Translate

Monday, December 31, 2012

ከዚህም ከዚያም



love1
ፍቅር ቁመት አይወስነውም                                                                                                                                  

የዓለማችን ረጅም ወጣት የከንፈር ወዳጅ የሆነው የ22ዓመቱ ብራዚላዊ ከፍቅረኛው ጋር ያለው ግንኙነት እጅግ አስደሳች እንደሆነ ገለጸ፡፡ ዕድሜዋ 17ዓመትና ቁመትዋ 6ጫማ ከ8ኢንች (2.1ሜትር) የምትረዝመው ኤሊሳኒ ሲልቫ ዕድገቷን የሚቆጣጠረው ዕጢ ላይ ባጋጠማት ችግር ምክንያት እንደዚህ ቁመቷ ሊረዝም እንደቻለና በሽታዋ ከታወቀ በኋላ ሐኪሞች ዕብጠቱን እንዳስወገዱት ተገልጾዋል፡፡

ወደፊት ሞዴሊስት ለመሆን የምታስበው የከንፈው ወዳጅዋ መልካም ስብዕና ያለውና ለእርሷም ድንቅ አመለካከት እንዳለው ገልጻለች፡፡ ሆኖም ችግሯን ከመግለጽ አልተቆጠበችም፤ “ያለኝ ዋና ችግር እጅ ለእጅ ተያይዘን ስንሄድ ትንሹን ወንድሜን ወይም ልጄን ይዤ የምሄድ ይመስለኛል” ብላለች፡፡
የዓመቱ ሰው
ቀዳማዊ ኃይለሥላሴን ታህሳስ 4፤ 1928ዓም (ጃኑዋሪ 6፤1936 አውሮጳውያኑ ቆጣጠር) ዕትሙ የዓመቱ ሰው በማለት የሰየማቸውና በየዓመቱ ይህንኑ ሲያደርግ የቆየው ታይም መጽሔት ባራክ ኦባማን የ2012 የዓመቱ ሰው በማለት ሰይሟቸዋል፡፡ ለስያሜው ምክንያት አድርጎ የጠቀሰውም ባራክ ኦባማ የአሜሪካንን ኅብረት ወደ ተሻለ ደረጃ በማድረስና በዚህ አስቸጋሪ ዘመን ደካማነትን ወደ ዕድል (ብርታት) በመቀየር ቀዳሚውን ቦታ በመያዛቸው የዓመቱ ሰው ለመባል መቻላቸውን ይጠቅሳል፡፡
 
በተቃራኒው የፕሬዚዳንቱን መመረጥ የሚቃወሙ ድርጊቱን አጥብቀው የኮነኑ ሲሆን ባራክ ኦባማ ለዚህ የዓመቱ ሰው ክብር መብቃት የቻሉት “ደደቦች ስለሚወዷቸው እና የመረጃ እጦት ያላቸው ስለሚደግፏቸው” መሆኑን በመጥቀስ ምርጫውን ያጥላሉም አሉ፡፡
የግብረሰዶማውያን መጽሐፍ ቅዱስ
ራሱን “የግብረሰዶማውያን መጽሐፍቅዱስ” በማለት የሚጠራ መጽሐፍ መታተሙን ሰሞኑን ተሰምቷል፡፡ ከቀደምት መጽሃፍቅዱስ ትርጉሞች መካከል በዋንኛነት የሚጠቀሰው የንጉሥ ጀምስ ዕትምን በመተካት የንግሥት ጀምስ ዕትም በማለት የወጣው ይኸው መጽሐፍ በመጽሐፍቅዱስ ላይ ስለ ግብረሰዶማውያን የተጠቀሰውን የፍርሃቻና የተዛባ አጻጻፍ በተከላከለ መልኩ የተጻፈ መሆኑን ያስረዳል፡፡
ደራሲው፡ እግዚአብሔር ተባባሪው ደግሞ ክርስቶስ በማለት በውስጥ ገጹ ላይ ያሰፈረውን ይህንን መጽሐፍ ማን እንዳዘጋጀው የተሰጠ ምንም ዓይነት መረጃ የለም፡፡ በአሁኑ ጊዜ በሽያጭ ላይ የሚገኝ ሲሆን በርካታ አስተያየት ሰጪዎችም የተለያዩ የሃይማኖት መጽሐፎች በተለይም ቁርዓን እንደዚህ ባለ መልኩ ለግብረሰዶማውያን እንዲታተም ጥያቄ አቅርበዋል፡፡
“ስታሊንን እወደዋለሁ” 
ሰሞኑን የቀድሞዋ ሶቪየት ኅብረት መሪ የነበሩት ጆሴፍ ስታሊን 133ኛ የልደት በዓል በተከበረ ጊዜ በጆርጂያና በሩሲያ የሚገኙ ደጋፊዎቻቸው በዓሉን በሃዘን – መሪያቸውን በማጣታቸው – በኩራት – እንደ ስታሊን ዓይነት ወደዚህ ምድር በመወለዱ – አክብረውታል፡፡
“ስታሊንን እወደዋለሁ” የሚሉት በበዓሉ ላይ የተገኙት ደጋፊ ሲናገሩ “የ12 ዓመት ልጅ ሆኜ ሳለሁ አያቴ ስታሊን ሞቶ እንዴት አምርራ ስታለቅስ እንደነበረ አስታውሳለሁ” ብለዋል፡፡ በሩሲያ በተከበረው በዓል ላይ በኮሙኒስት ፓርቲው መሪ ጌናዲ ዡጋኖቭ የሚመሩ በመቶዎች የሚቆጠሩ ደጋፊዎች የስታሊን መቃብር በሚገኝበት ቀዩ አደባባይ አበባ አኑረዋል፡፡ የስታሊን ተቃዋሚ የሆኑ በተለይም በዩክሬይን የሚኖሩም በዓሉን ተቃውሞ በማሰማት አሳልፈዋል፡፡
“በወንድሙ ጦስ ተገደለ”
የአሳድን አገዛዝ ለመጣል እየተዋጉ ያሉትና የምዕራባውያን ቀጥተኛ ድጋፍ ያላቸው የሶሪያ አማጺያን ሰሞኑን የፈጸሙት ግድያ በአሰቃቂነቱ ተጠቃሽ ሆኗል፡፡ የክርስትና እምነት ተከታይ የሆነውን ግለሰብ ታፍኖ ከተወሰደ በኋላ አማጺያኑ አንገቱን ቆርጠው የቀረውን አካሉን ለውሾች መስጠታቸውን ታውቋል፡፡
በታክሲ ሥራ የሚተዳደረው የ38 ዓመቱ ግለሰብ ወንድም አማጺያኑን በመንቀፍ የውንብድና ሥራ እየሰሩ መሆናቸውን ከተናገረ በኋላ በወንድሙ ጦስ ታፍኖ መወሰዱን ጉዳዩን በቅርብ የሚያውቁት መነኩሴይት ተናግረዋል፡፡ የቅዱስ ያዕቆብ ገዳም መነኩሴ የሆኑት እናት በድርጊቱ እስላማዊ አክራሪዎችን የኮነኑ ሲሆን ምዕራባውያን እንዲህ ያለው አሰቃቂ ድርጊት በአገራቸው እንዲፈጸም ለአማጺያኑ መሣሪያ በማቀበል መደገፋቸውን አጥብቀው ኮንነዋል፡፡ በቶሎ ካልተቋጨ ወደፊት ወደ ሃይማኖታዊ ጦርነት ሊሸጋገር እንደሚችል የከረረ ሃሳብ እየተሰጠበት ያለውና ሁለት ዓመት ሊሞላው ጥቂት ወራት የቀሩት የሶሪያ ጦርነት እስካሁን ከ44ሺህ በላይ ዜጎችን ህይወት ቀጥፏል፡፡
ጥይት መከላከያ ለልጆች
በቅርቡ በአሜሪካ በት/ቤት ተኩስ ተከፍቶ 20ሕጻናት ተማሪዎች ከተገደሉ በኋላ በኮሎምቢያ የሚገኝ የጥይት መከላከያ ጃኬት አምራች ድርጅት ለልጆች የሚሆን ልብስ ማዘጋጀቱን ገለጸ፡፡
ከማንኛውም ዓይነት የሽጉጥና አውቶማቲክ ጠብመንጃ ጥይት የሚከላከለውና ቀለል ያለ ክብደት ያለው ጃኬት የልጆችን ቀልብ እንዲስብ በተለያዩ ቀለማት እንደሚሠራ ኩባንያው አስታውቋል፡፡ ዋጋው 500ዶላር ከሆነው ከዚህ ጃኬት በተጨማሪ ኩባንያው ጥይት የሚከላከል የልጆች ደብተር መያዣ ቦርሳም እንዳዘጋጀ ገልጾዋል፡፡
ኤሌክትሮኒክ ሲጋራ አያዋጣም
የሲጋራ ሱስን ለመተው ይረዳል እየተባለ በስፋት የሚሸጠው የኤሌክትሮኒክ ሲጋራ ማጨስ ለማቆም እንደማይረዳ ተሰማ፡፡ የጣሊያን ጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ባወጣው በዚሁ መግለጫ መሠረት ኒኮቲን ያለው በመሆኑ ጉዳቱ እንደመደበኛው ሲጋራ ሲሆን አጫሾችን ሲጋራ ለማቆም የሚያደርገው አስተዋጽዖ እንደሌለ አስታውቋል፡፡
በሲጋራ ማጨስ ማቆምን አስመልክቶ ምክር የሚሰጡ እንደሚሉት ኒኮቲንን ከሰውነትበማስወገድ በአጠቃላይ ሲጋራ ማጨስ ማቆም አማራጭ የሌለው ጉዳይ እንደሆን ይናገራሉ፡፡ ሰዎች ይህንን ውሳኔ ሲያደርጉ የተለያዩ ስሜቶች የሚፈራረቁባቸው ቢሆንም አስቸጋሪ የሆኑት ስሜቶች ከ24 እስከ 72ሰዓታት ባሉት ጊዜያት ውስጥ እንደሚጠፉ እንዲሁም በአካል ላይ የሚከሰቱት ችግሮች ደግሞ ከአራት ሳምንታት ባልበለጠ ጊዜ ፈጽሞ እንደሚወገዱ ሳይንሳዊ መረጃዎችን በመጥቀስ አስተያየት ይሰጣሉ፡፡
የሳምንቱ ምርጥ ፎቶ
ምስሉን ያገኘነው ከፌስቡክ ነው፡፡ “ልማቱ እንዴት ነው?” ብሎ ለሚጠይቅ ብዙ ከማለት ይህንን “ልማታዊ ፎቶ” “ከሶማሊያውያን የሚበልጡ ኢትዮጵያዊያን ተሰደዋል” በሚል ርዕስ የተባበሩት መንግሥታት የስደተኞች ኮሚሽን ያወጣውን ዘገባ አጣቅሰን ከጻፍነው “ደጋፊ ዜና” ጋር ማቅረብ ጥሩ መልስ ሊሆን ይችላል፡፡
ዘገባውን ለማጠናቀር በየጽሁፉ ከጠቀስናቸው ምንጮች በተጨማሪ ሌሎችንም የሚዲያ ውጤቶች መጠቀማችንን ለመግለፅ እንወዳለን፡፡ ከዜናዎቹ ማነስ አኳያ በየጸሁፉ ለመግለጽ ባለመቻላችን ይቅርታ እንጠይቃለን፡፡  

No comments:

Post a Comment