Translate

Friday, December 7, 2012

“ዲቪ አልቀረም!! ቀረ ያለው ማን ነው?”


“ዲቪ አልቀረም!! ቀረ ያለው ማን ነው?”

house of rep


የዲቪ ሎተሪ እድለኛ ነው። ባገኘው እድል መሰረት አሜሪካ ለመግባት ማሟላት የሚገባውን ሁሉ እያከናወነ ይገኛል። በአካል አዲስ አበባ፣ በሃሳብ አሜሪካ ያለው ወጣት ስራውን በገዛ ፈቃዱ ተሰናብቷል። እቃውን ለሚወዳቸው ማከፋፈል ጀምሯል። አውሮፕላን ውስጥ ተሳፍሮ የብስና ውቂያኖስ አልሰነጠቀም እንጂ በምኞት በየቀኑ በረራ ያደርጋል። አሜሪካ!!

“ማርና ወተት የምታፈሰው አሜሪካ እንደገባሁ” እያለ ቃል የሚገባላቸው ዘመዶቹና ቤተሰቦቹ ስንቅ እያዘጋጁለት ነው። ስጦታ ያበረከቱለትና ድንገት ካልተገናኘን በማለት የተሰናበቱት አሉ። እንዳኮበኮበ ያለው ወጣት ላሊበላ ሬስቶራንት ጫማ እያስጠረገ የአጭር የስልክ መልዕክት ይደርሰዋል። መልዕክቱ “ዲቪ ቀረ” የሚል ነበር። ወዲያው “ማን ነው ቀረ ያለው” ሲል መልሶ ጠየቀ። ደነገጠ። ብርክ ያዘው። ህልሙ፣ ውጥኑ ሁሉ ሲተን፣ ከእጁ ሲያመልጠው ታየው፡፡ ለተወሰነ ጊዜ መረጋጋት አቅቶት ነበር። ሌላም ሌላም … ይህንን ገጠመኝ ያገኘነው ከአንድ ወዳጃችን ነው።
አዎ!! ሰሞኑን ይፋ የሆነው የዲቪ ዜና አስደንጋጭ የሆነባቸው ጥቂት አይደሉም። ዲቪ አከተመለት፣ በሩ ተዘጋ ከሚሉት ጀምሮ በሂደት ጉዳያቸውን እያንቀሳቀሱ ያሉት እድለኞች ስጋት ገብቷቸዋል። ጉዳያቸው የተጨናገፈ ያህል ተስፋ የቆረጡም አሉ። በተለይም ዜናውን ተከትሎ በተለያዩ ድረገጾች ዜናውን ለመቀባበልና ላልሰማ ለማሰማት የነበረው ውክቢያ ፈጣን ነበር። የ“ዲቪ ቀረ” ወሬ ያዲስ ዓመት ርችት መስሎ ሞገዱን አጣቦ ከርሟል። ደግነቱ እንዲጸድቅ የተጠየቀው ህግ ዲቪ የደረሳቸውንና አሜሪካ የገቡትን ከነቤተሰቦቻቸው የሚመለከት አለመሆኑ እንጂ ከዚህም በላይ በሆነ ነበር። ይህን ሁሉ እንድናነሳ ያደረገን ሰሞኑን ከአሜሪካ የተወካዮች ምክርቤት ዲቪን አስመልክቶ የተላለፈውን የውሳኔ ሃሳብ ተከትሎ በበርካታ ኢትዮጵያውያን አዋጅ በአዋጅ ሳይሻር፣ ነባር ህግ በአዲስ ህግ መተካቱ ይፋ ሳይሆን “ዲቪ ቀርቷል” የሚያሰኝ ድምዳሜ ላይ የመደረሱ ጉዳይ ነው።
ሁለት ዓስርተ ዓመታትን ሊያስቆጥር ጥቂት የቀረው የዲቪ ሎተሪ ፕሮግራም በመጀመሪያ ሕግ ሆኖ ሲወጣ የነበረው ዓላማ በአሜሪካ ውስጥ የስደተኛ ቁጥራቸው ጥቂት ለሆኑ አገሮች የቪዛና የመኖሪያ ፈቃድ በመስጠት የተመጣጠነ የኢሚግሬሽን ሥርዓት ለመከተል ነበር፡፡ ገና ከጅምሩ እጅግ በርካታ መላምቶችና ነቀፋዎች የተሰጡበት ይኸው ፕሮግራም እስካሁን ቀጥሎ በየዓመቱ በሺዎች የሚቆጠሩ ወደ አሜሪካ በፈቃዳቸው አንዳንዶችም እጅግ ውድ ዋጋ ከፍለው እየተጋዙበት ይገኛሉ፡፡ ለተሻለ ኑሮ!!
የዲቪ ሎተሪ እንደ አውሮጳውያኑ አቆጣጠር በ1995 ሲጀመር ለ55ሺህ ሰዎች ከዓለም ዙሪያ የመኖሪያ ፈቃድ በመስጠት ሲሆን ከ1999 ዓም ጀምሮ 5ሺህው ቪዛ ናካራ (NACARA) ተብሎ በሚጠራው ህግ መሠረት ኒካራጓውያን፣ ኩባውያን፣ ጓቴማላውያን እና ከቀድሞ የሶቪየት አገራት ለሚመጡ ጥገኝነት ጠያቂዎች እንዲውል በመደረጉ የዲቪ አጠቃላይ ቁጥር ወደ 50ሺህ ዝቅ ብሏል፡፡
ይህም ሆኖ በየዓመቱ በሚካሄደው በዚህ የዲቪ ፕሮግራም ኢትዮጵያው በብዛት እየተጠቀሙ ይገኛሉ፡፡ ከአፍሪካ ውስጥ ለኢትዮጵያ የሚሰጠው የቪዛ ቁጥር የሚበልጠው የናይጄሪያውያኑ ብቻ ነው፡፡ የአሜሪካ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መስሪያቤት መረጃ እንደሚጠቁመው ከ1995 እስከ 2012 ድረስ ከኢትዮጵያ ብቻ ወደ 61ሺህ ሰባት መቶ ለሚጠጉ እድለኞች የዲቪ ሎተሪው የወጣላቸው ሲሆን፣ 63ሺህ ስድስት መቶ ደግሞ ለናይጄሪያውያን ተሰጥቷል፡፡ ከናይጄሪያና ኢትዮጵያ ጋር ሲነጻጸር ዝቅተኛ የሕዝብ ቁጥር ያላት ጋና በእነዚሁ ዓመታት 41ሺህ ስድስት መቶ አካባቢ ቪዛ አግኝታለች፡፡ ዝቅተኛ ከሚባሉት መካከል የኢኳቶሪያል ጊኒ ሲሆ በእነዚህ 17ዓመታት ውስጥ 30ቪዛ አግኝታለች፡፡
በአሜሪካ የኢሚግሬሽን ህግ ተሃድሶ እንደሚያሻው በየምርጫውና የምክርቤት ስብሰባ ላይ ከፍተኛ ክርክር የሚያስነሳ ጉዳይ ነው፡፡ ህጉ እድሳት እንዲደረግለት የሚፈልጉት ፖለቲከኞች ከበስተጀርባው የፓርቲያቸውን የፖለቲካ ዓላማ የማስፈጸም ተግባር ስለሚያስቀድሙ የጉዳዩ ባለቤት የሆነውን ተጠቃሚ ከመርዳት አኳያ እስካሁን ይህን ነው የሚባል ለውጥ አልመጣም፡፡
ላማር ስሚዝ
ባራክ ኦባማ የዛሬ አራት ዓመት ሥልጣን በያዙበት ወቅት በምርጫ ዘመቻቸው የኢሚግሬሽንን ህግ እንደሚያሻሽሉ ቃል ቢገቡም እስካሁን ግን ምንም የመጣ ለውጥ የለም፡፡ በዚሁ የኢሚግሬሽን ህግ ላይ ተሃድሶ በማምጣት የአብዛኛውን ላቲን አሜሪካ ተወላጅ ልብ ለመሳብ የሚፈልጉት ሪፓብሊካውያኑም በዚህ ጉዳይ ላይ አልተኙም፡፡
ባለፈው ዓመት የመስከረም ወር በቴክሳሱ የሪፓብሊካን ፓርቲ ተወካይ ላማር ስሚዝ ወደ መድረክ የመጣው ይህ ረቂቅ ህግ ብዙም ሳይገፋ ወዲያው ነበር ወደ መቃብር የወረደው፡፡ ተወካዩ ያቀረቡት ረቂቅ ሕግ H.R. 6429: STEM Jobs Act of 2012 የሚባል ሲሆን ዋንኛ ዓላማውም  በየዓመቱ ከአሜሪካ ዩኒቨርሲቲዎች በማስተርስና ዶክትሬት ዲግሪ በሳይንስ፣ ቴክኖሎጂ፣ ምህንድስና እና ሒሳብ የትምህርት ዘርፎች ለሚመረቁ ስደተኞች በየዓመቱ 55ሺህ የመኖሪያ ፈቃድ (ግሪን ካርድ) በመስጠት አሜሪካ እንዲቀሩ ለማድረግ ነው፡፡ ይህ ሲሆን በየዓመቱ በዲቪ ፕሮግራም የሚሰጠው ቪዛ እንዲቀር በረቂቅ ሕጉ ላይ አብሮ ጥያቄው ቀርቧል፡፡ ረቂቅ ሕጉ በባችለር ዲግሪ ስለሚመረቁም ሌሎች መዘርዝሮችን አካትቷል፡፡
በአሜሪካ የፕሬዚዳንታዊ፣ የተወካዮችና የሕግ መወሰኛ ምክርቤት ምርጫ በተጠናቀቀ ወቅት የፕሬዚዳንትነትንና የሕግ መወሰኛ ም/ቤትን መቆጣጠር ያቃታቸው ሪፓብሊካኑ የተወካዮች ም/ቤትን በአብላጫው የሚቆጣጠሩ በመሆኑ ባለፈው ሳምንት ረቂቅ ሕጉ እንደገና ተነስቶ በ245 ድጋፍ 139 ተቃውሞና 48 ድምጸተዓቅቦ በተወካዮች ም/ቤት እንዲያልፍ ተደርጓል፡፡
ለረቂቅ ሕጉ ድጋፍ ከሰጡት ከ245 መካከል 27ቱ ብቻ ናቸው የዴሞክራቲክ ፓርቲ ተወካዮች፤ ከተቃወሙት መካከል ደግሞ 5ቱ ብቻ የሪፓብሊካን ፓርቲ ተወካዮች ናቸው፡፡ በአሜሪካ የሕግ አወጣጥ ሥርዓት መሠረት ረቂቅ ሕጉ በሥራ ላይ ለመዋል ዴሞክራቶች በአብላጫው በሚቆጣጠሩት የሕግ መወሰኛ ምክርቤት (ሴኔት) ቀርቦ መጽደቅ አለበት፡፡ ከዚያም ፕሬዚዳንቱ ፊርማቸውን ሲያኖሩበት በተግባር መዋል ይጀምራል፡፡ እነዚህን ሁለት ከፍተኛ መስናክሎች የማለፍ ግዴታ የሚጠብቀው ይህ ረቂቅ ሕግ ዴሞክራቶች በሚቆጣጠሩት የህግ መወሰኛ ም/ቤት ከፍተኛ ተቃውሞ እንደሚገጥመው ይጠበቃል፡፡ ይህንንም ቢያልፍ እንኳን ፕሬዚዳንቱ ካልተስማሙበት ድምጽን በድምጽ የመሻር መብታቸውን ተጠቅመው ሕጉን “አልፈርምም” በማለት ውድቅ ሊያደርጉት ይችላሉ፡፡ ሆኖም ፕሬዚዳንቱና አብላጫው የህግ መወሰኛ አባላት ከተመሳሳይ ፓርቲ በመሆናቸው ህጉን ያለመፈረማቸው ዕድል ዝቅተኛ ነው፡፡
በቅርቡ በተጠናቀቀው ምርጫ ከፍተኛ ሽንፈት የተጎነጩት ሪፓብሊካውያኑ በብዛት የስደተኞች ድጋፍ ያለውን የዴሞክራቲክ ፓርቲን በቀጣይ ምርጫዎች ለመርታት አስቀድመው ያቀዱት ነው የሚባልለት ይህ ሕግ በተለይ በሳይንስና ቴክኖሎጂ ከእስያ ለሚመጡት ስደተኞች እንደዚህ ያለውን ዕድል በመስጠት የምርጫ ድጋፍ ካሁኑ ለማግኘት የወጠኑት ነው እየተባለ በሰፊው ይነገርለታል፡፡ ስለሆነም ጉዳዩ የኢሚግሬሽንን ሕግ ለማደስ ሳይሆን የፖለቲካ ጥቅም ለማግኘት ነው በማለት የኢሚግሬሽን ተሟጋቾች ይነቅፋሉ፡፡ ዕድሉ ከአንዱ ጭብጦ ነጥቆ ለሌላው በመስጠት ዓይነት (የዜሮ ድምር ጨዋታ) ከሚካሄድ ይልቅ የዲቪን ፕሮግራም ሳያስቀር የሳይንስና ቴክኖሎጂ ምሩቃንንም ዕድል የሚያሰጥ መሆን አለበት በማለት ዴሞክራቶች ይከራከራሉ፡፡ በሕግ መወሰኛው ላይ ሲቀርብም ረቂቅ ሕጉ ውድቅ ካልተደረገ ምናልባት ይህንን ዓይነት ማሻሻያ ይደረግበታል የሚል ግምትም አለ፡፡
የዚህ ረቂቅ ሕግ ደጋፊና አቀንቃኞች ግን በዲቪ ፕሮግራም እየተካሄደ ያለውን ማጭበርበርና ውስልትና በመጥቀስ የዲቪ ፕሮግራም ለአሜሪካ የሚሰጠው ጥቅም እምብዛም እንዳልሆነ ይተቻሉ፡፡ በተለይ ይህ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየከፋ የመጣውን ማጭበርበር ለመከላከል የሚደረገው አሠራር በአጠቃላይ በኢሚግሬሽን ሕጉ ላይ እያስከተለ ያለውን ተጽዕኖ ይጠቅሳሉ፡፡ ከዚህ በተጨማሪም በዲቪ ፕሮግራም የሚመጡት ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ያጠናቀቁና የሁለት ዓመት የሙያ ሥራ ልምድ ያላቸው በመሆኑ 21ኛው ክፍለዘመን ለሚጠይቀው የሳይንስና ቴክኖሎጂ ፍላጎት ብቃት የሌላቸውና ለአሜሪካ ዕድገት የሚያበረክቱት ከቁጥር የማይገባ ነው በማለት የዲቪ ፕሮግራምን ያጥላላሉ፡፡
የዲቪ ፕሮግራም መቅረት እንደ ኢትዮጵያ ላሉ አገራት ወደ ውጪ ከሚልኳቸው ስደተኞች የሚያገኙትን የውጪ ምንዛሪ የሚያስቀር ቢሆንም አዲሱ ህግ ሥራ ላይ ከዋለ የሚያደርሰው ጉዳት ከዲቪ የላቀ እንደሚሆን ግምት ይሰጣል፡፡ በተለይ በምዕራባውያን እየተደገፉ ሥልጣን ላይ ለዘመናት የቆዩ አምባገነን መንግሥታትን የተማረው የሰው ኃይላቸው በጭቆና ከመኖር ወደ ውጪ ለመውጣት በሚያደርገው ፍላጎት ቀጥተኛ ድጋፍ በመስጠት አምባገነንነትን በተዘዋዋሪ መንገድ ከመደገፍ አልፎ በአገራት ዕድገት ላይ የራሱ ተጽዕኖ ያስከትላል የሚሉ ጥቂቶች አይደሉም፡፡
የሆነው ሆኖ የዲቪ ፕሮግራም እስካሁን አልቀረም፡፡ ይህ አዲስ የተወሰነው ውሳኔም በፕሮግራሙ ላይ የራሱ የሆነ ጥላ ቢጥልም ወደፊት የሚቀሩትን የሕግ አወጣጥ ሥርዓቶችን ተከትሎ በተግባር እስኪተረጎም ድረስ የዲቪ ፕሮግራም ይቀጥላል፡፡ በአዲስ አበባ የአሜሪካ ኤምባሲ ባለሥልጣን ለሪፖርተር እንደገለጹት አዲሱ ሕግ ገና ጸድቆ በተግባር ላይ ያልዋለ ብቻ ሳይሆን በአሁኑ ወቅት የቪዛ ተራቸውን በሚጠበወቁና የጉዞ ዝግጅት በጀመሩ ላይ ምንም ተጽዕኖ እንደሌላው አስታውቀዋል፡፡
ስለዚህ ጫማ አስጠራጊው ወጣት ከድንጋጤው በረድ ይበል፡፡ የ“አሜሪካ ስገባ” ምኞቱንና ሕልሙንም ይቀጥል – ይንሳፈፍበት፡፡ አሜሪካ ማርና ወተት የምታፈስ አገር ስለመሆኗ ቃል የሚገባለት ባይኖርም፤ ዲቪ ግን እንዳልቀረ እናረጋግጥለታለን፡፡ በአገሩ እየኖረ ስደተኛ ከመሆን ህጋዊ ስደተኛ ሆኖ መኖር ይሻል ይሆን? ወይስ ነገሩ ከዝንጀሮ ቆንጆ … ይሆን? መልሱን ባውቀው እኔስ ስደተኛ ሆኜ እቀር ነበር?

No comments:

Post a Comment