Translate

Friday, September 28, 2012

ፀረ - ማርያም ፖለቲካ


         ስብሃት ነጋ፣ በፓልቶክ ክፍል ተጋብዞ ባደረገው ንግግር፣ “ለኦርቶዶክስ ወይም ለአማራ ብቻ ተወስኖ የቆውን የኢትዮጵያ መንገስታዊ ስልጣን ለተጨቆነው ህዝብ አስረከብነው” ማለቱን አንድ ጓደኛዬ ነገረኝ። ይህን የነገረኝ ጓደኛዬ በስብሃት ንግግር በጣም ተገርሞ ስለነበር፣ 

        “አታስብ! ስብሃት አብሻቂ የንግግር ጠባይ አለው።” ስል ጠቆምኩት። ለነገሩ በሚናገረው ባልስማማም፣ ስብሃት ያመነበትን እንደወረደ ስለሚያፈርጠው ከሌሎቹ እሱ ይሻለኛል። “በዚህች አለም ላይ መጥፎም ይሁን ጥሩ ያመንክበትን ፈፅመህና የልብህን ተናግረህ ማረፍን የመሰለ እርካታ የለም” ይል ነበር መለስ ዜናዊ - ነፍሱን ይማረውና።
          ስብሃት ነጋ በርካታ ዝነኛ ያልሆኑ አባባሎች አሉት። ለመጥቀስ ያህል፣ “….ትግሬዎችን ወደመጡበት እንመልሳቸዋለን” የተባለችው የበድሩ አደም ነጠላ ዜማ የተለለቀቀች ሰሞን፣ ስብሃት እንዲህ ሲል መልስ ሰጥቶአል፣ “….እኛ ወደመጣንበት ስንባረር፣ መንዜዎችን ሰሜን ሸዋ አራግፈን ነው የምናልፈው!”

ርግጥ ነው፣ አቦይ ስብሃት ከአማራው ኤሊት ጋር አንድ ችግር ያለበት ይመስላል። ከመንዝ ኦርቶዶክስ የፈለቁት መሪዎች፣ የምኒልክን ቤተመንግስት “ለሰፊው ህዝብ” አስረክበው ከስልጣኑ ገለል ካሉ 40 አመታት ሞልቶአቸዋልና ዛሬ ስማቸውን ማንሳት ተገቢ አልነበረም። ዳሩ ግን ከብሽሽቁ እና ከእልሁ በስተጀርባ ያለው ፖለቲካዊ ይዘት ከቶ ምንድነው?
ኮሎኔል መንግስቱ በርግጥ በእናቱ የሸዋ አማራ ነው። እንደ ህወሃት ሰዎች አባባል ኮሎኔሉ የአማራው ገዢ መደብ አገልጋይ የነበረ ነው። ይሄ በራሱ አከራካሪ ነው። ኮሎኔል መንግስቱንም ሆነ መለስ ዜናዊን የኦርቶዶክስ ሃይማኖት ተከታዮች ማለትም አይቻልም። ሁለቱም ኢ-አማኒ ነበሩ። እና የስብሃት፣ “ከአማራ እና ከኦርቶዶክስ” አባበል ለምን መጣ?
የስብሃትን አባባል ተከትሎ ለሃይለማርያም፣ “ፀረ-ማርያም” እና፣ “ፀረ-አማራ” የተባሉ ቅፅሎች እየተሰጡት ነው። በሶሺያል ሚዲያዎች እና በድረገፆች ጭምር የሃይለማርያም መናፍቅ መሆን እየተሰበከ ይገኛል። በእግረመንገድ ምክትሉ ደመቀ መኮንን እስላም መሆኑ እየተጠቀሰ፣ “የጎንደርን መሬት ለሱዳን የሸጠ” የሚል ካባ ይመረቅለታል። ዋናው የጥቃት ኢላማ ከሆነው ሃይለማርያም ላይ የሚወረወሩት ቦምቦች በአብዛኛው ውሸት ናቸው። ለአብነት ሃይለማርያም ሶስት ጊዜ ሃይማኖት ስለመለዋወጡ የሚፃፈው እውነት አይደለም።
ሃይለማርያም በጴንጤነቱ እና በወላይታነቱ ምክንያት በአማሮች የደረሰበት በደል እንደ መወያያ አጀንዳ ሆኖ ጠረጴዛ ላይ ወድቆአል። እንደ ዘገባው ሃይለማርያም የወያኔ አባል ለመሆን ፍላጎት ያደረበት፣ በዘረኛነት ምክንያት እድል የነፈጉትን አማራ ግለሰቦች ለመበቀል ሲል ነበር። ባለቤት አልባው መጣጥፍ እንደሚጠቅመው ሃይለማርያም ወደፊት “በፀረ-አማራነት አቋሙ” ሊገፋበት ይችላል?
ለመሆኑ እንዲህ ያሉ ያልተረጋገጡ መረጃዎችን የሚለቀው ማነው?
ለምን አላማ?
በርግጥ ሃይለማርያም ፀረ-አማራ አቋም አለው? 

ፅሁፎቹ፣ “ትምክህተኞች” በግዴለሽነት የሚበትኗቸው ናቸው ወይስ ህወሃት ሆን ብሎ ለአላማው የሚያሰራጨው? መረጃ ስለሌለኝ አላውቅም። ይህን በመሰሉ ቅስቀሳዎች ግን ወያኔ ይበልጥ ተጠቃሚ ሊሆን እንደሚችል ማሳመን ይቻላል።
የህወሃት ሰዎች ሃይለማርያምን በመሪነት ሲያስቀምጡ፣ ለጊዜው አማራጭ ስለሌላቸው እንጂ፣ ልባቸው ፈቅዶት አይደለም። ብአዴን የተባለውን የስልጣን ተፎካካሪ፣ ገለል ለማድረግ ግን የሃይለማርያምን ሹመት ከማፅደቅ የተሻለ አማራጭ አልነበራቸውም። እንዲህም ሆኖ የብአዴን እና የህወሃት የውስጥ ሽኩቻ ገና መፍትሄ አላገኘም። የብአዴን ሰዎች እንደ መድሃኒት ቤቱ የእባብ አርማ፣ ሃይለማርያም ላይ ተጠምጥመውበታል። ኤልያስ ክፍሌ የጀመረው፣ “ለሃይለማርያም እድል እንስጠው!” ዝንባሌም ለህወሃት አሳሳቢና ራስ ምታት ሊሆን እንደሚችል ማመን ይቻላል። ምክንያቱም ሃይለማርያምን እንደ አባዱላ ጠፍጥፈው እንዳልሰሩት ያውቃሉ። ያነበበ፣ በማንበብ ላይ ያለ እና የተማረ ሰው ነው። የተማረና ያነበበ መሆኑ፣ ብቁ የፖለቲካ መሪ ሊያደርገው ባይችልም፣ የጠቅላይ ሚኒስትሩን ቢሮ ሲለማመደው አንጎሉን መጠቀም ሊጀምር ይችላል ብለው ይሰጋሉ። ከሃይለማርያም ሹመት በፊት ተጣድፈው ጄኔራሎቹን መሾማቸው ለዚህ አባባል አንድ ጠቋሚ ምልክት ነው። ሃይለማርያም ከምእራባውያን እና ከህዝብ በሚያገኘው ድጋፍ፣ አሻንጉሊት ላለመሆን ድፍረት ሊሆነውም ይችላል። ሃይለማርያም አንድ ደካማ ግለሰብ ቢሆንም፣ የገባበት ቢሮ ሃይል ሆኖ ሊያበረታው ይችላል።  የህወሃት ሰዎች ይህን ያውቃሉ፣ ይህንንም ይገምታሉ።
ከሃይለማርያም በኩል ያጋጥመናል ብለው ከሚሰጉት ነገር ዋናው፣ ከብአዴን ወይም ከተቃዋሚዎች፣ (በተለይ ከአማራ ተቃዋሚዎች) ጋር የአላማ አንድነት ከመሰረተ ህወሃትን ማንሳፈፍ የመቻሉ እውነት ነው። ከወዲሁ ሃይለማርያምን ከአማሮችና ከኦርቶዶክሶች ማጋጨት ይህን አደጋ ይቀንሰው ይሆን? በትክክል ይመስላል። ለሃይለማርያም፣ “ፀረ-አማራ” እና “ፀረ-ኦርቶዶክስ” የተባሉ ቅፅሎችን የመለጠፉ ዘመቻ በማን እንደተጀመረ ባይታወቅም፣ አንድ ስሙን ያልጠቀሰ፣ “የሃይለማርያም ተማሪ ነበርኩ” ባይ ግለሰብ ግን መርዝ የተቀቡ ከረሜላዎችን በነፃ ሲያድል ሰንብቶአል። ይህን ፅሁፍ በመቃወም በጎ አስተዋፅኦ ለማድረግ የሞከረው ዶክተር አባቡ ተክለማርያም ምስጋና ያስፈልገዋል። ከምስጋና ይልቅ ግን፣ “አድርባይ” የተባለ ርግማን ሲወርድበት ነበር የሰነበተው።
እንግዲህ ብእሮች ሃይለማርያም ላይ ማነጣጠራቸው ግድ ነው። ሃይለማርያምን ከፀረ-ማርያምነት እስከ ፀረ-አማራነት ፈርጀነዋል። ከአሻንጉሊትነት እስከ አምባገነንነት መድበነዋል። ከየዋህነቱ እስከ መሰሪነቱ ልቡን እየቆፈርን ተንትነናል። ከጭንቀታምነቱ እስከ ኮስታራነቱ፣ እንደ ሞተር በትነን ገጥመነዋል። ሃይለማርያም ማን መሆኑ እስኪረጋገጥ፣ ወይም ኤልያስ ክፍሌ አጥብቆ እንደጠየቀው፣ “ሃይለማርያም አቋሙን ግልፅ እስኪያደርግ”  ግምታዊ ሙገሳ እና ውንጀላው በዚህ መንገድ ለጥቂት ሳምንታት መቀጠሉ ግድ ነው።  

http://tgindex.blogspot.no/2012/09/blog-post.html   

No comments:

Post a Comment