እድል ስለሚያገኝ ጸረ-ሕወኀት ትግሉን በአንድ ማዕከል ለማሰባሰብ ትልቅ ጥቅም ይኖረዋል።
3. የትግራይ ሕዝብ
የትግራይ ሕዝብ ይህን ዕኩይ ዕቅድ ለማክሸፍ ግንባር ቀደም ሚና ይጫዎታል። የሕወኀት ቁልፍ ባለሥልጣናት ይህን ዕቅድ የወጠኑት ለራሳቸው፣ ለቤተሰቦቻቸውና እጅግ ቢረዝም ለቅርብ ዘመዶቻቸው ከማሰብና ‘የትግራይ ሕዝብ በታሪክ ሲረግመኝ ከሚኖር ለይስሙላም ቢሆን ይህን ሞክሬ ነበር’ ለማለት ብቻ እንጂ ለትግራይ ሕዝብ አስበው አይደለም። ለሕዝቡ የሚያስብ አገዛዝ ለሰው ልጅ ከምንም በላይ አስፈላጊ የሆኑትን ነፃነት፣ መብትና ሰው የመሆን ክብር ከሚያስተዳድረው ሕዝብ ላይ አይገፍም። የአገዛዙ ባለሥልጣናት ትግሉ ሲበረታ ሀብት ወዳሸሹባቸውና ንብረት ወዳዘጋጁባቸው አገሮች እንደሚሸሹ የትግራይ ሕዝብ ሊጠራጠር አይገባም። ከዚህም በላይ በሕወኀት ዕቅድ መተባበር የትግራይ ሕዝብ እስካሁን በሕወኀት አገዛዝ ሥር የደረሰበት ግፍ፣ አፈናና ጭቆና ለወደፊቱ ተባብሶ እንዲቀጥል መፍቀድ ይሆናል። ስለዚህ በመጀመሪያ ይህን ዕቅድ መደገፍ ከራሱ ከትግራይ ሕዝብ ደህንነትና ዘላቂ ኅልውና ጋራ በቀጥታ የተቆራኘ መሆኑን ማስተዋል ያስፈልጋል።
ሁለተኛው ለትግራይ ሕዝብ በቤንሻንጉል ጉሙዝና በጋምቤላ በኩል የሚቀርብለት መደለያ ታሪኩ በመጽሐፍ ቅዱስ እንደተጠቀሰው እንደሎጥ ምድር ፍጻሜው አያምርም። የትግራይ ሕዝብ ሌሎችን ጎሳዎች በመንቀልና በማያቋርጥ ተከታታይ የዘር ማጥፋት ዘመቻ በመተባበር አገኘዋለሁ የሚለው ጥቅም በየትኛውም መንገድ ተገቢም ዘላቂም አይደለም። ሕወኀት የራሱን ባለሥልጣናት ተገዢና ታማኝ ለማድረግ የሙስና ወንጀል እንዲፈጽሙ እንደሚያበረታታቸው በተደጋጋሚ ተዘግቧል። በተመሳሳይ በተለያዩ የኢትዮጵያ ክልሎች ክፉ የሆነው ነገር ሁሉ በትግራይ ተወላጆች እንዲፈጸምና የተለያየ ጥቅማ ጥቅምም እንዲያገኙ የሚያደርገው ሕወኀት ለትግራይ ተወላጆች አስቦ ሳይሆን ቀሪው የኢትዮጵያ ሕዝብ ይህ የደረሰብኝ በትግራይ ተወላጆች ነው በማለት ቅሬታ እንዲኖረውና ይህም መልሶ የትግራይ ተወላጆችን የማያቋርጥ ሥጋት ውስጥ በመክተት ለሕወኀት ታማኝነታቸውን እንዲያረጋግጥለት መሆኑን የትግራይ ተወላጆች በአንክሮ ሊያብሰለስሉት ይገባል።
ሦስተኛው የትግራይ ሕዝብ ለሁለተኛ ጊዜ በኢትዮጵያ ሕዝብና በስሙ በሚነግዱ ጨቋኝ ገዢዎች መካከል እንዲመርጥ ጥያቄ የቀረበለት መሆኑ ነው። ማንን መምረጥ እንዳለበት ለትግራይ ሕዝብ ነጋሪ አያስፈልገውም። የዚህን መልስ በመጪው ምርጫ “አረና”ን የመሰሉ በአገር ሉዓላዊነት የሚያምኑ ድርጅቶችን ነቅሎ ከቤቱ በመውጣትና በመምረጥ ማሳየት ይጠበቅበታል።
አሁን ያለው ተጨባጭ ሁኔታ የሕወኀት ዘመን ረጅም እንደሆነ አያመለክትም። እስከመጪው ምርጫ ድረስ ብዙ ያልተጠበቀ ነገር ሊሆን የሚችልበት በቂ ጊዜ አለ። በትናንትና በዛሬ መካከል እንኳን ብዙ ልዩነት እያየን ነው። ሆኖም ያ መሆን ካልቻለ ደግሞ መጪውን ምርጫ ይልቁንም በትግራይ የሚደረገውን ምርጫ ችላ እንዳንል የሚያደርገን መጪው ምርጫ የትግራይ ሕዝብ በኢትዮጵያዊነቱ ላይ ያለውን አቋም እንድንረዳ እንደ አንድ መመዘኛ የሚያገለግልና ውጤቱ የታሪክን አቅጣጫ ሊቀይር የሚችልበት አቅም ስላለው ነው። በትግራይ ሕዝብ ስም የሚንቀሳቀሱ ግለሰቦች፣ ‘አረና’ እና “ድምሒት”ን የመሰሉ ተቃዋሚዎች በኢትዮጵያ ሉዓላዊነት ላይ ከመቸውም ይልቅ የማይናወጥ አቋም መያዝ ይጠበቅባቸዋል። መጪውን ምርጫ ለማሸነፍ የሚጠይቀውን አቅም ከሌሎች ድርጅቶችና በውጭ ከሚኖረው ኢትዮጵያዊ ጋራ ተባብሮ በመገንባትና መስዋዕትነት በመክፈል አሸናፊነታቸውን መረጋገጥ ይጠበቅባቸዋል። ከዚህ ባልተናነሰ የኢትዮጵያ ሕዝብ፣ ተቃዋሚ ድርጅቶች፣ አክቲቪስቶች፣ መገናኛ ብዙኃንና ምሁራን ከመቸውም ጊዜ በላይ የትግራይን ሕዝብ ከአገዛዙ ለይቶ በማየት ለትግራይ ሕዝብ ፍጹም የወንድማማችነት እጃቸውን እንዲዘረጉና ለ“አረና” እና ለ“ድምሒት” ያላቸውን ድጋፍ እንዲያጠናክሩ ይጠበቅባቸዋል።
4. የቤንሻንጉል ጉሙዝና የጋምቤላ ክልሎች ሕዝብ፣ ሹማምንቱና የየፓርቲዎቹ ካድሬዎች
የቤንሻንጉል ጉሙዝና የጋምቤላ ክልሎች ሕዝብ፣ ሹማምንቱና የየፓርቲዎቹ ካድሬዎች “የራስ አስተዳደር” በሚል ሰበብ ከኢትዮጵያ ስለ መለየት ዛሬ የሚሰብካቸው ሕወኀት ስለነርሱ ነፃነትና እድገት በማሰብ ሳይሆን የክልላቸው ለም መሬትና የተፈጥሮ ሀብት ሕወኀት አገር ለመመሥረት ይጎድለኛል ብሎ የሚያስበውን በሟሟላት ወሳኝ ሚና ይኖረዋል ከሚል ብቻ እንደሆነ በሚገባ እንዲረዱት ያስፈልጋል።
ሕወኀት እስካሁን ያደረገውና አሁንም እያደረገ ያለው ማንነቱን ይገልጠዋል። ሕወኀት ለጋምቤላና ለቤንሻንጉል ክልል ሕዝብ እድገት የሚፈልግ ቢሆን ኖሮ ኗሪዎቹን እያፈናቀለና ከይዞታቸው እየነቀለ በመሬቱ ላይ የራሱን ደጋፊዎች ባላሰፈረ ነበር። ለክልሉ ሕዝብ እድገት የሚመኝ ቢሆን ኖሮ ከክልሉ ዋና ዋና ጎሳዎች መካከል ዋና መተዳደሪያው እርሻ በሆነው የአኝዋክ ሕዝብ ላይ የዘር ማጽዳት ዘመቻ ባላካሄደ ነበር። በአኝዋክ ላይ የተፈጸመው ለዕቅዱ መፈጸም መንገድ ጠራጊ እርምጃ የነበረ መሆኑ ከመቸውም ይልቅ አሁን ግልጽ ከመሆኑም በላይ ሕወኀት በእነዚህ ክልሎች ሕዝብ ላይ ወደፊት ለማድረግ ያሰበውን በማያሻማ መንገድ አመልካችም ጭምር ነው። ክልሎቹን በአጭርና በረጅም ጊዜ ዕቅድ የራሱ አድርጎ ለመጠቅለል የወሰነ እንደመሆኑ ለዚህ እንቅፋት ይሆኑኛል ያላቸውን የክልሉን ኗሪዎች በቡድንና በግል ግልጽና ስውር በሆኑ ዘዴዎች ለጉልበት ሥራ የሚያገለግሉትን ብቻ አስቀርቶ ሌሎችን ቀስ በቀስ ያስወግዳል። በወልቃይት ሕዝብ ላይ የተፈጸመው ለሁሉም ትምህርት ለመሆን የሚበቃ ነው። ለሁለቱ ክልሎች ሕዝብ በ“ራስ አስተዳደር” ሰበብ ተጠቅልሎ የሚቀርብላቸው በመርዝ የተለወሰ ምርጫ ‘ሌላ መውጫ የለኝም’ ብሎ በማሰብ ለራሱም የማያዛልቀውን ዕቅድ ወጥኖ ትግሉ ሲጠጥር ለመሸሽ በተዘጋጀው ሕወኀት እና የትግራይን ሕዝብ ጨምሮ በቀሪው የኢትዮጵያ ሕዝብ መካከል መሆኑን መረዳት ያስፈልጋል። ለኢትዮጵያ ጥቅም ያልሠራው ሕወኀት ለቤንሻንጉል ጉሙዝና ለጋምቤላ ክልሎች ሕዝብ ጥቅም ሊሠራ አይችልም። የወልቃይትን ወንዶች ገድሎ መሬታቸውን ከወሰደ በኋላ ሴቶቻቸውን ከትግራይ ተወላጆች ልጆችን እንዲወልዱ አድርጎ ዘራቸውን በማጥፋት የቀሩትን በሁመራ ለራሱ የቀን ሠራተኛ ያደረገው ሕወኀት ለነርሱ የተለየ ሊሆን አይችልም። ስለዚህ የቤንሻንጉል ጉሙዝና የጋምቤላ ክልሎች ሕዝብ፣ ሹማምንቱና የየፓርቲዎቹ ካድሬዎች ሕወኀት ለጋምቤላና ቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል በማሰብ ይህን ዕቅድ እንዳልወጠነ ሳይዘገይ መረዳትና ይህን ዕኩይ ዕቅድ ተፈጻሚ እንዳይሆን ከውስጥና ከውጭ በግልጽና በኅቡዕ ታግለው ማፍረስ የዘላቂ ኅልውናቸው አስኳል ነው።
5. የሱዳን መንግሥታት
ሁለቱም የሱዳን መንግሥታትና ሕዝባቸው ይህ የምሥራቅ አፍሪካን ቀጠና በጠቅላላ ወደ ደም መፋሰስ እንዲያመራ የሚያደርግ መሠሪ ዕቅድ ተግባራዊ እንዲሆን መተባበሩን ትተው ለዘላቂ መረጋጋትና ሰላም ከኢትዮጵያ ሕዝብ ጎን እንዲቆሙ የዕቅዱን መዘዝ በግልጽ በማስረዳት ከፍተኛ የሆነ የዲፕሎማሲ ግፊት ከሁሉም ወገን የሚጠበቅ ነው። ራሱ በፈጠረው ፍርኃትና ጥርጣሬ ምክንያት በኢትዮጵያ ሕዝብ ላይ ይህን ያደረገና ለማድረግ የተዘጋጀ ሕወኀት ማንኛውንም ጠንካራ መንግሥት በአካባቢው ማየት ይፈልጋል ብሎ ማሰብ ትልቅ ስሕተት ነው። ሁለቱ ሱዳኖች ሲለያዩ ደጋፊም ተቃዋሚም ሳይሆን የታየበት ምክንያት ቀጥሎ ከሁለቱ አገሮች ጋራ ስለሚመሠርተው ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት በማሰብ ብቻ ሳይሆን የሁለቱ ሱዳኖች መለያየት ሱዳንን እንደሚያዳክማትና በመጀመሪያ ሕወኀት የሚያቀርብላትን ፕሮፖዛል ከመቀበል ጀምሮ ለዘለቄታው ሱዳንን ለማዳከም ከሚወጥነው ወጥመድ ውስጥ ሁለቱም ሱዳኖች ሰተት ብለው እንዲገቡለት እንደሚረዳው ስለሚገነዘብ ነው። ለዚህም ነው ለኢትዮጵያ ያልሆነ ሕወኀት ለሱዳኖች የማይተኛ መሆኑንና ለዘላቂ ወዳጅነት ከአንድ መሠሪ ቡድን ይልቅ የኢትዮጵያ ሕዝብ አስተማማኝ እንደሆነ ደጋግሞ ማስረዳት ተገቢም አስፈላጊ የሚሆነው።
6. የኤርትራ መንግሥትና ሕዝብ
የኤርትራ መንግሥትና ሕዝብ ይህን ዕቅድ ለማክሸፍ ትልቅ ሚና አላቸው። ሕወኀት የተረጋጋችና ጠንካራ ኤርትራ ባለችበት ይህን ዕቅድ ሊያሳካ እንደማይችልና ለጊዜው ማሳካት ቢችል እንኳን ዕቅዱ እድሜ እንደማይኖረው ያውቃል። ለዚህ ዕቅድ መሳካት ኢትዮጵያን ወደ እርስ በርስ ግጭት መውሰድና መበተን አስፈላጊ እንደሆነው ሁሉ ኤርትራን መናጥ፣ ግጭቱ የሚፈጥረው ግርግር ካመቸው አሰብን መጠቅለልና በኤርትራ የራሱን አሻንጉሊት መንግሥት መመሥረት የዕቅዱ አካል የመሆኑ እድል ሰፊ ነው። ስለዚህ የኤርትራ ሕዝብና መንግሥት ከኢትዮጵያ ሕዝብና ድርጅቶች ጋራ እጅ ለእጅ ተያይዘው ሕወኀት አንዳቸውንም እቅዶቹን ለማስፈጸም ከመንቀሳቀሱ በፊት ዕቅዱን በማፍረስ ሊመጣ ያለውን አደጋ የማርከስ አቅም ይኖራቸዋል።
የኤርትራ መንግሥት በሱዳን ላይ ሊያደርገው የሚችለው የዲፕሎማሲ ጫና ሌላው ትልቅ ውጤት ሊመዘገብበት የሚችል ተግባር መሆኑን ማስተዋል ያስፈልጋል። ከዚሁ ጋራ በተያያዘ በኢትዮጵያ ሉዓላዊነት ጉዳይ የማያሻማ አቋም እያላቸው ከኤርትራ መንግሥትና ሕዝብ ጋራ የሚደረገውን ትብብር የሚቃወሙ ኢትዮጵያውያን የኤርትራ መንግሥትና ሕዝብ ሊያበረክቱ የሚችሉትን አስተዋጽኦ በመንገዘብ አቋማቸውን እንደገና እንዲገመግሙ ያስፈልጋል።
በኤርትራ መንግሥትና በኢትዮጵያ ድርጅቶችና ሕዝብ መካከል በጠንካራ መተማመን ላይ የተመሠረተ ግንኙነት እንዲፈጠር ወደኤርትራ እየተጓዘ የነበረው የአቶ አንዳርጋቸው ጽጌ ታፍኖ ወደኢትዮጵያ መወሰድ ትልቅ እድል ፈጥሯል። እስካሁን በኤርትራ መንግሥት በኩል በየመን ላይ የተሞከረው እንደተጠበቀ ሆኖ በየመንም ሆነ በኢትዮጵያ በኩል ውጤት እስከሚያስገኝ ጫናው ተጠናክሮ መቀጠሉ የሚጠበቅ ነው። በዚህ ወርቃማ ጊዜ (Opportune time) ሁሉም የሚጠብቀውን ውጤት ማግኘት ከተቻለ የኤርትራ መንግሥትንና የኢትዮጵያዊ ድርጅቶችን አቅም በደጋፊም በተቃዋሚም ያስመሰክራል፣ ግንኙነቱንና ትግሉንም በታሪክ ሲታወስ ወደሚኖር ታላቅ እመርታ ያሸጋግረዋል።
7. በውጭ የሚኖረው ኢትዮጵያዊ
በውጭ የሚኖረው ኢትዮጵያዊና ሁሉም የፓለቲካ ድርጅቶች በጠቅላላ አሁን ያለንበት ጊዜ አገርን የማዳን ስለሆነ ማንኛውንም ምክንያት አስወግደው ወይም ምክንያታቸውን ለሌላ ጊዜ አዘግይተው በጋራ በመቀመጥ በአንድ እዝ የሚተዳደር ከሁሉም የተውጣጣ አስተባባሪ ግብረ ኃይል፣ ከሁሉም የተውጣጣ የጦር ኃይል እና የሽግግር ጊዜ አስተዳደርና ለነዚህና ሊመጣ ላለው ሁኔታ በአስቸኳይ በቂ መልስ ለመስጠት የሚያስችል የእውቀት፣ የገንዘብና የቁሳቁስ አቅም ለመገንባት የሚሠራ ራሱን የቻለ ተቋም (Foundation) በማቋቋም ለመጪው ጊዜ ከመቸውም ጊዜ በላይ ተዘጋጅተው መጠበቅና እነዚህ ዕቅዶች እንዳይሳኩ እንደ አንድ ቃል ተናጋሪና አድራጊ ሆነው መሥራት ይጠበቅባቸዋል።
በውጭ የሚኖረው ኢትዮጵያዊ ቁጥር በሚሊዮን የሚቆጠርና የአንድን ትንሽ አገር ሕዝብ ቁጥር የሚስተካከል ሆኖ እያለ በአንድ ግብረ ኃይል የሚመራ ጠንካራ አሠራርና ተጨማሪ ፓርቲዎችን ሳይሆን አቅም ያላቸው ተቋማትን በውጭ ለማቋቋም ያለመቻላችን እስካሁን ጎድቶናል። እሥራኤልን ከጠፋችበትና ሕዝቧም በየዓለማቱ ተበትኖ ከነበረበት ሰብስበው አገር መመሥረት እንደቻሉት እንደነ ዴቪድ ቤንጉሪዮን ዓይነት ሥነልቡና ይዘን እነርሱ እስራኤልን ከመመሥረታቸው በፊት እንዳደረጉት ጠንካራ ተቋማትን በውጭ ማቋቋም ዛሬ ነገ ሳይባል ሊከናወን የሚገባው ነው። እነርሱ ያደረጉትን እኛም ማድረግ የማንችልበት ምክንያት የለም። እስካሁን ካደረግነው ጥረት የማይበልጥ ከመሆኑም በላይ የየድርጅቶቹን መሪዎች ፈቃደኝነት የሚጠይቅ ነው። ጠንካራ ውጥኖች በየድርጅቶቹ ይገኛሉ። ኢሳት አንድ ጥሩ ምሳሌ ነው። ነገር ግን እስካሁን በተናጠል የሆነው በአንድ ግብረኃይል ሥር መደራጀት ይኖርበታል። የሰው ኃይል፣ የገንዘብ፣ የቁሳቁስና የእውቀት (ቴክኖሎጂን ይጨምራል) አቅምን በከፍተኛ ደረጃ ማሳደግ እጅግ በጣም አስፈላጊ ነው። ይህን ለማሳካት በመላው ዓለም የሚገኘውን ኢትዮጵያዊ ከጫፍ ጫፍ ከፖለቲካ በላይ በሆነ አገርን የማዳን ዓላማ ጥላ ሥር ማሰባሰብ ያስፈልጋል።
እንዲህ ዓይነት በራሱ የሚተማመን አንድ ግብረኃይል፣ የአገር ውስጥ ድርጅቶችን ታሳቢ ያደረገ የሽግግር አስተዳደር፣ ከሁሉም የተውጣጣ የጦር ሠራዊትና ለችግሮቻችን አጥጋቢና ፈጣን መልስ መስጠት የሚችሉ ጠንካራ ተቋማት በውጭ ቢኖሩን የትግሉ ሜዳ መለወጥ ብቻ ሳይሆን ድሉም ፈጣን ይሆናል።
8. ዓለም አቀፍ ማኅበረሰብ
ሁለተኛው የሕወኀት ትልቅ ዕቅድ የመጀመሪያውን ዕቅድ ለማሳካት በጎሳዎች መካከል የእርስ በርስ ግጭት መፍጠር መሆኑ ከመቸውም ጊዜ በላይ ገሀድ እየሆነ ነው። ይህ ዕቅድ የምሥራቅ አፍሪካን ቀጠና መረጋጋት የሚያናጋና በሶማሊያና በየመን ያለው የእስልምና አክራሪነት በኢትዮጵያ ውስጥ እያቆጠቆጠ ካለው አክራሪነት ጋራ ተደምሮ ለዓለም አቀፍ አሸባሪዎች መስፋፋትና መጠናከር ምቹ ሁኔታን እንደሚፈጥር ግልጽ ነው። ይህንን ለኃያላኑ መንግሥታት፣ ለሰብአዊ መብት ድርጅቶችና ለሌሎችም ለሚመለከታቸው በማስገንዘብና ሕወኀትን ከእብደቱ ተመልሶ ወደብሔራዊ እርቅ እንዲመጣ እንዲያስገድዱት፣ ይህ ካልተቻለ ከኢትዮጵያ ሕዝብ ጎን በመቆም ለነርሱም ሥጋት የሆነውን የሕወኀት ሽብርተኝነት አስቀድመው እንዲዋጉ ጫና በመፍጠር ትልቅ የዲፕሎማሲ ሥራ መሥራት ይጠበቃል።

No comments:

Post a Comment