Translate

Thursday, December 20, 2012

ምርጫ ቦርድ ከኢህአዴግ በላይ ኢህአዴግ ሆኖብናል ሲሉ ተቃዋሚዎች ገለጹ


ታህሳስ ፲፩ (አስራ አንድ) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-መጪው የአካባቢና የአዲስ አበባ ምርጫ ፍትሀዊ መሆን አለበት በማለት ፔትሺን ተፈራርመው ያስገቡት 33 የፖለቲካ ድርጅቶች ዛሬ በመኢአድ ጽህፈት ቤት በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ፣ ምርጫ ቦርድ ለጥያቄያቸው መልስ አለመስጠቱን ገልጸው፣ በንባብ የሰጡዋቸውን ምላሽ እንደ አንድ ትልቅ መንግስታዊ ተቋም በደብዳቤ ለመግለጽ እንኳን ፈቃደኛ አልሆኑም ፣ ምርጫ ቦርድ ከኢህአዴግ በላይ ኢህአዴግ ሆኖብናል ብለዋል።
የፓርቲዎች ጥምረት ኮሚቴ በጋዜጣዊ መግለጫው ላይ እንዳስታወቀው ምርጫ ቦርድ ለገዢው ፓርቲ በግልጽ ወገናዊነቱን አሳይቷል ብሎአል። ያቀረቡትን የውይይት ሀሳቦች ቦርዱ አለመቀበሉን ያሳወቁት ፓርቲዎች ፣ ምርጫው ላይ ለመሳተፍ እና ላለመሳተፍ ገና አለመወሰናቸውን ገልጸዋል።
የምርጫ ቦርድ የህዝብ ግንኙነት ሀላፊ ወ/ሮ የሺ ፈቃደ በምርጫ 1997 ዓም ኢህአዴግን ወክለው ለምርጫ የተወዳደሩ ሲሆን ፣ በ80 ድምጽ ብቻ በማግኘት ተሸንፈው ሲወድቁ የምርጫ ቦርድ ኤክስፐርት ተብለው በህዝብ ግንኙነት ባለሙያነት ተሹመው የፓርቲውን ስራ ያስፈጽማሉ ብለዋል።

ይህ በእንዲህ እንዳለ የኢትዮጵያ ብሄራዊ የምርጫ ቦርድ ከ33ቱ ፓርቲዎች የቀረበለትን ከምርጫ በፊት ባሉት ችግሮች ላይ የእንወያይ
ጥያቄ “በተጨባጭ መረጃ የተደገፈ አይደለም፣ጥያቄዎቹ ከ2002 ምርጫ ጋር የተያያዙ ናቸው” በሚል ውድቅ
ያደረገበት አካሄድ የቦርዱን ገለልተኛ አለመሆን በተጨባጭ ያሳየ መሆኑን ከ33ቱ ፓርቲዎች አስተባባሪዎች አንዱ
ገለጸዋል፡፡
ይህ አስተያየት በ33ቱ ፓርቲዎች የጋራ አቋም የተያዘበት ባለመሆኑ የሚሰጡት የግል ሃሳባቸውን መሆኑን የተናገሩ
ከፍተኛ አመራሩ ምርጫ ቦርድ ጥቅምት 15 ቀን 2005 ዓ.ም በአዳማ በጠራው መድረክ ላይ አንድ አቋም የያዙት
33 ፓርቲዎች ያቀረቡትን የእንወያይ ጥያቄ ሆን ብሎ ምላሽ ሳይሰጥ ሲያንከባልል ቆይቶ ከወራት በኃላ
ሳያነጋግራቸው በራሱ ጊዜ በመንግስት መገናኛ ብዙሃን መግለጫ በመስጠት ውድቅ ማድረጉ ከዚህ ቀደም በተደጋጋሚ
የሚነሳበትን የገለልተኝነት ጥያቄ ያረጋገጠ ነው ሲሉ ኮንነውታል፡፡
ቦርዱ ትክክለኛ ቢሆን ኖሮ ለገዥው ፓርቲ በመወገን የፓርቲዎቹን የእንወያይ ጥያቄ ውድቅ ወደማድረግ ከመሄዱ በፊት
ቢያንስ ባሉት ችግሮች ላይ በመወያየት፣ኀሳቡንም ለፓርቲዎቹ በማስረዳት ወደ መግለጫው ቢሄድ ኖሮ ቢያንስ ውጥረቱንና
አለመተማመኑን በመጠኑ መቅረፍ በቻለ ነበር ብለዋል፡፡
አያይዘውም ቦርዱ ፓርቲዎቹ ያቀረቡት ማለትም የምርጫ ቦርዱ ከላይ እስከታች ያሉ መዋቅሮች ገለልተኛ ያለመሆን
ጉዳይ፣በነጻነት የመንቀሳቀስ፣ደጋፊዎቻቸውን ሰብስበው ማነጋገር ያለመቻላቸው ጉዳይ፣በየክልሉ በአባሎቻቸውና
ደጋፊዎቻቸው ላይ ሕገወጥ እስሮች፣ማሳደድና ከስራ ማሰናበት የመኖሩ ጉዳይ፣የመንግስት መገናኛ ብዙሃን ፍትሐዊ
አጠቃቀም ጉዳይ፣የአንድነት ጋዜጣ በሕገወጥ መንገድ ዕትሙ እንዲቆም መደረጉና የመሳሰሉት ናቸው፡፡
“ቦርዱ ፓርቲዎቹን ጠርቶ ላቀረባችሁት አቤቱታ ምን መረጃ አላችሁ ብሎ ፓርቲዎቹን ሳይጠይቅ የሰጠው ምላሽ
ለፓርቲዎቹ ያለውን ግምት የቱን ያህል የዘቀጠ መሆኑን የሚያሳይና እነዚህ ችግሮች እንደሌሉ ለማረጋገጥ ያደረገው
ሙከራ በመሆኑ ይህ አካል ነጻና ገለልተኛ ምርጫ ያካሂዳል ብሎ ማሰብ እንዴት ይቻላል” ሲሉ ባለስልጣኑ  ጠይቀዋል፡፡
ከአሁን በኃላ ምን ታደርጋላችሁ ተብሎ ለቀረበላቸው ጥያቄ ይህ ውሳኔ በጋራ የሚተላለፍ መሆኑን አስታውሰው ነገር ግን
ከ33ቱ ፓርቲዎች አብዛኛዎቹ ሕዝባዊ ተቃውሞ በመስቀል አደባባይ ለመጥራት ፍላጎት እንዳላቸው አውቃለሁ ብለዋል፡፡
ምርጫ ቦርድ ዘንድሮ የሚያካሂደውን የአካባቢና የአዲስአበባ አስተዳደር ጊዜያዊ የጊዜ ሰሌዳ ላይ ለመምከር በአዳማ
ኤግዚኪዩቲቭ ሆቴል ጥቅምት 15 ቀን 2005 ዓ.ም በጠራው ስብሰባ ላይ ከተገኙ 65 ፓርቲዎች መካከል 33 ያህሉ
ከምርጫ በፊት ውይይት ይቅደም በሚል የጋራ አቋም በመያዝ ለቦርዱ ማሳወቃቸው ይታወሳል፡፡

No comments:

Post a Comment