Translate

Saturday, December 1, 2012

የዛሬ ኅዳር 21 የችሎት ውሎ


* አቃቤ ሕግ ባለፈው ሳምንት በመደናበር የዛሬውን ችሎት ደግሞ በሽወዳ ፈጽሞታል

* ሕግ የማይገዛቸው የኢትዮጵያ ቴሌቪዥንና ዛሚ ኤፍ.ኤም ‹‹ሕግ ይግዛችሁ›› ተብለዋል
* ልደታ አካባቢ ፌዴራል ፖሊሶች ‹‹እስላም ማየት አስጠላን›› ሲሉ ውለዋል
ባለፈው ሳምንት ገልጸነው እንደነበረው ዛሬም መሪዎቻችንን ከሕዝብ እይታ ለመሰወር ፖሊስ በደረቅ ሌሊት ነበር ከቃሊቲ ወደ ልደታ ፍርድ ቤት ያመጣቸው፡፡ ሌቱ እስኪነጋና የችሎት ሰዓት እስኪጀምርም በፍርድ ቤቱ ግቢ ውስጥ በፖሊስ ጥበቃ እንዲቆዩ ተደርጓል፡፡ ችሎቱ ከተሰየመ በኋላም የመሪዎቻችን ጠበቆች የኢትዮጵያ ቴሌቪዥንና ዛሚ ኤፍ.ኤም ጣቢያዎች ደንበኞቻችን በተጠረጠሩበት ወንጀል ጥፋተኛ ሳይባሉ ጣቢያዎቹ ግን በተቃራኒው ከፍተኛ የስም ማጥፋት ስራ ላይ ስለተሰማሩ እዚህ ችሎት ውስጥ ካሉ ይውጡልን ብለው ጠይቀዋል፡፡ ዳኛው ችሎቱ ለማንም ክፍት በመሆኑ ይህን ሊያዙ እንደማይችሉና ጣቢያዎቹ የተባለውን ተግባር እየፈጸሙ ከሆነ ግን ከድርጊታቸው እንዲታቀቡ አዘዋል፡፡
የዛሬ ኅዳር 21 የችሎት ውሎ
ቀጥሎ በቀጥታ የባለፈውን ሳምንት የጠበቆች የመጀመሪያ መቃወሚያ፤ መቃወሚያ ለማቅረብ ቀጠሮ አስይዞ ወደ ነበረው ችሎት የተገባ ሲሆን አራቱ ጠበቆችም በመተጋገዝ መቃወሚያቸውን ለፍርድ ቤቱ አቅርበዋል፡፡ የመሪዎቻችንና ወንድሞቻችን ጠበቆች አንስተውት ለነበረው አንኳር እና ጠንካራ የተብራራ መቃወሚያ ሲያደምጥ አቃቤ ሕግ ባለፈው ሳምንት ችሎት በመደናገጥ እና በመደናበር ስሜት ውስጥ እንዳልታየ ዛሬ ደግሞ ችሎቱ ላይ ‹‹መቃወሚያው የተብራራ አይደለም›› የሚል ምላሽ ሰጥቷል፡፡ መሪዎቻችን የተከሰሱት ከሕግ ውጪ እንደሆነ፣ በዋነኝነት የተከሰሱበትና በ2001 የጸደቀው የጸረ ሽብር ሕጉ ሕገ መንግስታዊ ድንጋጌዎችን የጣሰ ነው፣ ክሱ የሕግ ትርጓሜ ጉዳዮችን ስለሚያስነሳ መታየት ያለበት ሕጋዊ ስልጣን በተሰጠው ፌዴሬሽን ም/ቤት ነው፣ ይህ ፍ/ቤት ይህንን ክስ የማየት ስልጣን በሕግ አልተሰጠውም እና ደንበኞቻችን በነጻ ይሰናበቱልን የሚሉ መከራከሪያዎችን ከአገሪቱ እና ከአለም አቀፍ ሕግጋት ጋር ተዋድደው የቀረበለት አቃቤ ሕግ፤ ምላሽ ለመስጠት ሳምንት ያህል ተዘጋጅቶም ሊሰጥ የቻለው ምላሽ ‹‹ይሄ ፍርድ ቤት አያየውም ካላችሁ ለምን እዚህ መጣችሁ?›› ብሎ መሪዎቻችንን እና ጠበቆቻቸውን ግራ በገባው ሽወዳ መጠየቅ ነበር፡፡ አቃቤ ሕግ መሪዎቻችንን በግድ ከቤታቸው ወስዶ እንዳሳሰራቸውና ከሶም (ለምን መጣችሁ ባለበት) ፍርድ ቤት እንዳቀረባቸው እንኳ በውል አያውቅም፡፡
የመሪዎቻችን ጠበቆች ባቀረቧቸው ሌሎች መቃወሚያዎች ላይም አቃቤ ሕግ በቂ ምላሽ መስጠት ሳይችል ምላሹን አጠናቋል፡፡ ፍ/ቤቱ አሁን በተነሳው ወቃወሚያ ላይ ብይን ሰጥቶ ወደ ክርክር ይገባ ወይም አይገባ በሚለው አጀንዳ ላይ ውሳኔ ለመስጠት ለሚቀጥለው ሳምንት ሐሙስ ኅዳር 27 ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡ ችሎቱ ከመጠናቀቁ በፊት ጠበቃዎች የመሪዎቻችን ቤተሰቦች ችሎቱን እንዳይታደሙ መከልከላቸውን በመግለጽ ፍ/ቤቱ ውሳኔ እንዲያሳልፍ የጠየቁ ሲሆን ከቀጣይ ችሎት ጀምሮም ቤተሰቦች መግባት እንደሚችሉ ፍ/ቤቱ ገልጿል፡፡ በሽፍን በዳኞች መግቢያ በር የገቡት መሪዎቻችን በዚያው በር ከሰው እይታ በተሰወረ መልኩ ወጥተው በከፍተኛ የፌዴራል ፖሊስ አጀባ በልደታ ኮንዶሚኒየም፣ በአዲሱ የብስራተ ገብርዔል መንገድ አድርገው ወደ ቃሊቲ ተመልሰዋል፡፡ ዛሬም የመጡባት መኪና ሰማያዊዋ ባለሶስት መስኮት መኪና ስትሆን መሪዎቻችን አጋርነቱን ሊያሳያቸው የተሰበሰበውን ሕዝብ በርቀት እጃቸውን በማውለብለብ ሰላምታ ሰጥተዋል፡፡
በሌላ በኩል ልደታ እንድንገናኝ የተላለፈውን መልዕክት ተከትሎ በጣም በርካታ የአዲስ አበባ ሙስሊም ነዋሪዎች ከማለዳው አንድ ሰዓትና ከዚያም ቀድመው ልደታ አካባቢ ቢደርሱም ባልጠበቁት መልኩ አካባቢው በከፍተኛ ታጣቂ ኃይሎች ከበባ ውስጥ ወድቆ ነበር፡፡ የእጅ ቦምቦችን ጨምሮ ሙሉ የጦር መሣሪያዎችን የታጠቁ የፌዴራል ፖሊስ አባላት ከታች ጦር ኃይሎች አቅጣጫ ጀምሮ የሕንጻ ኮሌጅና የፍርድ ቤቱን ኃላ ታክኮ እከከ ኮካ መገንጠያ ድረስ፣ በፊት አቅጣጫም ከአዋሽ ወይን ጠጅ ፋብሪካ ጀምሮ ልደታ ጋር ሲደርስ ወደላይ በሁለት አቅጣጫ በመከፈል ወደ ልደታ ቤተ ክርስቲያን እና ወደ አብነት የሚወስደው አቅጣጫ በታጣቂ ፌዴራል እና አዲስ አበባ ፖሊስ አባላት ተሞልቶ ነበር፡፡ በአማካይ በየሰባት ሜትር ርቀቱ በርካታ የፌዴራል ፖሊስ አባላት በአጀብ ቆመው ነበር፡፡ አካባቢውንም የጦር ቀጠና አስመስለውት ነበር፡፡ አንድ ታዛቢ እንደገለጸውም ከብረት ለበስ ወታደራዊ ተሸከርካሪ በቀር የቀረ አልነበረም፡፡
ይሄ ሁሉ ግርግር 11 የትግል ወራትን ላሳለፍነው ለኛ ሙስሊሞች በደንብ ይገባናል፡፡ የፖሊሶች ዓለማ አንድም ትንኮሳ መፍጠር ሁለትም በፍርሃት ሰው ሁኔታቸውን ተመልክቶ ወደ ቤት በፍርሀት እንዲመለስ ማድረግ፡፡ ይህን ድራማ ከአርሲ አሳሳ እስከ ደቡብ ወሎ ገርባ ተመልክተነዋል፡፡ ዛሬም ዓላማው ይህ ነበር፡፡ የፌዴራል ፖሊስ አባላት ገና ሻርፕ የለበሱ፣ ጂልባብ የተከናነቡ፣ ኒቃብ የለበሱ ሙስሊም ሴቶችን እንዳዩ የጭካኔ በትራቸውን ማወናጨፍ ጀመሩ፡፡ ከሴት ማኅጸን የወጡ የማይመስሉት ፌዴራል ፖሊሶች በሴት እህቶቻችን እና እናቶቻችን ላይ ያዘንቡ የነበረውን ዱላ የተመለከተ ተፈጥሮአቸውን ይጠራጠር ነበር፡፡ ፌዴራል ፖሊሶች መኪና እንዳይተላለፍ በማድረግ፣ ተላላፊውን ስም እየጠየቁ ሙስሊም መሆኑን ካረጋገጡ በመስደብ፣ በመምታት፣ በማሰር፣ የአካባቢውን የንግድ ሱቆች ሁሉ በግድ በማዘጋት፣ በፍርድ ቤቱ የመታደም መብት ያላቸውን ዜጎች ይህን እድላቸውን በመንፈግ፣ በፍርድ ቤቱ ጉዳይ ያላቸውም ግለሰቦች ወደ ውስጥ እንዳይገቡ በማቀብ ሽብር መፍጠርን ከንድፍ ሐሳብ በዘለለ መልኩ በተግባር ሲያሳዩ ነበር የዋሉት፡፡
የፌዴራል ፖሊሶቹ የፍርዱን ሂደት ለመከታተል እና በተግባር ይህ ሁሉ ድብደባ እየተፈጸመበት ያለውን ሰላማዊ ሕዝብ ሲመሩ ‹‹አሸባሪ›› ለተባሉት መሪዎቹ አጋርነቱን ለማሳየት የተገኘውን ሕዝብ ከቦታ ቦታ የመንቀሳቀስ ሕገ መንግስታዊ መብቱን በመንፈግ በዱላ እየደበደቡ ከአካባቢው እንዲርቅ ሲያደርጉ ወጪ ወራጁ ሁላ ታዝቧል፡፡ የእስልምና አለባበስ እና ምልክት ያለባቸውን መንድሞችና እኅቶች በየመንገዱ በማስቆም ይሰነዝሩት የነበረው ዘለፋ እና ዱላ አገሪቱ የሕግ የበላይነትን አሽቀንጥራ መጣሏን መስካሪ ነበሩ፡፡ ሙስሊምም ኢትዮጵያዊም መሆን አይቻልም የሚል የእጅ አዙር አዋጅ የወጣ ይመስል ለመንገደኛው ሙስሊም ሁሉ በተለይም ለሴት እኅቶቻችን እና እናቶቻችን ዛሬ ምላሻቸው ዱላ ብቻ ሆነ፡፡ በአካባቢው ድብደባ ከተፈጸመባቸው ውጪ በቁጥር በርካታ የሚሆኑ ሙስሊሞች በተለይም እኅቶች በፖሊስ ተይዘው ወደ አካባቢው ፖሊስ ጣቢያዎች ተወስደዋል፡፡ እንደ ፖሊሶቹ ምርጫ ከእነሱ ጋር ግብግብ እና ድንጋይ ውርወራ የሚገጥማቸው ጎረምሳ ነበር የሚፈልጉት – ግን አጡ፡፡ ሙስሊሙ በመሪዎቹ የታዘዘውን የሰላም ቃል ኪዳን ዛሬም አላጥፍም ብሏል፡፡ ነስሩ እየቀረበ ነው፡፡ የድል ወጋገን መውጣት ጀምራለች፡፡ አላህ ከእኛ ጋር ይሁን፡፡
አላሁ አክበር!!

No comments:

Post a Comment