Translate

Wednesday, April 4, 2018

ቀጣዬ 100 ቀናት!(ኤርሚያስ ለገሰ)

Ermias Legesse, author and ESAT TV and Radio contributor
መንደርደሪያ
የትግራይ ነፃ አውጪ በገጠመው ሕዝባዊ ማእበል፣ እንዲሁም የሕዝቡን ተቃዉሞ በተከተለበት ጫና ዶክተር አቢይን ወደ ጠቅላይ ሚኒስትርነት አምጥቷል። የዶክተር አቢይ ወደ ፊት መምጣት በብዙ መልኩ የተደበላለቀ ስሜቶችን ፈጥሯል። በህውሓት ደጃፍ ከፍተኛ ቁዘማና ንዴት የፈጠረ ሲሆን በለውጥ ፈላጊው ዘንድ የተከፋፈለ አስተያየቶች በመስተናገድ ላይ ናቸው። በተለይም ዶክተሩ በበአለ ሲመቱ እለት ያቀረበው ንግግር የብዙ ኢትዬጲያውያንን አንጀት ቅቤ ያጠጣ ነበር። በታሪካዊነቱም ተመዝግቧል።

በአጭር ጊዜ ውስጥ በስልጣን ኮርቻው ላይ የወጣው ዶክተር አቢይ እጅግ ውስብስብ የሆኑ ችግሮችን ለመፍታት፣ መንፈሱ የተበታተነውን የኢትዬጲያ ህዝብ ለማረጋጋት፣ ኢትዬጲያን ወደ ፊት ሊያራምዱ የሚችሉ ሁሉንም ኃይሎች ለማስተባበር፣ የኢኮኖሚ እና ፓለቲካ እቅዶችን ለማስተዋወቅ ጥረት አድርጓል።
ይህንም ተከትሎ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በቀጣይ ቀናት ወደ ተግባር ሊመነዝራቸው ይገባል የተባሉ ስፍር ቁጥር የሌላቸዉ ድርጊቶች መዘርገፍ ጀምረዋል። ሰውየው ለወደፊቱ ያለበትን ተልእኮ የሚያሳስበውም ብዙ ነው። እኔም እንደ አንድ ኢትዬጲያዊ ዶክተር አቢይ በኦሮሚያ የጀመረውን ስራ ሳይጨርስ ወደ ፌዴራል መምጣቱ ልቤ አልተቀበለውም። ተቃውሞዬን በአደባባይ ገልጫለሁ። በጠላቶቹ ሜዳ ላይ ከመጫወቱ በፊት የራሱን ሜዳ በብረት እንዲያጥረው ፍላጐቴ ነበር።
አሁንም ቢሆን ከትላንት አቋሜ የተለወጠ ነገር የለኝም። በስልጣን ላይ ያለው ሽፍታ አገዛዝ አሁንም የስለላና ወታደራዊ መዋቅሩን የተቆጣጠረው ነው። ወደድነውም ጠላነውም የኢኮኖሚ መዋቅሩን የተቆጣጠረው ይህ ከፋፋይ ቡድን ነው። ሌላው ቀርቶ የአሁኖቹ የዶክተር አቢይ የግልና የቤተመንግስት ጠባቂዎች የሟቹ መለስ ዜናዊ ጠባቂዎች ናቸው።
በመሆኑም ሰውየው በአምባገነኖች፣ በዘረኞች፣ በማይማን፣ ኢትዬጲያን በሚጠሉና በሚያሳፍሩ ሰዎች መዳፍ ውስጥ መግባቱን ስመለከት መንፈሴ ይረበሻል። የትግራይ ነፃ አውጪ ካድሬዎች እና ባለሟሎች እንዳይሰራ መውጪያ መግቢያውን እንደሚዘጉበት ሳውቅ ልቤ ይደማል። በፈላ ውሃ እንደምትቀቀለው እንቁራሪት እየሆኑ ያሉት ህውሓቶች የተካኑበትን አጥፍቶ መጥፋት ፓሊሲ እንዳይፈፅሙበት እሰጋለሁ።
በሌላ በኩል አዲሱ ጠቅላይ ሚኒስትር ለኢትዬጲያ ህዝብ ያቀረበው ራዕይ አስደስቶኛል። የኢትዬጲያ ተስፋና የኢትዬጲያችን መቀጠል ሲያስጨንቀው አብሬ ተጨንቄያለሁ። ዶክተር አቢይ የሕዝብ አሽከር ሆኖ ሕዝብን ለማገልገል ቆርጦ መነሳቱን ሳይ በምን ልደግፈው እችል ይሆን የሚል ጥያቄ አንስቻለሁ። የጠላት ሜዳ ላይ አሸንፎ ለመውጣት እንዴት ቢጫወት ያዋጣዋል የሚለውን አስቤያለሁ።
እናም ዶክተር አቢይ የኢትዬጲያ ህዝብ ትግልና እምቢተኝነትን እንደ ነዳጅ እየወሰደ የተቆጠረ ግቦችን በተቆጠረ ጊዜ ቢፈፅም አሸናፊ ሆኖ ሊወጣ ይችላል። ባለፈው መጣጥፌ በተራዘመ ጊዜ ሊፈፅማቸው የሚችሉትን አላማዎች ጠቆም አድርጌ ነበር። ለዛሬው በመቶ ቀናት ሊፈፅማቸው ይገባል ያልኳቸውን የአደረጃጀትና የፓለቲካ ግቦች ጠቁሜያለሁ። እነዚህ አራት ግቦችና በስራቸው ያሉ የተቆጠሩ ተግባራት ከአረጃጀት፣ በመንግስትና በፓርቲ መካከል መኖር ስለሚገባው ግንኙነት፣ ስልጣንን እና ሌብነትን እንዲሁም የዲሞክራሲ እሴቶችን ለመገንባት የተዘረዘሩ ናቸው። ግቦቹና ዝርዝር ተግባራቱ ያለቀላቸው ሳይሆኑ ለውይይት መነሻ ሆነው የሚያገለግሉ ናቸው።
***
##ግብ አንድ:-
በሕገ መንግስቱ መሰረት በኢትዬጲያ ህዝብ አመኔታ እና ተቀባይነት የላቸውን በመለየት የሚኒስትሮች ምክር ቤትና ሌሎች ከፍተኛ የስልጣን እርከኖች ማዋቀር።
*
#የግብ አንድ ተግባር አንድ:-
ሕገ መንግስቱ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከህዝብ ተወካዬች ምክር ቤት አባላት እና ከምክር ቤት አባላት ውጪ ሚኒስትሮችን በመመልመል በፓርላማው ያፀድቃል በሚለው መሰረት እጩዎችን ከሁሉም የህብረተሰብ ክፍሎች መመልመል።
*
#የግብ አንድ ተግባር ሁለት፣
ከተመለመሉት ውስጥ በብቃታቸው፣ በስነምግባራቸውና ተቀባይነታቸው የላቁትን ለሽግግር ጊዜው በሚኒስትርነት መመደብ። በዚህ መሰረት የሚከተሉት ግለሰቦች ለሽግግር ጊዜው ለእጩነት ቢቀርቡ በምክረ ሃሳብ የቀረቡ ናቸው፣
° ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርነት: አቶ ደመቀ መኮንን
° ውጭ ጉዳይ ሚኒስትርነት: ፕሮፌሰር መረራ ጉዲና
° ኢኮኖሚና ፋይናንስ ሚኒስትር: አቶ ስዩም ተሾመ
° ፍትሕ ሚኒስትር: አቶ ተማም አባቡልጋ
° ደህንነት ሚኒስትር: አቶ ገዱ አንዳርጋቸው
° ኮሙዩኒኬሽን ሚኒስትር: አቶ ንጉሱ ጥላሁን
°የአገር ደህንነት ሚኒስትር: አቶ አንዷለም አራጌ
° ገቢዎች ሚኒስትር: - አቶ አስራት አብርሃም
° አርብቶ አደር ሚኒስትር: ዶክተር አብርሃ ተከስተ
° መገናኛ ሚኒስትር: አቶ የሺዋስ አሰፋ
° መከላከያ ሚኒስትር : አቶ በቀለ ገርባ
° ትምህርት ሚኒስትር:- አቶ ሬድዋን ሁሴን
° አሳ ሐብት ሚኒስትር: ወ/ት ፈትለወርቅ ገብረእግዚአብሔር
° የጡረታ ሚኒስትር: አቶ አስመላሽ ወልደስላሴ ( አባይ ነብሶ)
° ቱሪዝም ሚኒስትር:- ዶክተር አዲሳለም ባሌማ
° የኢንቨስትመንት ሚኒስትር:- አቶ ግርማ ሰይፉ
° ወጣቶች ሚኒስትር: - አብርሃ ደስታ
° ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር: - አርቲስት አስቴር በዳኔ
° ኤታማዦር ሹም: - ጄነራል ተፈራ ማሞ
° ፌዴራል ፓሊስ ሹም:- ኮረኔል ደመቀ ዘውዴ
° ሴቶችና ህፃናት ሚኒስትር:- ወይዘሮ የትነበርሽ
° የጽህፈት ቤቱ ሚኒስትር:- አቶ ደግፌ ቡላ
° የንግድ ሚኒስትር:- ተስፋዬ በጅጋ
° የግብርና ሚኒስትር: - አቶ ሲራጅ ፈርጌሳ
*
#ግብ አንድ ተግባር ሁለት፣
የመንግስት የልማት ድርጅቶች፣ ኮርፓሬሽን፣ ባለስልጣናት እና ተቋማት ስራ አስኪያጅ፣ ዋና ስራ አስፈፃሚና ዴሬክተሮች ሹመት የየትኛውም የፓለቲካ ድርጅት አባላት ካልሆኑ ኢትዬጲያውያን ውስጥ ብቃት ያላቸውን መሾም። መመዘኛዎቹ በሚዲያ ተቋማት በግልፅ እንዲነገሩ ማድረግ። ሂደቱን ሕዝቡ በቀጥታ በሚከታተለው መልኩ እና ተወዳዳሪዎች ተቋማቱን እንዴት እንደሚመሩ እና የት ማድረስ እንደሚፈልጉ በሚገልፁበት ሁኔታ እንዲፈፀም ማድረግ። በውጭ የሚኖሩ ከፍተኛ ሙያተኛ የሆኑ ኢትዬጲያውያን እና ትውልደ ኢትዬጲያውያን የውድድሩ አካል እንዲሆኑ ማድረግ።
ከእነዚህ የስልጣን ቦታዎች መካከል ዋና ዋናዎቹ የሚከተሉት ይሆናሉ፣
• የብሔራዊ ባንክ ገዥ
• የልማት ባንክና ንግድ ባንክ ዋና ስራ አስፈፃሚ
• የኢትዬጲያ መድን ድርጅት
• የኢትዬጲያ አየር መንገድ
• የኢትዬጲያ ቴሌ ኮሙዩኒኬሽን
• የመንግስት ሆቴሎች
• የኢትዬጲያ ቴሌቪዥን እና ሬዲዬ
• የመንገዶች ባለስልጣን
• ምርት ገበያ ( ECX)
• ዋና ኦዲተር ጄኔራል
• ሁሉም የአምባሳደርነት ቦታዎች
• አደጋና ዝግጁነት ዴሬክተር ( አመዝኮ)
*
#የግብ አንድ ተግባር ሶስት:-
በመንግስት በጀት የሚተዳደሩ አላስፈላጊ የሚኒስቴር መስሪያቤቶች፣ ባለስልጣናት ፣ ተቋማት እና የሐላፊነት ቦታዎችን ማፍረስ። ከእነዚህ ውስጥ ቅድሚያ የሚሰጣቸው፣
• ፌዴራል ጉዳዬች ሚኒስትር
• የመንግስት ዋና ተጠሪ ፅህፈት ቤት
• የብሮድካስት ባለስልጣን
• የኢትዬጲያ ዜና አገልግሎት እና ፕሬስ ድርጅት
• የእምባ ጠባቂ ኮሚሽን
• የሰብአዊ መብት ኮሚሽን
• ምርጫ ቦርድ
• የብረታ ብረት ኮርፓሬሽን ( ሜቴክ)
• ብሔራዊ መረጃ መረብ ደህንነት ኤጀንሲ(ኢንሳ)
• የፓሊሲ ምርምር፣ ጥናትና አማካሪ ቢሮ
*
#የግብ አንድ ተግባር አራት፣
ጠቅላይ ሚኒስትሩን በቋሚነት የሚያሟክሩ በኢትዬጲያ ሕዝብ ተቀባይነት ያላቸው ከ25 እስከ 30 የሚጠጉ ምስጉን የአገር ሽማግሌዎች፣ የሐይማኖት አባቶችና አገራችንን በአለም ደረጃ ያስተዋወቁ አባላት የያዘ “ አማካሪ ምክር ቤት” ማቋቋም።
• አማካሪ ምክርቤቱ በሁለት ሳምንት አንዴ ( ቅዳሜ ከሰአት) ለግማሽ ቀን የሚሰበሰብ ይሆናል።
• አማካሪ ምክር ቤቱ ዋነኛው ተልእኮ የሽግግር ሂደቱን ለማፋጠን ድልድይ ሆኖ የሚያገለግል ይሆናል። የፓለቲካ ፓርቲዎችን ድርድር በይፋና በሚስጥር ያደርጋል። ፓርቲዎቹ የሚያቀርቡትን የሽግግር ሰነድ እየመረመረ ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ያቀርባል። የዲሞክራሲ ተቋማት ተአማኒነት ባለው መልኩ የሚዋቀሩበትን ሐሳቦች በማመንጨት ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ያቀርባል።
• የአማካሪ ምክር ቤት አባላት የገዥው ፓርቲ አባላትም ሆነ ደጋፊዎች መሆን የለባቸውም።
• ለአማካሪ ምክር ቤት አባልነት ለመነሻ እንዲሆን አቶ እየሱስ ወርቅ ዛፋ፣ አቶ ቡልቻ ደመቅሳ፣ ዶክተር ነጋሶ ጊዳዳ፣ አቶ ክቡር ገና፣ ፕሮፌሰር በየነ ጴጥሮስ፣ አቶ ገብረየስ ቤኛ፣ ዶክተር ዳኛቸው አሰፋ፣ ዶክተር በድሉ ዋቅጅራ፣ አቶ አርአያ ገ/ እግዚአብሔር፣ አቶ ገብሩ አስራት፣ ፕሮፌሰር መስፍን ወልደማርያም፣ ዶክተር ያዕቆብ ሐይለማርያም፣ ዶክተር በፍቃዱ ደግፌ፣ አርቲስት አሊ ቢራ፣ አርቲስት ቴዎድሮስ ካሳሁን፣አርቲስት አረጋኸኝ ወራሽ፣ አትሌት ሐይሌ ገብረስላሴ፣ አቶ አስገደ ገ/ ስላሴ፣ አቶ ገብሩ ገብረማሪያም፣ አቶ ቆስጠንጢኖስ በርሄ፣ ፕሮፌሰር ፍቅሬ ቶሎሳ የመሳሰሉት አባል የሚሆኑበት ይሆናል።
*
#የግብ አንድ ተግባር አምስት፣
የቀድሞ የሕውሓት/ ኢህአዴግ ባለስልጣናትን በሶስት ዙር በጡረታ ማሰናበት። ከጡረታ በኃላ በየትኛውም የሚዲያ ተቋም ፣ብሔራዊና ድርጅታዊ በአላት፣ ስብሰባዎች፣ ምርቃቶች እንዳይገኙ ማድረግ። አቶ ተፈራ ዋልዋ ልምዱን እንዲያካፍላቸው መድረክ ማዘጋጀት። በመጀመሪያው ዙር የሚሰናበቱት አቶ ስዩም መስፍን፣ አቶ በረኸት ስምኦን፣ አቶ አርከበ እቁባይ፣ አቶ ስብሃት ነጋ፣ አቶ አባይ ፀሀዬ፣ አቶ ግርማ ብሩ፣ ዶክተር ካሱ ኢላላ ፣ ኩማ ደመቅሳ ፣ አዲሱ ለገሰ፣ ሳሞራ የኑስ፣ ጌታቸው አሰፋ፣ አለማየሁ ተገኑ ይሆናሉ።
***
#ግብ ሁለት፣
የመንግስት እና ፓርቲ ስራ እንዲለያዩ ማድረግ። ፓርቲ መንግስትን ተክቶ አመራር አይሰጥም። መንግስት በቀጥታ በፓርቲው እየተመራ አመራር አይቀበልም።
*
#የግብ ሁለት ተግባር አንድ፣
የመንግስት አካላት የሚከተሉትን አጠቃላይ የፓለቲካ፣ የኢኮኖሚ፣ የማህበራዊና የባህል ፓሊሲዎች የሚቀየሱት በሚኒስትሮች ምክር ቤት ብቻ ይሆናል።
*
#የግብ ሁለት ተግባር ሁለት፣
በሕዝብ ምርጫ ከሚደራጁ ምክር ቤቶችና ካቢኔዎች ( እስከ ቀበሌ) ውጭ የሚሞሉ የመንግስት ሐላፊነት ቦታዎች የየትኛውም የፓለቲካ ፓርቲ አባል ያልሆኑ ኢትዬጲያውያን እንዲያዝ ማድረግ።
*
#የግብ ሁለት ተግባር ሶስት፣
በሲቪል ሰርቪስ ውስጥ ተቀጥረው የሚሰሩ ሰራተኞችም ሆነ በቀጣይ የሚቀጠሩ ሰራተኞች የትኛውም የፓለቲካ ፓርቲ አባል እንዳይሆኑ ማድረግ። በሲቪል ሰርቪስ ውስጥ እየሰሩ አስቀድሞ አባል የሆኑ ሲቪል ሰርቫንቶች ለነበሩበት ፓርቲ በይፋ መልቀቂያ እንዲያስገቡ ማድረግ። የፓርቲ መልቀቂያ ለማስገባት ፍቃደኛ ያልሆኑ የመንግስት ሰራተኞች በፍቃደኝነት ስራቸውን እንዲለቁ ማድረግ።
*
#የግብ ሁለት ተግባር አራት፣
በመንግስት የስራ ሰአት፣ በመንግስት ፅህፈት ቤት ውስጥ የየትኛውም የፓለቲካ ድርጅት የፓለቲካ ስራ( ማደራጀት፣ መሰብሰብ፣ ካድሬ መመልመል) እንዳይካሄድ ማድረግ። የመንግስት ንብረት ለመንግስት ስራ ብቻ ማዋል። ይሄን ተላልፎ የሚገኝ ማንኛውም ሰራተኛ ከስራ እንዲሰናበት እና የትኛውም የመንግስት መስሪያ ቤት በድጋሚ እንዳይቀጠር ማድረግ።
*
#የግብ ሁለት ተግባር አምስት፣
በዩንቨርስቲዎች፣ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት፣ቴክኒክና ሙያ እንዲሁም በአንደኛ እና ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ማንኛውም የፓለቲካ ፓርቲ በይፋም ሆነ በግልፅ የድርጅት ስራ ( ምልመላ፣ ማደራጀት፣ ስብሰባ፣ መሰረታዊ ድርጅት) የመሳሰሉትን እንዳይሰራ ማድረግ። የትምህርት ተቋማቱ አመራሮች ምደባ የፓለቲካ ፓርቲ አባል አለመሆንን እንደ ቅድመ ሁኔታ በመውሰድ መመዘኛው ብቃት እና ብቃት ብቻ እንዲሆን ማድረግ። በየትኛውም ደረጃ ያሉ መምህራት እንደ ሲቪል ሰርቪስ ሰራተኝነታቸው ከየትኛውም የፓለቲካ ድርጅት አባል አይሆኑም። ህሊናቸው ካልፈቀደ በፍቃደኝነት ስራቸውን እንዲለቁ ይደረጋል።
***
# ግብ ሶስት፣
ስልጣን የሐብት ምንጭ የማይሆንበት ሁኔታ መፍጠር።
*
#የግብ ሶስት ተግባር አንድ፣
ሚኒስትሮች፣ ምክትል ሚኒስትሮች፣ ዋናና ምክትል ስራ አስፈፃሚዎች፣ ስራ አስኪያጆች፣ ዴሬክተሮች፣ መምሪያ ሐላፊዎች፣አምባሳዳሮች፣ ዲፕሎማቶች፣ ከኮረኔል እስከ ጄኔራል ባለ ማእረግ የጦር አዛዦች ንብረታቸውን በመመዝገብ ለሕዝብ ይፋ ማድረግ። የወር የገቢና ወጪ መጠናቸውን፣ የልጆች ትምህርት ቤት ወጪ ወዘተ በምዝገባው እንዲካተት ማድረግ። ለምዝገባ ፍቃደኛ የሆኑትን እና ለመደበቅ ጥረት የሚያደርጉትን ለሕዝብ በማጋለጥ ለህግ ማቅረብ። በአርአያነት ጠቅላይ ሚኒስትሩ እና የካቢኔው አባላት በአንድ ወር ውስጥ ንብረታቸውን ይፋ እንዲያደርጉ ማድረግ።
*
#የግብ ሶስት ተግባር ሁለት፣
በግብ ሶስት ተግባር ሁለት የተገለጡት ባለስልጣናት ከአንድ በላይ የቦርድ አመራርም ሆነ የቦርድ አባል እንዳይሆኑ ማድረግ። በቦርድ የሚተዳደሩ ተቋማት ውስጥ ቢያንስ ሁለት ከተፎካካሪ ፓርቲ፣ አንድ ከባለስልጣንም ሆነ ከሲቪል ሰራተኛ ውጭ ማድረግ። በቦርድ ውስጥ የማገልገል ስራ በፍላጐትና ያለምንም ክፍያ እንዲሆን ማድረግ።
*
#የግብ ሶስት ተግባር ሶስት፣
በግብ ሶስት ተግባር ሁለት የተጠቀሱት ባለስልጣናት የቅርብ ዘመዶች ባለቤት የሆኑበት ቢዝነስ ከባለስልጣኑ ስራ ጋር በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ የሚገናኝ ከሆነ ባለስልጣኑ ሐላፊነቱን በፍቃደኝነት እንዲለቅ አሊያም ሌላ ቦታ ተዘዋውሮ እንዲያገለግል ማድረግ። በተጨማሪም ባለስልጣናቱ ከመንግስት ተቋማት ውጪ ባሉ ድርጅቶች የቦርድ አባልነትም ሆነ የአማካሪነት ስራ መስራት አይችሉም።
*
#የግብ ሶስት ተግባር አራት፣
የፓለቲካ ፓርቲዎች የሚያስተዳድሩት ንብረትም ሆነ ቢዝነስ እንደማይኖራቸው በሕጉ የተገለፀውም ተፈፃሚ ማድረግ። በዚህ ሕግ መሰረት የኤፈርት፣ የትልማ፣ ረስት፣ ጥረት፣ ዲንሾ፣ ወንዶ ንብረቶች ለግል ባለሀብት እንዲሸጡ ማድረግ። ከሽያጭ የሚገኘውን ገቢ ለአንደኛ ፣ሁለተኛና ዩንቨርስቲዎች ማከፋፈል።
*
#የግብ ሶስት ተግባር አምስት፣
የግሉ ዘርፍ በነፃ ገበያው መርህ እየተመራ በኢኮኖሚው ላይ የበላይነቱን እንዲያረጋግጥ ምቹ ሁኔታ መፍጠር። በመንግስት የተያዙ ተቋማት በነፃ ገበያ ህግጋት መሰረት በሂደት ወደ ግል የሚዞሩበት ጥናቶችን ሰርቶ ማጠናቀቅ።
***
#ግብ አራት፣
በኢትዬጲያ ህዝብ ውስጥ ዲሞክራሲያዊ ባህልና እሴቶች እንዲጠናከሩ ማድረግ።
*
#የግብ አራት ተግባር አንድ፣
የፀረ ሽብርተኝነት ፣ የመንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች እና የፕሬስ ህጉን በገለልተኛ ወገን እንዲጠና ማድረግ። የሚኒስትሮች ምክርቤት እና የአማካሪ ምክር ቤት አባላት በጋራ በመሆን በገለልተኝነት አጥንተው የሚያመጡ ሙያተኞችን በስምምነት እንዲመድቡ ማድረግ። ጥናቱ ተጠናቆ እስኪመጣ ድረስ አዋጆቹ በጠቅላይ ሚኒስትሩ አቅራቢነት በፓርላማ እንዲታገዱ ማድረግ። በህውሓት ፓርላማ “ ሽብርተኛ!” ተብለው የተፈረጁ አገራዊ ድርጅቶች በአስቸኳይ እንዲሰረዙ ማድረግ።
*
#የግብ አራት ተግባር ሁለት፣
በሕግ መልኩ በፓርላማ ሊወጣ የተዘጋጀውን “ የማህበራዊ ሚዲያ አጠቃቀም ሕግ” ሙሉ ለሙሉ ሂደቱ እንዲቋረጥ ማድረግ። እንደዚህ አይነት ከፀረ ሽብርተኝነት የባሰ ጨቋኝ ህግ እንዲወጣ በመታሰቡ ለወጣው የሕዝብ ገንዘብ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ይቅርታ ጠይቀው እንደማይደገም ቃል መግባት።
*
#የግብ አራት ተግባር ሶስት፣
ሬዲዬ ፋና፣ ዋልታ፣ ENN ፣ ድምፀ ወያኔ የመሳሰሉ የፓርቲ ሚዲያዎችን ማገድ። በግልፅ ጨረታ ወደ ግል ይዞታ የሚዞሩበትን ሁኔታ ማመቻቸት። ሂደቱ በሚኒስትሮች ምክርቤትና በአማካሪ ምክር ቤቱ መደበኛ ስብሰባ እየቀረበ አበረታች ምርመራ እንዲካሄድ ማድረግ።
*
#የግብ አራት ተግባር ሶስት፣
የሽግግር ሰነድ ካዘጋጁ ተፎካካሪ የፓለቲካ ድርጅቶች ጋር ሚኒስትሮች ምክር ቤትና አማካሪ ምክር ቤቱ ይፋዊ ውይይቱን መጀመር። ውስጣዊ ድርድሮቹ ካለቁ በኃላ ለህዝብ ይፋ በሆነ መንገድ ውይይቱን መጀመር።
-----//----

No comments:

Post a Comment