Translate

Monday, December 31, 2012

ከእሁድ እስከ እሁድ


(የሳምንቱ አጫጭር ዜናዎች)

junedin and eprdf
ጁነዲንና ኢህአዴግ ፊርማቸውን ቀደዱ                                                                                                           
ከሚኒስትርነታቸውና ከኦህዴድ ስራ አስፈጻሚነታቸው በግምገማ እንዲነሱ የተደረጉት አቶ ጁነዲን ሳዶ ያለ መከሰስ መብታቸው ተነስቶ ክስ እንደሚመሰረትባቸው ሰንደቅ ጋዜጣ መዘገቡ ይታወሳል። ሪፖርተር በእሁድ እትሙ ጁነዲን ሳዶ ያለመከሰስ መብታቸው ለማንሳት ፓርላማው በዝግጅት ላይ መሆኑን ይፋ የምክር ቤት ምንጮቹን ጠቅሶ አስታውቋል።

ባለፈው ሐሙስ የዓመቱን ዘጠነኛ ስብሰባውን ያካሄደው የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በአምስት አጀንዳዎች ላይ ለመወያየት ፕሮግራም ይዞ የነበረ ቢሆንም፣ በአራቱ ላይ ብቻ ተወያይቶ የቀረውን ላልተወሰነ ጊዜ አስተላልፎታል፡፡ ሪፖርተር እንዳለው “የአንድ የምክር ቤት አባልን የሕግ ከለላ ስለማንሳት የቀረበ የውሳኔ ሐሳብን መርምሮ ማፅደቅ” የሚል  ቢሆንም፣ የምክር ቤቱ አፈ ጉባዔ አቶ አባዱላ ገመዳ ይህንን በቀጣይ ስብሰባ ለመመልከት ላልተወሰነ ጊዜ አስተላልፈውታል፡፡ ምክር ቤቱ በስምንተኛ መደበኛ ስብሰባው ቃለ ጉባዔ፣ በወንጀል ድርጊት የተገኘ ገንዘብ ወይም ንብረትን ሕጋዊ አስመስሎ ማቅረብንና ሽብርተኝነትን በገንዘብ መርዳትን ለመቆጣጠር የቀረበ ረቂቅ አዋጅና ሌሎች አዋጆችን ማጽደቁ ታውቋል።
አቶ ጁነዲን ይመልከት አይመልከት ባይታወቅም ከአልጀዚራ ጋር ቃለ ምልልስ ያደረጉት ጠ/ሚኒስትር ሃይለማርያም ደሳለኝ፣ ከሽብር ጋር በተያያዘ ባለስልጣንም ሆነ ማንም ከህግ በላይ አይደለም ማለታቸው ይታወሳል። አቶ ጁነዲን ባለቤታቸው ከሽብር ጋር በተያያዘ መታሰራቸው፣ እሳቸውም ባለቤታቸው በእናታቸው ኑዛዜ መሰረት መስጂድ ለማሰራት ከመንቀሳቀሳቸው ውጪ ሰሩት ጥፋት እንደሌለ ጠቅሰው በተለያዩ ጋዜጦች ማተማቸው አይዘነጋም። ሁኔታውን የሚከታተሉ አቶ ጁነዲንና ኢህአዴግ ፊርማቸውን ቀደዱ ብለዋል፡፡
ደህንነትና ጸረሙስና ሊቀናጁ ነው
የፌደራል የስነ ምግባርና የጸረ ሙስና ኮሚሽን በታላላቅ ፕሮጀክቶች ላይ የሚፈጸሙ ሙስናዎችን ለመመርመር ይችል ዘንድ ከብሔራዊ ደህንነት ኤጀንሲ ጋር በመቀናጀት የሚሰራ ግብረ ሃይል ለማቋቋም እየሰራ መሆኑን ሪፖርተር አስታወቀ። ጋዜጣው ምንጮቹን ጠቅሶ እንደዘገበው ትኩረት የሚደረግባቸው ዋና ዋና ዘርፎች መንግሥት ከፍተኛ ገንዘብ በመመደብ በሚያንቀሳቅሳቸው የኤሌክትሪክ ኃይል፣ የስኳር ፕሮጀክቶች፣ የባቡር መስመሮችና የተለያዩ የመሠረተ ልማት ግንባታዎች ላይ ነው።
በከፍተኛ ደረጃ ሙስና ቢስፋፋም ርምጃ ግን አይወስድም በሚል የሚታማው ኢህአዴግ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በሙስና ላይ ለመዝመት በተደጋጋሚ ዘመቻ እንደሚጀምር ቢያስታውቅም ተግባር ላይ ግን አይታይም። ጸረ ሙስና ኮሚሽን ሲቋቋም በተመሳሳይ ታላቅ ለውጥ ይመጣል ቢባልም ኮሚሽኑ የተጠበቀውን ያህል እንዳልሰራና በህወሃት ውስጥ ያሉትን ዋንኛ ሞሳኝ አሣዎችን ከማጥመድ ይልቅ ጥቃቅኑን ዓሣ በማጥመድ ትልቅ ሥራ እየተሠራ መሆኑን አሳማኝ አድርጎ ለማቅረብ የሚደረገው አግባብ እንዳልሆነ የሚወቅሱ አሉ።
የዩኒቨርስቲው ዲን ተማሪውን ደፈረ
በጎንደር ዩኒቨርሲቲ ተፈጸመ የተባለውን የአስገድዶ መድፈር ወንጀል ደብዛ ለማጥፋት ሲባል በተቀናጀ ሁኔታ የህክምና ማስረጃ እንዲጠፋ መደረጉን ዶቼ ቬሌ በሳምንቱ አጋማሽ ዘግቧል።ጉዳት የደረሰባት ተማሪ በደሏን ለሚመለከታቸው አካላት ብታቀርብም መፍትሄ አለማግኘቷ ታውቋል። አቤቱታዋን ካቀረበችበት ክፍል እስካሁን መፍትሄ አማግኘቷ አነጋጋሪ እንደሆነ ተመልክቷል።
ባለፈዉ ሕዳር መደፈሯ የተገለፀው ይህቺ ተማሪ በደሉ የደረሰባት በዩኒቨርሲቲዉ የተማሪዎች አገልግሎት ዲን በመሆኑ ጉዳዩ እንዲድበሰበስ አድርጎታል። ተፈፀመ የተባለዉን አስገድዶ የመድፈር ወንጀል ጥርጣሬ ደብዛ ለማጥፋት ተጎጂዋ ሃኪም ዘንድ የታከመችበትን ማስረጃ ሙሉ በሙሉ ማግኘት እንዳልቻሉ አንድ ስማቸዉ እንዳይገለጽ የጠየቁ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ለዶቼ ቬለ መግለጻቸው ታውቋል። እንዲህ ያለ አስነዋሪ ድርጊት ለሚፈጽሙ ወንጀለኞች መረጃ በማሸሽና በመደበቅ በሚተባበሩ የህክምና ባለሙያዎች ላይ ማህበረሰቡ ሊያወግዛቸውና በ“ህግ” ሊጠይቃቸው እንደሚገባ አስተያየት ተሰጥቷል።
ወሮበሎች የደፈሯት ወጣት አረፈች
በህንድ ኒዉዴሊ አስራ ሁለት ወረበሎች የደፈሯት ወጣት አረፈች። ወጣቷ ህይወቷ ያለፈው ለህክምና ሲንጋፖር ከሄደች በኋላ ነው። የሃያ ሶስት ዓመቷ ወጣት ህልፈትን ተከትሎ በህንድ ከፍተኛ ቁጣና ሃዘን ተቀስቅሷል። በአደባባይ ለተቃዉሞ የወጡ ሰልፈኞች ሟች ፍትህ እንድታገኝ እና በአገሪቷ የሚታየዉ ከፍተኛ የወሲብ ጥቃት እንዲቆም ጠይቀዋል።
ወጣቷ  ከሁለት ሳምንት በፊት በኒዉዴሊ አዉቶቡስ ዉስጥ ተሳፍራ ሳለ በስድስት ወንዶች በብረት ዱላ ተደብድባና ተደፍራ ከአዉቶቡሱ መወርወርዋ በተለያዩ መገናኛዎች ነው የተጠቆመው። አሰቃቂ የወሲብ ጥቃት የተፈፀመባት ወጣት በዉስጥ የአካላ ክፍሏ ላይ የደረሰባትን ጉዳት  የህክምና ባለሞያዎች ለማዳን ያደረጉት ጥረት ባለመሳካቱ ህይወቷ ሊያልፍ ችሏል። በወጣቷ ላይ የደረሰውን አደጋ ተከትሎ በርካታ ሴቶች አደባባይ በመውጣት ሴቶች የተሻለ መብት ሊኖራቸው እንደሚገባ  ጠይቀዋል። በዋና ከተማዋ ኒዉዴሊ የተቃዉሞ ሰልፉን ተከትሎ ከፍተኛ የፀጥታ ሃይላት በየመንገዱ የተሰማሩ ሲሆን፤ የከርሰ ምድር የህዝብ ማመላለሻ ባቡሮች መዘጋታቸዉ ታዉቋል። ከአንድ ሳምንት በፊት የወሲብ ጥቃት የተፈጸመባትን ወጣት በማስመልከት በተነሳዉ ከፍተኛ ተቃዉሞ ሰልፍ በሰዎች ላይ ጉዳት ደርሷል።  አንድ ጸጥታ አስከባሪ ፖሊስ ህይወት አልፏል።
በዩኒቨርስቲ አማርኛ ፊደል ለይተው የማያውቁ አሉ
በኢትዮጵያ የአንደኛ ደረጃ ትምህርት ቁልቁል እየተጓዘ የት እስኪደርስ እንደሚጠበቅ ግራ እንደገባቸው በአዲስ አበባ የሳይንስ አካዳሚ ምሁራን አመራሮች ባጠኑት ጥናት አስታወቁ። ጥናቱ በትግራይ፣ በአማራ፣ በደቡብ ክልልና፣ በኦሮሚያበተመረጡ አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ላይ የተካሄደ ሲሆን፣ የአሜሪካ ሬዲዮ ዘጋቢ እንዳስታወቀው ችግሩ የነበረ፣ ያለና ወደፊትም የሚኖር ነው። ከአጥኚዎቹ መካከል ፕ/ር ፉርዳሳ ጀቤሳ “ትምህርቱ እያሽቆለቆለ ሄዷል፤ ወድቋል” ሲሉ፣ ፕ/ር ባዬ ይማም በበኩላቸው “አማርኛን በዋና ትምህርትነት ለማጥናት ከሚመጡ የዩኒቨርስቲ ተማሪዎች መካከል ፊደል ለይተው የማያውቁ አሉ” ብለዋል። “ሳ” እና “ሶ” መለየት አቅቷቸው የሚጠይቁ እንዳጋጠሙዋቸው ተናግረዋል። ችግሩ በኦሮሚኛ ቁቤ ትምህርትና በትግርኛ ላይም እንዳለ አረጋግጠዋል። በጥናቱ ላይ የተገኙት የትምህርት ሚኒስትር ተወካይ “ችግር ቢኖርም በጥናቱ እንደተቀመጠው አይደለም” ሲሉ ተቃርነዋል።
በጥናቱ እንደተገለጸው ተማሪዎችን በማደራጀት፣ስብሰባ በመጥራት፣ሪፖርት እንዲጽፉ በማድረግ ዋናውን የክህሎትና አመለካከት የማሳደግ ስራ እንዲዘነጋ ተደርጓል።ችግሩም በከፍተኛ ደረጃ አሳሳቢ አንደሆነ ተጠቁሟል፡፡
በደቡብ አፍሪካ ኢትዮጵያዊያን 30ሺህ ትኬት ገዙ
ደቡብ አፍሪካ በሚዘጋጀው የአፍሪካ ዋንጫ ተሳታፊ የሚሆነውን የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ለመደገፍ ትኬት የቆረጡ ኢትዮጵያዊያን ቁጥር ክፍተኛ መሆኑ ታወቀ። የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌደሬሽን/ካፍ/ የውድድር አዘጋጅ ኮሚቴ እንዳስታወቀው በአንደኛ ደረጃ በርካታ ትኬት የገዙት የዛምቢያ ደጋፊዎች ሲሆኑ 50ሺህ ቲኬት ገዝተዋል። ደቡብ አፍሪካ የሚኖሩ ኢትዮጵያዊያን 30ሺህ ቲኬት በመግዛት ሁለተኛ ደረጃ ሲይዙ፣ የአልጄሪያ ደጋፊዎች 15 ሺህ ቲኬት በመግዛት የሶስተኛ ደረጃ ይዘዋል።
ከሰላሳ አንድ ዓመት በኋላ ወደ አፍሪካ ዋንጫ የገባው የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን አባላት ለውድድሩ ብቁ መሆናቸው ከተረጋጋጠ በኋላ የሚቀርብላቸው ውዳሴና ሙገሳ ስለበዛ እንዳያዘናጋቸው ስጋት የገባቸው ወገኖች ሚዲያዎች መረጃና ጠቃሚ ሃሳብ በመስጠት አገራዊ ግዳጃቸውን ያለ ይሉንታ ቢወጡ እንደሚሻል ጠቁመዋል። ለመወዳደሱ ከውድድሩ በኋላ በቂ ጊዜ እንዳለ የሚጠቁሙት ክፍሎች ሁሉም ሚዲያዎች ተመሳሳይ አቋም በመያዝ የድግስና የሽልማት ወሬ ላይ ተጠምደዋል። ቡድኑ ከባድ ሽንፈት ቢገጥመው እነሱም ከመወቀስ አያልፉም ብለዋል። ጋዜጠኛ ከተስካርና ከድግስ ወሬ ይልቅ ቡድኑን ሊጠቅሙ የሚችል መረጃ ወደመስጠት ሊያተኩሩ ይገባል ብለዋል።

No comments:

Post a Comment