Translate

Friday, December 14, 2012

ሜጀር ጄነራል አብርሀ በኦጋዴን ጦርነት አትራፊ ናቸው ተባለ

ሜጀር ጄነራል አብርሀ በኦጋዴን ጦርነት አትራፊ ናቸው ተባለ
በኦጋዴን ደገሀቡር ውስጥ በመንግስት ወታደሮችና በኦጋዴን ነጻ አውጪ ግንባር ተዋጊዎች መካከል በተደረገ ውጊያ፤ ከሁለቱም ወገን 32 ሰዎች መገደላቸው ሲገለጽ፤ ጦርነቱን የሚያቀጣጥሉት ከአካባቢው ከሚካሄደው የኮንትሮባንድ ንግድ ትርፍ የሚያጋብሱ የምስራቅ እዝ የጦር አዛዥ ጄኔራል አብርሀ ወልደማሪያም እና የክልሉ ፕሬዚዳንት ናቸው ሲሉ የኦብነግ አመራር አባል አቶ ሀሰን አብዱላሂ ለኢሳት ገለጹ።
በጅጅጋ የሚገኙ ዲፕሎማቲክ ምንጮችን ጠቅሶ ኦጋዴን ቱዴይ ፕሬስ እንደዘገበው የኦብነግ ተዋጊዎች በደገሀቡር ውስጥ ለቢጋ በተባለ መንደር ባለ የመንግስት የጦር ካምፕ ላይ ጥቃት ሰንዝረው 30 የሚሆኑ የመንግስት ወታደሮች መግደላቸውን ገልጸዋል።
17 ቆስለው በደገሀቡር ሆስፒታል እንደሚገኙና ከኦብነግ በኩልም 2 ሰዎች መሞታቸውን የኦብነግ አመራር አባል አቶ ሀሰን አብዱላሂ ከአውሮፓ ገልጸዋል።
ከጥቃቱ በሁዋላ የመንግስት ወታደሮች በመንደሩ ላይ ጥቃት ከፍተው የአካባቢውን ሽማግሌዎችና ሴቶች ታጣቂዎቹን ትደብቃላችሁ በሚል ሰበብ አፍነው እንደወሰዷቸውና የደረሱበት እንደማይታወቅ ኦጋዴን ቱዴይ የዘገበ ሲሆን፤ አቶ ሀሰን አብዱላሂም ይሄንኑ አረጋግጠዋል።
ስለውጊያውና በኬንያ ተጀምሮ ስለነበረው የእርቅ ድርድርና ጠቅላይ ሚኒስትር ሀይለማሪያም ደሳለኝ ሕገመንግስቱን ተቀበሉ ብለው ስላስቀመጡት ቅድመ ሁኔታ የጠየቅናቸው አቶ ሀሰን አብዱላሂ፤ ሕገመንግስቱ ችግራቸው እንዳልሆነ፤ ነገር ግን ጦርነቱ እንዳይቆም የሚፈልጉ የመንግስት የጦር መኮንኖችና የክልሉ ፕሬዚዳንት ለሰላሙ መምጣት እንቅፋት እንደሆኑ ጠቅሰዋል።
በተለይም የምስራቅ ጦር ዋና አዛዥ የሆኑት ሜጀር ጄኔራል አብርሀ ወልደማሪያም በቅጽል ስማቸው ኳርተር፤ ከነቤተሰቦቻቸው በአካባቢው ላይ ከፍተኛ የንግድና ኮንትሮባንድ ቢዝነስ ስላላቸው፤ እንዲሁም የክልሉ የመንገድ፤ የትምህርት ቤቶች፤ የመንግስት ህንጻዎች ግንባታዎች ኮንትራቶች ለጄኔራል አብርሀ ሚስትና ዘመዶች ስለተሰጡ፤ የጦርነቱን መቀጠል ይፈልጉታል ሲሉ ተናግረዋል።
ከአቶ ሀሰን አብዱላሂ ጋር ያደረግነውን ሙሉ ቃለምልልስ በኢሳት ሬድዮ ይከታተሉት።

No comments:

Post a Comment