Translate

Monday, December 3, 2012

የጎልጉል ቅምሻ


(ከዚህም ከዚያም)

high fructose corn syrup per person


ስኳር ለስኳር በሽታ ያጋልጣል
“ጣመኝ ድገመኝ” የምንላቸው ዓይነት ብስኩቶች፣ የቸኮሌት ውጤቶች፣ አይስክሬም፣ ብርታት ሰጪ መጠጦች፣ … በከፍተኛ ሁኔታ ለስኳር በሽታ እንደሚያጋልጡ ሳይንስ ደርሼበታለሁ ይለናል፡፡ በእነዚህ የምግብ ውጤቶች ውስጥ የሚገኘው የበቆሎ ስኳር (fructose corn syrup – HFCS) ምግቦቹን ለማጣፈጥ የሚጨመር በመሆኑ ይህንን ተመጋቢ የሆኑ 20በመቶ ለስኳር በሽታ መጋለጣቸው የማይቀር ነው ይላል ውጤቱ፡፡

ከምዕራባውያን አገራት መካከል አሜሪካ በጣፋጩ አወሳሰድ ቀዳሚውን ስትይዝ በአማካይ አንድ ሰው በዓመት 24.78ኪሎ የበቆሎውን ስኳር በተለያዩ ምግቦች አማካኝነት ወደ ሆዱ ይጭናል፡፡ አንድ ካናዳዊ በዓመት 9.13ኪሎ ሲጭን አንድ ጣሊያናዊ ወይም እንግሊዛዊ ከግማሽ ኪሎ በታች እንደሆነ ጥናቱ ጠቁሟል፡፡ ግብጻዊያን 1.6ኪሎ በአማካይ እንደሚጭኑ ያስረዳው ሪፖርት የኢትዮጵያን ቁጥር አላስቀመጠም፡፡ እንዲህ ያለው አመጋገብና የበቆሎ ስኳር አወሳሰድ ለስኳር በሽታ ብቻ ሳይሆን ለውፍረትና ከዚያ ጋር ተዛማጅ ለሆኑ በሽታዎች እንደሚያልጥ የተለያዩ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡
ማሞና መለያው
ባለፉት ወራቶች በኒውዮርክ ከተማ ሦስት ባለሱቆችን ገድሏል የተባለው ግለሰብ ሲያዝ አስቀድሞ ፖሊስ ከበተነው ምስል ጋር ፈጽሞ ያለመመሳሰሉ ብዙዎችን አስገርሟል፡፡
ወንጀሎቹ በተፈጸሙባቸው ጊዜያት ፖሊስ ባገኘው መረጃ መሠረት ያሰራጨው ምስል የአንድ ፈርጠም ያለና መነጽር ያደረገ ወጣት ጥቁር አሜሪካዊን ነበር፡፡ በቁጥጥር ሥር የዋለው ወንጀለኛ ግን አውሮጳዊ መልክ ያለው የ64ዓመት ዕድሜ ባለጸጋና ጸጉሩ ከወደፊቱ አካባቢ የሳሳ አዛውንት ነው፡፡ የወንጀለኛውና የተጠርጣሪው አለመመሳሰል ወንጀል በተሰራ ቁጥር በጥቁሮች ላይ የማሳበብ ባህልን በግልጽ ያሳየ ነው በማለት በርካታዎች ተችተውታል፡፡
ኢኮኖሚያዊ የሞት ቅጣት
ወደ 250ሺህ ሰነዶችን ይፋ በማድረግ የዓለም መንግሥታትን በተለይም የአሜሪካንን ምስጢራትን ያጋለጠውና የሹልክዓምድ (WikiLeaks) መስራች የሆነው ጁሊያን አሳንጅ ድርጅቱ ገንዘብ መሰብሰብ እንዳይችል በምዕራባውያን የተደረገበት አፈና በድርጅቱ ላይ “ኢኮኖሚያዊ የሞት ቅጣት” እንዲደርስበት ያደረገ መሆኑን ተናገረ፡፡ በለንደን በሚገኘው የኤኳዶር ኤምባሲ ውስጥ በጥገኝነት የሚገኘው አሳንጅ በስካይፕ በሰጠው መግለጫ በተለይ ከስድስት የአሜሪካ የገንዘብ ተቋማት (ቪዛ፣ ማስተርካርድ፣ …) የደረሰበት ዕቀባ በድርጅቱ ላይ ወደ 50ሚሊዮን ዶላር ኪሣራ እንዳመጣበት ጠቁሟል፡፡ ከኤምባሲው ውጪ ከፍተኛ የፖሊስ ቁጥጥር እየተካሄደ ባለበት ወቅት በኤምባሲው ውስጥ ለተገኙትና በግምባር በዓለምዙሪያ ደግሞ በስካይፕ መልዕክቱን ሲያስተላልፍ ስለ ጤንነቱ የቀረበለትን ጥያቄ ሳይመልስ አልፎታል፡፡ ሥር በሰደደ የሳንባ በሽታ እየተጠቃ ነው የተባለውን ዜና የኤኳዶር መንግሥት አስተባብሏል፡፡
በተያያዘ ዜና ለሹልክዓምድ መረጃ በማቀበል ተባብሯል የተባለው የአሜሪካ ወታደር ብራድሊ ማኒንግ ሰሞኑን ፍርድቤት በቀረበ ወቅት ባለፉት ሁለት ዓመታት እስርቤት የደረሰበትን መከራ አጋለጠ፡፡ አንዳንዴም መናገር እያቃተው በመንተባተብ በሰጠው ቃል ራሱን ለማጥፋት በተደጋጋሚ ሙከራ እንዳደረገ የተናገረ ሲሆን ለዘጠኝ ወራት በአንዲት ትንሽ ቤት ውስጥ ብቻውን እንዲያሳልፍ መደረጉ ከፍተኛ የስነልቦና ጉዳት እንዳደረሰበት የ24ዓመቱ ወጣት አስረድቷል፡፡ ከዚህ ሁሉ በላይ ግን ለበርካታ ቀናት ዕርቃነሥጋውን እንዲተኛ መደረጉ ያለፍርድ ቅጣት እንዲቀበል ያደረገው በመሆኑ የደረሰበት እስካሁን የከፈለው ቅጣት ተቆጥሮለት ክሱ እንዲቆምለት ፍላጎት እንዳለው አስታውቋል፡፡
ዘመነ ብልጥስልክ ሊያበቃ ነው
ከወደ ቴክኖሎጂው መንደር ጉድ የሚያሰኝ ዜና ሰሞኑን ተሰምቶዋል፡፡ በቅልጥፍናቸው፣ በአጠቃቀም ብቃታቸው፣ … ተወዳጅ የሆኑት ብልጥስልኮች (Smartphones) ተገልግለን ሳንጠግባቸው ተፈላጊነታቸው በመነጽር ላይ በሚሰኩ ኮምፒውተሮች ይተካሉ እየተባለ ነው፡፡
የጉግል መነጽር
የማይክሮሶፍት መነጽር
ጉግል (Google Glass) የሚባል እና ማይክሮሶፍት ደግሞ ተመሳሳዩን እያሰሩ የሚገኘው ይኸው የኮምፒውተር መነጽር ይፋ ሲሆን የብልጥስልኮች ተፈላጊነትን በእጅጉ እንደሚቀንሰው እየተነገረ ነው፡፡ የኮምፒውተርን የዕድገት ለውጥ በማንሳት የሚከራከሩ “የዛሬውን አያድርገውና ኮምፒውተር ማለት በርካታ ፎቆች ካሉት ህንጻ ጋር የሚወዳደር ነበር፡፡ ቀጥሎም በመቀመጫ ዴስካችን ላይ ሆነ ከዚያም ጭናችን ላይ አሁን ደግሞ የእጃችን መዳፍ ላይ ነው፡፡ ቀጣዩ ፊታችን ላይ ይሆናል” በማለት ትንበያውን ያጠናክራሉ፡፡
በማህጸን ውስጥ የተስፋፊነት “ጦርነት”
መንትያዎች በእናታቸው ማሕጸን ውስጥ ሆነው ያችኑ ትንሽ ቦታ ለመጠቀም የእርስበርስ ትግል እንደሚያደርጉ ከወደህክምናው ዓለም ተሰምቷል፡፡ ሲኒማዊ በሆነ መልኩ የተቀረጸው የ MRI ውጤት እንደሚያሳየው ተስፋፊነትና የይገባኛል ጥያቄ የሚጀምረው ከየት እንደሆነ ለማወቅ ያስቻለ ነው ያስብላል፡፡
ይኸው በእንግሊዝ የህክምና ተመራማሪዎች የተቀዳው ምስል እንደሚያሳየው መንትዮቹ በእናታቸው ማኅጸን ውስጥ ሆነው በቀኝ በኩል ያለው ትንሹ ሰፋ ያለ ቦታ ለማግኘት ትልቁን ሲመታውና ሲገፋው ይታያል፡፡ መጀመሪያ ላይ ትልቁ ምንም ያልሆነ መስሎ ቢታይም በኋላ ግን በጉልበቱ በመማታት የመልሶ ማጥቃትና የድንበር ማስጠበቅ ተግባር ሲፈጽም ይስተዋላል፡፡ ለበርካታ ምርምሮች ፈርቀዳጅ እንደሆነ የተነገረለት ይኸው ሁኔታ ተስፋፊነት፣ ድንበር ማስጠበቅ፣ ሉዓላዊነት፣ … የመሳሰሉት ሃሳቦች የት እንደሚጀምሩ ያመላከተ ነው ሊያስብል የሚችል ነው፡፡
ፊንላንድ፡ በትምህርት ሥርዓት አንደኛ
ፒርሰን የተሰኘው ተቋም ሰሞኑን ባወጣው ዘገባ መሠረት በትምህርት ሥርዓት ፊንላንድ አንደኛ ደቡብ ኮሪያ፣ ሆንግኮንግ፣ ጃፓን እና ሲንጋፖር በተከታታይ ከ2ኛ እስከ 5ኛ ደረጃ ላይ እንደሚገኙ ጨምሮ አስታውቋል፡፡
ይኸው የሰለጠኑ በሚባሉ አገራት መካከል ያለውን የትምህርት ጥራትና ሥርዓት የገመገመው ጥናታዊ ዘገባ ለአሜሪካ የ17ኛ ደረጃ ሰጥቷታል፡፡ በተመሳሳይ ሁኔታ በቅርቡ በሃርቫርድ ዩኒቨርሲቲ የተደረገ ጥናት በላትቪያ፣ ቺሌና ብራዚል የሚገኙ ተማሪዎች በአሜሪካ ከሚገኙ ተማሪዎች በሦስት እጥፍ ፈጣንእንደሆኑ የዘገበ ሲሆን በአጠቃላይ በ11 አገራት የሚገኙ ተማሪዎች በአሜሪካ ከሚገኙቱ የሁለት ዓመታት ያህል የትምህርት ብልጫ እንዳላቸው ዘግቧል፡፡ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ከ12 ዓመታት ወደ 10 ዓመታት “እንዲሻሻል” የተደረገባት አገራችንስ የትኛው ደረጃ ላይ ትሆን?
“ለመመረጥ ብዬ ነው እንጂ …”
በቅርቡ በተጠናቀቀው የአሜሪካ ምርጫ ከቴኔሲ ጠቅላይግዛት ወረዳቸውን በመወከል ለሸንጎ የተወዳደሩት ብራድ ስታትስ በፖሊስ ቁጥጥር ሥር ውለው እንደነበር የተሰማው ወሬ ግለሰቡን “ግብዝ” የሚያሰኝ ነበር፡፡
የአራት ልጆች አባት የሆኑትና የትዳርን እሴት በእጅጉ እንደሚያከብሩ በምርጫ ዘመቻ ወቅት ሲሰብኩ የነበሩት እኚሁ ግለሰብ ወግ አጥባቂ የሪፓብሊካንን አጀንዳ አራምደው በከፍተኛ ሁኔታ ከተሸነፉ በኋላ በሰጡት ንግግር ስለ ባለቤታቸው ሲናገሩ እርሷ ባትፈቅድልኝ ኖሮ ወደ ምርጫ ውድድር አልገባም ነበር በማለት አወድሰዋቸዋል፡፡ አሁን ግን ሁሉም ከተጠናቀቀና የሽንፈት ጽዋን ከተጎነጩ በኋላ ከባለቤታቸው ጋር በተነሳ ክርክር ሚስታቸውን በጥፊ ካጎኗቸው በኋላ አልጋላይ ወርውረዋቸው ቤቱን ለቅቀው ሄደዋል፡፡ ለየካቲት ወር ፍርድቤት የተቀጠሩት ስታትስ የ5ሺህ ዶላር ዋስ ተቀማጭ አድርገው ከእስርቤት ተለቅቀዋል፡፡
የሳምንቱ ምርጥ ፎቶ
የዝናብ ጉዳይ እጅግ የሚያሳስባቸው ኢንዶኔዥያውያን ዝናብ ወቅቱን ጠብቆ እንዲመጣ የሚያካሂዱት ዑጁንጋን የሚባል አስደናቂ ሥርዓት አላቸው፡፡ ወንዶች ከወገባቸው በላይ ራቁታቸውን ሆነው ከዘንባባ ዛፍ በተሰራ ጅራፍ ይዠላለጣሉ፡፡ በዥለጣው ደም መፍሰስ ከጀመረ ስለ ዝናብ የተጠየቀው በተገቢው ሁኔታ ምላሽ ማግኘቱን የሚያረጋግጡበት ነው፡፡ በደንቡ መሠረት ከወገብ በታችና ከአንገት በላይ መግረፍ ፈጽሞ የተከለከለ ነው፡፡ ዥለጣው ከተጠናቀቀ በኋላ ቂም፣ በቀል፣ ጥላቻ … ሳይኖር ሲዠላለጡ የነበሩት ተሳስቀው ዝናብ እየጠበቁ ኑሯቸውን ይቀጥላሉ፡፡
ዘገባውን ለማጠናቀር በየጽሁፉ ከጠቀስናቸው ምንጮች በተጨማሪ ሌሎችንም የሚዲያ ውጤቶች መጠቀማችንን ለመግለፅ እንወዳለን፡፡ ከዜናዎቹ ማነስ አኳያ በየጸሁፉ ለመግለጽ ባለመቻላችን ይቅርታ እንጠይቃለን፡፡

No comments:

Post a Comment