Translate

Saturday, December 8, 2012

ውለታ የማታውቅ ሀገር


limenih tadesse


• ያ የኮሜዲ አውራ “እብድ” ተብሎ ጎዳና ላይ “ቆሼ” ይለቅማል!
• እርሱን ያፈራው ኅብረተሰብ የወደቀን ቀና ከማድረግ እንዳይቃና ይተጋል
• ስለዚህ ኅብረተሰቡ እንደ ድመት የራሱን ልጆች ይበላል!

ይኸውልህ ወዳጄ የተመለከትኩትን፣ የታዘብኩትን እና ያስተዋልኩትን እንደወረደ ላጫውትህ፡፡ ያ ጉምቱ የጥበብ ሰው፣ ያ የኮሜዲ-የጭውውት አውራ፣ ያ ጥበብን የተቀባው ባለትልቅ ተሰጥዖው ሰው፣ ያ ከሥነ-ሠብዕ ጥበብ ተሻግሮ የአዕዋፋትን ዝማሬ ምስጢር፣ የንፋስን ሿሿታ፣ የበር-መስኮት ሲጥሲጥታ ሳይቀር በጥበብ ሥራው ላይ አክሎ የሚከውንልህ ተዋናይ ልመንህ ታደሠ፣ ከፒያሳ ወረድ ብሎ ከሚገኘው ቢስ መብራት አደባባይ ላይ፣ እንደ ማንም ቆሼ ሲለቅም ተመለከትኩት፡፡
ልመንህን ያየ፣ እኔን-አንተን አየ፤ እኔን-አንተን ያየ ኅብረተሰቡን አየ፤ ኅብረተሰቡን ያየ-ተቋማቱን አየ ነው እያልኩህ ያለሁት ወዳጄ፡፡
ያ የጥበብ አውራ ልመንህ ታደሰ ሰውነቱ ገርጥቶ፣ የማይቀይራትን ጥቁር ሰማያዊ ወይም ጥቁር ሱፍ በውሃ ሰማያዊ ሸሚዝ አጥልቆ፣ የተጨራመተች ልሙጥ ጥቁር ቆዳ ጫማ ተጫምቶ፣ እንደ ባይንደር መሳይ ነገር ላይ የተጨረማመቱ ቡጭቅጫቂ ወረቀቶችን ይዞ የሥነ ሥዕል ንድፍ እንደሚሰራ ጀማሪ ሰዓሊ ከአደባባይ ሆኖ ድምም-ፍዝዝ ይላል፤ በጀርባው ባነገተው ጥቁር ቦርሳ /ኮሮጆ/ አንዳች ነገሮችን ሸክፏል፡፡ ልመንህ ታደሠ ተርቦም ሊሆን ይችላል-ማን ያውቃል?
ለጠቅ አድርጎ ደግሞ ከቢስ መብራት ሳይርቅ አቀርቅሮ ራመድ-ራመድ ይልና ወዲያው ቆሼ-ነገር ይለቅማል ከመሬት፤ ከዚያም ቀረብ ብሎ ከድማሜው ከሚያናጥበው ሰው ጋር ከራሱ ጋር ብቻ በሚያወራ ሰው ድምጸት አንዳች ውል የሌለው ነገር ያወራል፡፡
ብዙዎች የእድሜ አቻዎቹና የእድሜ ትንሾቹ እያፌዙበት ያልፋሉ፡፡ “ልመንህ በአደባባይ ‹ላይቭ› እየተወንክ ነው፣ ልመንህ አለባቸው ተካ ይጠራሃል- አትሄድም ቶሎ፣ ልመንህ ኑሮ ጠረረብህ፣ ልመንህ ከዋሺንግተን ተንደርድረህ ፒያሳ ጎዳና…” እና ሌላም ሌላ በጆሮዬ ያደመጥኩት ከኅብረተሰቡ የተበረከተለት አቀባበል ነው፡፡ የጎዳና ተዳዳሪዎች ብቻ በፍቅር ሲቀርቡት አስተውያለሁ፡፡ ሊንከባከቡት ይሞክራሉ ግን ደግሞ እርሱ አይመቻቸውም፡፡
“እብዱ” ልመንህ ፊቱን ወደ ፒያሳ አዙሮ ተንቀሳቀሰ፡፡
እንደ ብዙ ወጪ ወራጅ ኢትዮጵያዊያን እና ኢትዮጵያዊያት እኔም በለበጣ ከንፈሬን እየመጠጥኩ ተዘባበትኩበት፤ እንደ ብዙ አሽከርካሪዎች እኔም ገልመጥ አድርጌው የስላቅ ፈገግታ አሳይቼ የእርምጃዬን ማርሽ ጨምሬ ወደ መርካቶ እብስ ለማለት ፈልጌ ነበር፤ ግን አልቻልኩም፡፡ (በመጽሐፍ ቅዱስ ያለው የሣምራዊው ታሪክ ትውስ አለኝ) አንዳች የጥፋተኝነት ስሜት ጭምድድ አድርጎ ያዘኝ፡፡
አይምሰልህ ወዳጄ! ልመንህን እኔ በግል አልበደልኩትም፤ በአካልም አላውቀውም፡፡ በተናጥል ያስቀየመኩትም አንዳች ነገር የለም! በቅርቡ “አበደ” ብለው ከአሜሪካ አገር አውጥተው (ዲፖርት አደረጉት ነው የሚባለው) በተወለደበት ኅብረተሰብ ውስጥ አምጥተው ህዝቡ ውስጥ እስኪደፉት (እስኪጥሉት) ጊዜ ድረስ እንደዚህ ገፅ ለገፅ በአካል አይቼውም አግኝቼውም አላውቅ፡፡
በቲቪ ስክሪን እና በሲዲዎች ብቻ የምመለከተውና የማደንቀው ብርቅዬ አርቲስት ነበር፡፡ ነበር ልበል እንግዲህ-ጎዳና ላይ ጣልነው አይደል፡፡ እኔ እና እሱ በትውልድም፣ በደረጃም ዱባ እና ቅል የምንባል ነን፡፡ የትና የት ይልቀኛል መሰለህ ኢህአዴግ ከበረሃ ወደ አዲስ አበባ በትጥቅ ትግል አሸንፎ በገባ እና ሥልጣነ-መንበሩን በተቆናጠጠበት ጊዜ የነበረውን አስፈሪ የሽግግር ወቅት፣ የበቅሎ ቤቱን ፍንዳታ፣ በልጅ ዓይናችን ያየነውን የሸጎሌውን ፍንዳታና እልቂት፣ በየቤታችን ጣራ በስቶ የሚመጣውን ተባራሪ ጥይትና የመትረየስ እሩምታ የፈጠረብንን ዘግናኝ የፍርሃት አባዜ በጥበብ ሥራቸው ያረሳሱን ከነበሩ ኮሜዲያን አንዱ እና ዋናው ልመንህ ታደሠ ነበር፤ ከአለባቸው ተካ ጋር ተጣምሮ፡፡
እንደማስታውሰው የኢትዮጵያ ቴሌቭዥን የመቶ ሃያ ፕሮግራምን አሁን (እሁድ መዝናኛ) ሲጀምር የዝግጅቱ አስኳል ተደርገው ከሚጠበቁት አርቲስቶች ልመንህ ታደሠ እና አለባቸው ተካ ዋናው ነበሩ፡፡ ዛሬ አለባቸው ተካ በድንገተኛ የመኪና አደጋ ካለፈ ሰነባበተ፤ ልመንህ ታደሠ ደግሞ አብዷል ተብሎ የወለደ (ያፈራ) ኅብረተሰብ ጥሎ አይጥልም ተብሎ ከአሜሪካን አገር ወደ አዲስ አበባ ፒያሳ-አራት ኪሎ ጎዳና ከደጅ ተደፍቷል፣ ተጥሏል ነው እያልኩህ ያለሁት፡፡
ግን እኮ የወለደ (ያፈራ) ኅብረተሰብ ጥሎ አይጥልም የሚለው አባባል ኢትዮጵያ ውስጥ የሚሰራ አይመስለኝም፡፡ ምናልባትም ወላጅ እናትህ ጥላ አትጥልህ ይሆናል፡፡ እንደ ኅብረተሰብ ግን ጥሎ እንዳይጥልህ ወይ በሥጋ የምትወለደው ቤተሰብ ከአጠገብህ ሊኖር ይገባል፤ አልያም በጎሳ፣ በሃይማኖት፣ በኑሮ መደብ ወይም በፖለቲካ ርዮት የምትቧደነው ቡድን ሊኖርህና ያም ቡድን በማህበረ-ፖለቲካው ጥሩ ሥፍራ ሊኖረው ግድ ነው፡፡
አለበለዚያ ከዚያ ውጭ ከሆንክ እንደ ልመንህ ታደሠ ልቀህ የጎላህበት፣ ሌት ተቀን የሰራህለት፣ ቋንቋውን የተቀኘህለት፣ ባህሉን ያዳበርክለት፣ ኪነቱን ያጎላህለት እና የኅብረተሰብ አገልግሎት ደከመኝ ሰለቸኝ ሳትል የሰጠኸው ህዝብ (የግለሰብ እና የማህበራዊ ተቋማት ስብስብ) “ውይ!” ብሎ ከንፈሩን እንደ ጡጦ መጥጦ “ዋ እንደርሱ እንዳትሆን” እያለ ለራሱና ለቤተሰቡ መማሪያው ያደርግሃል እንጂ ለአንተ ምንም አይፈይድልህ፡፡ ምክንያቱም እንደ ኅብረተሰብ ገና ህፃን ልጅ ነው አሁን ያለው ኢትዮጵያዊ ስብስብ፡፡
ይህን የምልህ አንድ ልመንህ ታደሠን ዋቢ አድርጌ ብቻ እንዳይመስልህ፡፡ በርካታ ለኅብረተሰቡ አገልግሎት የሰጡ ሰዎችን ከሠፈሬ፣ ከአካባቢዬ ልጠራልህ እችላለሁ፣ ዳሩ ግን አንተ እነርሱን በጉልህ አታውቃቸውም፣ እኔ ጸሐፊውና የአካባቢዬ ሰዎች ብቻ ነን የምናውቃቸው፡፡ አንተ እና በዙሪያህ ያሉ ሰዎች የምታውቋቸው እኔ የማላውቃቸው ለኅብረተሰቡ ብዙ የሰሩ ሰዎች እንደሚኖሩም እገምታለሁ፡፡
ስለዚህ በጋራ በምናውቃቸው ሰዎች ብቻ ለመጨዋወት እንሞክር ካልከኝ ደግሞ አንሙትን ታውቀው የለ? ምነው አንሙት ያ አጭሩ
ባለዋሽንት የጊሽ አባይ ኪነት ቡድን ጥበበኛ፣ አዎን እንዴት እርሱን ታጣዋለህ- ውለታ መብላት ነው የሚሆንብህ፤ ከድምፃዊያን ይሁኔ በላይ እና ሰማኸኝ በለው ጋር “አንቱየዋ እነርሱ እኮ ልጆች ናቸው፣ ይጫወቱ በጊዜያቸው” ሲል በሙዚቃዊ ድራማው ላይ የሚያቀነቅነው ባለዋሽንቱ እረኛ! ይኸውልህ ከጥቂት ዓመታት በፊት እርሱም በኑሮ ደህይቶና ተደብቶ ሸራተን ፊት ለፊት ላስቲክና ማዳበሪያ ዘርግቶ ተቀምቶ ነበር፡፡ ለነፍሴ ያሉ አበውና እመው ዳቦ እና ጣሳ ውሃ ሲሰጡት በእርሱ የጥበብ በረከት ሲዝናና እና ሲጨፍር የነበረው ኅብረተሰብ እና የማህበረ ፖለቲካው ሊቃውንት በማርሴዲስ መኪና ፍስስ እያሉ ወደ ሸራተን ሆቴል ሲገቡ የለበጣ ፈገግታቸውን እያሳዩት በበላይነት መንፈስ እየተኮፈሱበት ያልፉ ነበር፡፡
አብረውት ከልጅነት እስከ እውቀት የተጠበቡት ጥበበኞች ዝና እና ገንዘብ እንደ አሸን ባፈሱበት በዚያ ወቅት እንኳ ለእርሱ ጠብ ያደረጉለት ነገር አልነበረም፡፡ በመጨረሻ እራሱን እየገዛ እየተነቃቃ ሲመጣ ግን እንዲህ አድርጌለት ነበር፣ እምቢ አለኝ እንጂ እንዲህ ላደርግለት አስቤ ነበር፣ ቅብርጥሶ እያሉ ሞራል በሚያንሳቸው አንዳንድ መጽሔቶች ሞራላቸውን ሊያነቃቁ ሞከሩ፡፡
እሺ ወዳጄ ደግሞ በሌላ ሰው ታሪክ ልሰልስህ፤ ደራሲና ተርጓሚ ህሩይ ምናሴን (አውግቸው ተረፈ) ታውቀዋለህን? እርሱም እንዲሁ አበደ ተብሎ ከአደባባይ ወድቆ የእርሱን ማበድ ሳይሆን የእኛን የማኅበረሰቡን ማበድ እና ሞራል ማጣት ገሃድ አውጥቶብን ነበር፡፡ አንድን ሰው በማህበረ-አገልግሎት ዘመኑ እንደ ሸንኮራ ምጥጥ አድርገን ተጠቅመን እንደማናችንም አንዳች የህይወት ውጣ ውረድ ሲገጥመው ግን ምጣጩን ገለባ ብለን አደባባይ እንጥለዋለን፡፡ ምንም ውለታ እና ባለዕዳነት እንኳ አይሰማንም-እኔ፣ አንተ እና ኅብረተሰቡ ወዳጄ፡፡
ጸሐፊ እና ጋዜጠኛ ሰለሞን ሙሉ ታፈሰንም እንዲሁ ከትውስታህ ትስተዋለህ ብዬ አልጠረጥርም-ወዳጄ፡፡ ይኸው ያን የመሰለ ጸሐፊ የኑሮ ውጣ ውረዱ ላይ የእኛን የወደቀ ላይ ምሣር ማብዛት ጨምረንበት አደባባይ ከወረወርነው ዓመታት አለፉ፡፡ እዚህ ጊዮርጊስ አደባባይ ላይ ተቀምጦ ዘወትር ይታዘበናል፡፡
ትላንት ቤቱ እየተመላለሱ ተልካሻ የጥበብ ሥራቸውን እንዲያቃናላቸው አድርገው ስማቸውን የገነቡ የጥበብ ነጋዴዎች ሁሉ ዛሬበመኪና ሰላም ነሽ ሰሌ እያሉ ያልፉታል-እነርሱ ጥበብን ስለነገዱ አተረፉ፤ እርሱ ነጋዴ ባለመሆኑ አበደ ተባለ፣ አለቀ በቃ!
የሰለሞንን ብዕር ያልተጋራ እና ትሩፋቱን ያልተጠቀመበት የያን ጊዜው የኪነት ሰዎችና የማስታወቂያ ባለሙያዎች የሉም ለማለት እደፍራለሁ – ካለኝ መረጃ፡፡ ግን ዛሬ እነርሱም የእርሱ የገንዘብ ተጠቃሚዎቹም ሆኑ እኛ የጥበብ በረከቱን ያጣጣምን የኅብረተሰቡ አባላት በእርሱ የጎዳና ሕይወት የኛን የበላይነት እያሳየን ምንም ሳንፈይድ ባለዕዳነታችን ሳይሰማን እንደ ከብት በሃያ አንደኛው ክፍለዘመን የጦጣ ኑሮ እንኖራለን፡፡

ዘሪቱ ጌታሁን
ወዳጄ ከቀድሞዎቹ ሰለባዎች ዋቢ ከፈለክ ደግሞ ድምፃዊቷ ባለ-ክራር ሜሪ አርምዴን ታማ ቤቷን ዘግታ ስትቀመጥ የገጠማትን ወደ ኋላ ሄደህ አስታውስ፡፡ ሰሞኑን ደግሞ በመረዋ-ተርገብጋቢ ድምጽዋ “እንቁጣጣሽ … እንቁጣጣሽ …” እና “ትዝታን በፖስታ ልኬልሃለው፣ መልሱን በቶሎ እጠብቃለሁ” እያለች የምታዜመው ዘሪቱ ጌታሁንታማ ሐኪም ወደ ውጭ አገር ሄደሽ ካልታከምሽ በሕይወት የምትቆዪው ለአንድ ዓመት ብቻ ነው ብሏት ቤቷን ዘግታ ተቀምጣለች፡፡
በቃ ዘጠኝ ሞት መጣ ቢሉት አንዱን ግባ በለው ዓይነት ማለት ነው የእርሷ ቆይታ፡፡ ወዳጄ አንተን ማስደበር እንዳይሆንብኝ እንጂ ሌሎች በርካታ የታዋቂ ሰዎችን ዋቢ ታሪክ እያነሳሁ ባወጋህ በወደድኩ፤ ግን ስንቱን አንስተን በማውራት ስንቱን የኅብረተሰብ አባላት አስቀይመን እንችለዋልን፡፡ ያ የጥበብ አውራ ልመንህ ታደሰ እመር-እመር እያለ በመራመድ የሚለክፉትን “ፍንዳታዎች” እና የሚያሽሟጥጡትን ሽማግሌ-“ግንባታዎች” የመልስ ምት እየሰጠ፤ በአንድ ብር ምጽዋት ሊያልፉት የሚፈልጉትን ቁንን ሰዎች ሁለት ብር የመልስ ምት እየሰጠ፣ ገንዘቡን እየበተነ ያልፋል፡፡
እኔም ጸሐፊው ከኋላው እከተላለሁ-ጅል ታዛቢ ሆኜ፡፡ ሲኒማ አምፔር ጋር አንድ ትልቅ ሰው አስቆሙትና እጁን ይዘው “ልመንህ ምነው እንዲህ ራስህን ጣልክ አሉት?” ሀዘኔታ በሚታይበት የፊት ገፅታ፡፡ እርሱ በባይንደር መሳይ ነገሩ የያዛቸውን ወረቀቶች እንዳይነጥቁት በመስጋት ይመስላል በአንድ እጁ ደረቱ ላይ ለጥፎ ለምን አትተወኝም እኔ ማናችሁንም አልፈልግም፣ ተጣልቻችኋለሁ አላቸው፡፡ ሰውየው ሳቃቸው መጣ፡፡ ሌሎች ብዙ ሰዎች ከበዋቸው ቆሙ፡፡ ልመንህ ተቆጣ፡፡ እጁን አስለቅቆ የአራት ኪሎን መንገድ ያዘ፡፡ አስፋልት ዳር ለነበሩ የጎዳና ተዳዳሪዎች የያዘውን አንድ-አንድ ብር ሣንቲም እንዳለ ለገሳቸው እናም እየሳቀ ከራሱ ጋር እያወራ ነጎደ፡፡
ይህ እየሆነ ያለው ተመሳሳይ ክንፎች ያላቸው ወፎች በጋራ ይበራሉ በሚል ብሂል ለመረዳዳት የተሰባሰቡ የሙያ ማህበራት ባሉበት ሀገር ነው፡፡ የደራሲያን ማህበር፣ የሴት ደራሲያን ማህበር፣ የኮሜዲያን ማህበር፣ የሙዚቃ ማህበር፣ የተውኔት ባለሙያዎች ማህበር፣ የፊልም ባለሙያዎች ማህበር፣ የፕሮዲሰሮች ማህበር፣ የ … ማህበር ባሉበት ሀገር ነው፡፡ አየህ ወዳጄ ሀበሻ አበሻ ነው፡፡ ግለሰብ ሆነ ኅብረተሰብ፣ ተቋም ሆነ ዳያስፖራ (በውጭ የሚኖር ኢትዮጵያዊ) በዚህ ረገድ የሚፈይደው በጎ ነገር የለም፡፡
በቅርቡ ከአሜሪካ አገር ለእረፍት የመጣ ጓደኛዬ ድምጻዊ ቴዎድሮስ ታደሠን በአንድ ቅዝቅዝ ባለ ሀበሻ ሬስቶራንት ውስጥ ሲዘፍን እንደተመለከተው በኩራት ነግሮኝ እዚህ እንደ ታምር የምናያቸውን ድምፃዊያን እዚያ በአንድ ቢራ በቅርብ እንመለከታቸዋለን አለኝ፤ ልመንህ ታደሠን ጨምሮ፡፡ አሜሪካ ሁላችንንም እኩል አድርጋናለች፤ ይህንንም ለእከሌ ድምፃዊ ድሮ እኮ ሀገር ቤት እንደ ብርቅ ነበር የማይህ፣ እዚህ ግን እንደዋዛ አገኘሁህ ብዬ ነግሬዋለሁ በማለት ሥለ-ብርቅዬዎቻችን ምንምነት ሲነግረኝ በእነርሱ ሥነ-ልቦና ላይ ስላሳረፈው አሉታዊ ጠባሳ (Trauma) ምንም አልተጨነቀም ነበር፡፡
በአንፃሩ ሌሎች አገራት ታዋቂ ሰዎቻቸውን የአርዓያነት ሚና በኅብረተሰብ ውስጥ ስለሚያጫውቷቸው ለታዋቂ ሰዎቻቸው እንክብካቤያቸው የላቀ ነው፡፡ ከእነዚህ ታዋቂ ሰዎች ጀርባ ባሕላቸው፣ ቋንቋቸው፣ እሴታቸው እና ባንዲራቸው መኖሩን ለደቂቃ አይዘነጉትም፡፡ እንግሊዛውያን ከሼክስፒርም፣ ከቻርልስ ዲከንስ-ም ሆነ ከእግር ኳስ ተጫዋቾቹ ቤካም እና ሩኒ ጀርባ ታላቋ እንግሊዝ መኖሯን ጠንቅቀው ያውቃሉ፡፡ በተለይ በዚህ በ21ኛው ክፍለ ዘመን፡፡ እናም ለታዋቂ ሰዎቻቸው ይጠነቀቃሉ፡፡ የሰዎቻቸውን አያያዝ ያውቃሉ፡፡
በእንግሊዝ አገር ውስጥ ለጥበብ ሰዎቻቸው፣ ለጸሐፊዎቻቸው፣ ለጋዜጠኞቻቸው እና ለኅብረተሰቡ ምርምር ለሚያደርጉ ሰዎች በኑሮ ውጣ ውረድ ውስጥ ሰጥመው ለኅብረተሰቡ የሚሰጡትን አገልግሎት እንዳይገቱ “አርት ሬዝደንስ” የተባለ ተቋማዊ አገልግሎት አላቸው፡፡ ቢታመሙ ያሳክሟቸዋል፣ ቢቸገሩ መፍትሄ ያመላክቷቸዋል፡፡
ይህ ዓይነቱ የአገልግሎት ተቋም በለጋሽ ግለሰብ፣ ድርጅቶችና በመንግሥታዊ ድጎማ የሚንቀሳቀስ ሲሆን የሥራውን እቅድ አቅርቦ ተቀባይነት የሚያገኝ ጥበበኛ እንደ ተፈቀደለት ጊዜያት ለሁለት ሣምንት፣ ለወራት፣ ለአንድ ዓመት እና ለሁለት ዓመት ለኑሮ የሚያስፈልጉ ነገሮች ሁሉ በተቋሙ ቀርቦለት የጥበብ ሱባዔ ይገባል ማለት ነው፡፡ እቅዱን ተግባራዊ እንዲያደርገው፡፡
አየህ ወዳጄ አርት ሬዝደንስ የተባሉት ተቋማት ጥበብን የማዋለድ ሥራ ይሰራሉ፡፡ የዚህ ጸሐፊ ጓደኛም የሦስት ወር አገልግሎት ተሰጥቶት ተግባራዊ ማድረግ ተስኖት የነበረውን ጥበባዊ ክህሎቱን ባህር ተሻግሮ ተወጥቷል፡፡ ወደ እንግሊዝ የመብረሪያውን የአየር ትኬት፣ የምግብና የመኝታ አገልግሎቱን እና የቀን ተቀን የኪስ ገንዘቡን ሁሉ ሰጥተው ነበር በውስጡ የታመቀውን ኪነት ያዋለዱት፡፡
አስተውለህ ከተመለከትክ በአፍሪካ ግብፅ፣ ደቡብ አፍሪካ እና ቡርኪናፋሶ በመሳሰሉ አገራት ትልልቅ ፋውንዴሽን አሉ ለኅብረተሰባቸው አገልግሎት የሰጡ ሰዎች የህይወት ዕክል ሲገጥማቸው ሊያቃኗቸው የሚተጉበት፡፡ እዚህ የእኛ ሀገር ኢትዮጵያ ግን ምንም እንኳ የሦስት ሺህ ዓመት እንደ ሀገር የመቆም ታሪክ ቢኖረንም፣ ምንም እንኳ የቀደምት ሥልጣኔና ጥበብ ባለቤቶች ብንሆንም እንደ አንድ ኅብረተሰብ ገና በቅጡ አላደግንም፤ ገና ህፃን፡፡
በየዘርፉ ያገለገሉ አርዓያ ሰዎቻችንን የህይወት ውጣ ውረድ ሲገጥማቸው ቀና ልናደርጋቸው ከመጣር ይልቅ ቁልቁል ገደል ልንከታቸው እንረባረባለን፡፡ ታመው ከማሳከም ይልቅ ሞተው እናለቅስላቸዋለን፡፡ እንደ ልመንህ ታደሠ ያሉትን ወደ ሆስፒታል ወስደን ወደ ጤናቸው እና የመረጋጋት ህይወት ከመመለስ እና ብሄራዊ ክብራችንን ከመጠበቅ ይልቅ በጎዳና ከንፈር እንመጥላቸዋለን፡፡
አየህ ወዳጄ መፍትሄው እዚሁ ጉያችን ሥር አለ፤ የአእምሮ ህክምና አገልግሎት የሚሰጥባቸው ሆስፒታሎች አሉ፣ በዘርፉ ስፔሻሊስት ሐኪሞቹ አሉ፣ መድሃኒቶች አሉ ነገር ግን ይህን አቀናጅቶ ለእንደዚህ ዓይነት ሁኔታ አገልግሎት የሚሰጥ የተደራጀ ተቋም የለንም፡፡ እናም ያላደገ ኅብረተሰብ ነን ያልኩት ለዚህ ነው፡፡ ያላደገ ኅብረተሰብ ያደጉ ግለሰቦቹን እንደ ድመት ካለማወቅ ወልዶ ይበላቸዋል፡፡
ስለዚህ ውጤቱ አንቺም- ዜሮ- ዜሮ፣ አንተም ዜሮ- ዜሮ፣ እርሱም ዜሮ ዜሮ፣ ሁላችንም ዜሮ ሆነ፡፡ ወዳጄ ታዋቂው ኢትዮጵያዊው ኮሜዲያን ልመንህ ታደሠ በአደባባይ ብቻውን ሲጋልብ በርቀት ይታየኛል፡፡ ለእርሱ የሰጠነውን ኅብረተሰባዊ ምላሽ የተመለከተ ዕጩ ጠቢብ በአገልግሎት መንፈስ ጥበብን ያጋራን ይመስልሃል? ይልቅ ጥበብን ይነግድብሃል!!

No comments:

Post a Comment