Translate

Thursday, December 20, 2012

ጠቅላይ ፍርድቤት የእነ አቶ አንዱዓለምን ይግባኝ አዳመጠ


ኢሳት ዜና:-የፌዴራል ጠቅላይ ፍርደ ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት በእነ አንዷለም አራጌ የክስ መዝግብ በሥር ፍርድ ቤት በሽብር ወንጀል ጥፋተኝነት የተፈረደባቸውን የፖለቲካ ፓርቲ አመራር አባላትና ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ ይግባኝ ክርክር አድምጧል፡፡

ከቃሊቲ እና ቂሊንጦ እስር ቤቶች የቀረቡት ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ፣ የአንድነት ፓርቲ ምክትል ሊቀመንበርና የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ አንዷለም አራጌ፣ የፓርቲው አመራር አባልና የወጣቶች አደራጅ ኃላፊ ናትናኤል መኮንን፣ የመኢዴፓ ፓርቲ ኃላፊ ክንፈሚካኤል ደበበ (አበበ ቀስቶ)፣ የቀድሞው የፓርላማ አባል አቶ አንዷለም አያሌው ናቸው፡፡
የአንዷለም አራጌ፣ የናትናኤል መኮንን እና የክንፈሚካኤል ደበበ ተከላካይ ጠበቃ አቶ ደርበው ተመስገን መከራከሪያቸውን በዝርዝር አቅርበዋል፡፡ “የሥር ፍርድ ቤት (ከፍተኛው ፍርድ ቤት) በደበኞቻቸው ላይ ምንም አይነት የወንጀል ድርጊት ሳይኖር በሕጋዊ መንገድ በሚንቀሳቀሱበት ፓርቲዎችና ሃሳብን በነጻነት የመግለጽ መብታቸውን በመጠቀማቸው ብቻ ጨካኝ እና ከባድ ፍርድ ሳያገናዝብ እንደፈረደባቸው 5 ዋና ዋና ነጥቦችን አቅርበው አስረድተዋል፡፡ አንድ ነገር ወንጀል የሚባለው ህጋዊ ግዙፋዊ እና ሞራላዊ ሁኔታዎች በአንድ ላይ ሲኖሩ ነው፤ ይህ ባሌለበት ነው ፍርድ የተሰጠው” በማለት ጠበቃው ተከራክረዋል።

“በ1ኛ ክስ የጸረ-ሽብርተኝነት አዋጁ አንቀጽ3 እና 4 ተቀናጅተው የተተረጎሙ ቢሆንም ከሽብረተኛ ድርጅት ጋር መገናኘት የሽብርተኝነት ወንጀል መፈጸም ነው የሚል ሀሳብ የላቸውም። ይግባኝ ባዮች ከግንቦት7 አመራር አባላት ጋር ግንኙነት ስለማድረጋቸውም ሆነ ፋሲል የኔዓለም የተባለው ግለሰብ የግንቦት7 አመራርና አባል ስለመሆኑ ይግባኝ ባዮችም ከዚህ ግለሰብ ጋር ስለመገናኘታቸው፣ የሽብር ተግባር ስለማቀዳቸው የቀረበ ማስረጃ የለም።” ያሉት ጠበቃው፣ ይልቁንም አሳምነው ብርሀኑ የተባለው የአቃቢ ህግ ምስክር ” ከአቶ አንዱዓለምና ናትናኤል ጋር ስለአንድነት ፓርቲ መጠናከር እንጅ ስለ ግንቦት 7 አውርተን አናውቅም” በማለት መመስከሩን” ገልጸዋል።
“ሦስተኛ ይግባኝ ባይ አቶ ክንፈሚካኤል ደበበ በፖሊስ ተደብድበው የሰጡት ቃል ነው ፍርድ ቤት ተወስዶ የተፈረደባቸው፣ ዐቃቤ ህግ ያለበትን የማስረጃ ኃላፊነት ስላልተወጣ ይግባኝ ባዮች በነጻ እንዲለቀቁ ፤ ሃሳብን በነፃነት የመግለጽ መብታቸው ገደብ አልፏል ከተባለም መዳኘት ያለባቸው ሃሳብ በነፃነት ከመግለጽ ሕግ መብት አንፃር ነው” በማለት አቶ ደርበው ሞግተዋል፡፡
ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ ያለ ጠበቃ በራሱ ክርክር የቀረበ ሲሆን፣ “ዐቃቤ ህግ ያለምንም ማስረጃ፣ ሠነድ፣ የስልክ ጠለፋ እና የሰው ምስክር እኔን የግንቦት 7 አባል ያደረገኝ ፍጹም ሀሰት ነው፣ እንዲህ ብሎ ለመፈረጅም የተጠቀመበት በሚዲያ ያወጣሁትን ይፋዊ ጽሑፍ እንደማስረጃ በመጠቀም፣ በማቋቋም ላይ የነበረውን የሲቪክ ተቋም በማየት እና በአንድነት ፓርቲ ያደረኩትን ህዝባዊ ንግግር በመጠቀም ብቻ ነው” ብሏል፡፡
ጋዜጠኛ እስክንድር ” በእኔ ላይ የቀረበው የሰው ማስረጃ የመኢዴፓ ፓርቲ ሊቀመንበር አቶ ዘመኑ ሞላ ሲሆኑ እርሳቸውም የመሰከሩት ፓርቲያቸው ሊያደርግ ለነበረው ሰላማዊ ሰልፍ እኔን ፈልገው እንዳገኙኝ እና ምክር እንደጠየቁኝ፣ እኔም ይህን አታድርጉ ይቅርባችሁ እንዳልኳቸው፣ ከውጪ ሰዎች ምንም ዓይነት ግንኙነት እና ገንዘብ እንዳይቀበሉ እንደነገርኳቸው ፤ ይሄንንም የዐቃቤ ህግ ምስክርነታቸውን የእኔም መከላከያ ምስክር አድርጌ አፍርሼዋለሁ፡፡ መስራች አባል የነበርኩበትንና በመቋቋም ላይ የነበረው የሲቪክ ተቋምም ቢሆን ማህበራዊ ሲቪክ ተቋም መመስረት ወንጀል ቢሆን ለምን እኔ ብቻ ተነጥዬ እታሰራለሁ፣ እጠየቃለሁ መስራቾች ሰባት ነን ግን የተከሰስኩት እኔ ብቻ ነኝ ይሄንንም ፍርድ ቤቱ በጁዲሸሪ ኖቲስ ላይ ከግንዛቤ እንዲያስገባው” እጠይቃለሁ ብሏል፡፡
ጋዜጠኛ እና የፖለቲካ አክቲቪስት የሆነው እስክንድር ነጋ ለፍርድ ቤቱ ሲናገር “ዐቃቤ ህግ እኔን እና ግንቦት ሰባትን በዓላማ አገናኝቶናል፤ ነገር ግን የእኔ እና የግንቦት ሰባት ዓላማ አይገናኝም፤ እኔን የግንቦት ሰባት አባል ስለመሆኔ፣ የግንቦት ሰባት ጋዜጣ ያወጣውን ዜና ዋቢ በማድረግ ነው የፈረጁኝ፣ ከፍተኛው ፍርድ ቤትም የፈረደው” ብሎአል።
“የአረብ ስፕሪንግ ዓላማው ስልጣን መያዝ አልነበረም፣ ከፍተኛው ፍርድ ቤት ግን የመንግስት ስልጣን ለመያዝ ነው ሲል ተንትኗል፡፡ ነገር ግን የአረብ ስፕሪንግን ብንመለከት በቱኒዚያም፣ በግብጽም ሆነ በሊቢያ አንድም የፖለቲካ ስልጣን አልያዙም፤ ይልቁንም ፓርቲዎች ናቸው ስልጣኑን የያዙት፡፡ ነገር ግን ከፍተኛው ፍርድ ቤት እንደሚለው የአረብ ስፕሪንግ በፖለቲካ ፓርቲዎች አልተመራም፡፡ ከፍተኛው ፍርድ ቤት የአረብ ስፕሪንግ ህገወጥ ነው ቢልም የኢትዮጵያ መንግስት ግን የአረብ ስፕሪንግ ህዝባዊና ህጋዊ ነው በማለት እውቅና ከሰጡ አገራትና መንግስታት መካከል ይመደባል፡፡ እኔም የአረብ ስፕሪንግን  አርዓያ መከተሌ ህገመንግስታዊ እንጂ ኢ- ህገመንግስታዊ አይደለም፡፡” በማለት እስክንድር ተከራክሮአል።
ጋዜጠኛ እስክንድር ” በሀገሬ ላይ ያለው ምርጫ ህገመንግስቱ እንደሚለው ህጋዊና ፍትሃዊ ስላልሆነ ህገመንግስቱ የሚለው እንዲተገበር የዜግነት ግዴታ አለብኝ፡፡ ለዚህም በህጋዊ መንገድ ታግያለሁ፤ ምንም ዓይነት ነገር ዐቃቢ ህግ እንደሚለው በእቡዕ የሆነ ነገር የለም፣ በአደባባይ የተናገርኩት፣ በሚዲያ የጻፍኩት፣ የገለጽኩትና የተናገርኩት ነው አንድ እንኳ በእቡዕ የቀረበ ነገር የለም” በማለት በዝርዝር አስረድቷል፡፡
የፌዴራል ዐቃቤ ህግ ዘረሰናይ ምስግናው እና ብርሃኑ በላቸው በበኩላቸው ፣ “ይህ ክስ በባህሪው ለሽብርተኝነት በኤርትራ መንግስት ደጋፊነት የተደረገ ወንጀል ነው፡፡ በአድማ ስምምነት የሥራ ክፍፍል በማድረግ የተፈጸመ ሽብር ወንጀል ነው፡፡ ይህ የግንቦት ሰባት እቅድ ነው፣ አንደኛ እነርሱ እንዳደረጉት የሲቪክ ተቋም ተዳክሟል በማለት በመመስረት፣ ህጋዊ የፖለቲካ ድርጅቶችንና የመደራጀት መብት ሽፋን በማድረግና ሃሳብን በነጻነት የመግለጽ መብት በጋዜጠኝነት ሽፋን የሚያደርጉት እቡዕ ወንጀል ሲሆን ፣ ሌላው እንደተቀሩት ተከሳሾች ኤርትራ ድረስ በመሄድ ወታደራዊ ስልጠና በማድረግ የጦር ሽብር ማድረግ ነው ። ወንጀሉ  በተናጥል መታየት የለበትም፣ በአንድ ላይ አድማ በማድረግ ስለሆነ አንድ ላይ ነው መታየት ያለበት- ይሄም የግንቦት ሰባትን ዓላማ ለማስፈጸም ነው፤ ዓላማ እና ግቡ ሲታይ ነው የሽብር ተግባር የሚሆነው” ሲል ተከራክሮአል፡፡
ዐቃቤ ህግ ለፍርድ ቤቱ ሲያስረዳ ” እኛ የከሰስናቸው አሲረዋል አቅደዋል ብለን ነው፤ በዚህም ላይ ፋሲል የኔዓለም ከአንድም ሁለት ጊዜ በኢትዮጵያ ፍርድ ቤት ጥፋተኛ የተባለ ግለሰብ ነው፤ ከዚህ ቀደም ከነ ኮሎኔል አለበል ጋር በተያያዘ በግንቦት ሰባት አመራርነት የተፈረደበት ነው፡፡ ይሄን ሰው ነው ጥፋተኛ አይደለም የሚሉት፡፡ ከዚሁ ከኢሳት ጣቢያ እናንተ ነጻ ስላልሆናችሁ ከእናንተ ጋር ለመስራት እቸገራለሁ ሲሉ የስራ መልቀቂያ ያስገቡት የአቶ ከፍያለው ማሞን  ደብዳቤ አቅርበናል ፣ ይህ ኢሳት የግንቦት ሰባት ስለመሆኑና ነፃ ሚዲያ አለመሆኑን ያሳያል፣ ተከሳሽ የፓርቲ አመራሮችም ለፓርቲያቸው ሳይሆን በዚያ ሽፋን ለግንቦት ሰባት ወጣቶችን ሲመለምሉ ነበር፣ ግንኙነታቸው የነበረው ከቢሮ ውጪ ነው ሲል” ተከራክሯል፡፡
ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ ለዐቃቤ ህግ የመልስ መልስ ሰጥቷል”"  ”እኔ የሀገሬ ህገመንግስት የሚፈቅደውን መብቴን ነው ተግባራዊ ያደረኩት፡፡ ህገመንግስቱ የሚፈቅደው ስለምርጫ ብቻ ሳይሆን ስለህጋዊና  ፍትሃዊ ምርጫ ነው፣ ይሄ በሀገሬ ስለሌለ ህጋዊና ፍትሃዊ ምርጫ እንዲደረግ ሞግቻለሁ፡፡ በሀገሬ ያለው ምርጫ ይሄን ህጋዊና ፍትሃዊ የሚለውን ህግ ስለማያሟላ፡፡   ዐቃቤ ህግ ጋዜጠኝነትና የሰብዓዊ መብት አክቲቪስትነቱን ሽፋን አድርጎ በህቡእ የሚለው አልገባኝም፡፡ እነዚህን ሽፋን ካደረኩ እቡዕ ምን ያደርግልኛል፤ እሺ ሽፋን አድርጌስ ምን አደረኩ? የቀረበብኝ ነገር የለም፡፡በማለት ጠይቋል።
እስክንድር አያይዞም ” ክቡር ፍርድ ቤት ፣ አበበ በለው ጥፋተኛ የተባለው ከኔ ጋር ስለተገናኘ ነው ፡፡ ከኔ ከመገናኘቱ በፊት እንዲህ አልተባለም፤ እኔ ግንቦት ሰባት በመባሌ ነው  እርሱም ግንቦት ሰባት የተባለው፤ ከክሱ በፊት ከእርሱ ጋር ያደረኩትን ቃለመጠይቅ ነው በኋላ ለተፈጠረው ክስ እንደማስረጃ ያቀረቡብኝ፣ እንደ እኔ በግፍ ግንቦት ሰባት የተባሉ በውጪ የሚገኙ ኢትዮጵያዊያን ብዙ ናቸው ” ብሎአል።
ከፍተኛው ፍርድ ቤት በአቶ አንዱአለም አራጌ ላይ እድሜልክ፣ በአቶ ናትናኤል መኮንን ላይ 18 አመት እና በአቶ ክንፈሚካኤል ደበበ ላይ 25 አመት ጽኑ እስራት መፍረዱ ይታወቃል።

No comments:

Post a Comment