Translate

Thursday, August 16, 2012

መለስ ዜናዊ ከነጥፋት ውሃው ሲታወስ


በተለምዶ ሰው የዘራውን ያጭዳል ይባላል:: ከመልካም ዘር ደግ ነገር ይመረታል እጸበለስን የዘራ መርዝን ያመርታል:: ይህ በሰው ህይወት  ዘመን ሁሉ ተፈጻሚ ነው:: ከእባብ ግንEthiopian pm Meles Zenawiየርግብ እንቁላል አይጠበቅም:: መለስ የተባለ ሰው በወጣትነት ዘመኑ ጥሩ የትምህርት ዘር ዘርቶ በታወቀው የጀነራል ዊንጌት ሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን እንዳጠናቀቀ ይነገራል:: ከዛም በቀዳማዊ ኅይለሥላሴ ዩንቨርሲቲ የህክምና ትምህርት ሲከታተል ቆይቶ እስከሁለተኛ ዓመት ድረስ ዘልቋል:: እስከዚህ ጊዜ ድረስ መልካም ዘር የዘራበት ነበር ማለት ይቻላል:: መጥፎ ዘር መዝራት የጀመረው የከፍተኛ ተቋም ትምህርቱን አቋርጦ ጫካ ከገባ በኋላ  ይመስላል:: የጥፋቱ መጠንና ዓይነት ዘርፈ ብዙ ስለሆነ ዘርዝሮ መጨረስ አስቸጋሪ ይሁን እንጂ አያዳግትም:: ስለሆነም  አንኳር አንኳር የሆኑትን የጥፋት ዘሮች እንደሚከተለው እንዳሳቸው::

በዱርቤቱ  የዘራው
ለአስራ ሰባት ዓመታት ያህል ተንኮል እየቀመመ በጓዶቹ ላይ ዘመተ:: የንጹሃን ጓደኞቹን ሕይወት በቀጥታም ሆነ በተዛዋሪ ቀሰፈ አስቀሰፈ:: በኢትዮጵያና በትዮጵያዊነት ላይ መጠነ ሰፊ የሆነ ደባ ፈጸመ:: የትግል አጋር የሆኑትን የኢሃፓ ወጣቶች ጨፈጨፈ አስጨፍጨፈ:: በመርህና በአቋም ደረጃ በአማራው ላይ እንዲዘመት ድርጅቱን አስተምሮና መከሮ በተግባር ፈጸመ:: በተረ መንግስት ለመያዝና የጥፋት ውሃውን እንደፈለገው መርጨት እንዲአመቸው ባደረገው ትግል የብዙ ሰው ሕይወት ቀሰፈ:: የሃገር የሕዝብና  የግለሰቦችን ሃብትና ንብረት አወደመ:: ወጣት ልጆችን ወደ ሽፍትነት እንዲቀላቀሉ እየመለመለ የሳት እራት አደረገ::  በተለይም የጎንደርንና የትግራይን ወላጆች ልጃ አልባ አደረገ አስደረገ::
የኢትዮጵያን የሃገር አንድነት የሚአፈራርስ ደባና ተንኮል ሸርቦና አስተምሮ አስራሰባት አመታት ታገሎ አታገለ:: የሞት ሽረት በሚጠይቅ ውጊያና ጦርነት ሁሉ ጓዶቹን አጋፍጦ የሚሸሽ ፈሪ ፋኖና ታጋይ እንድሆነ ይታወሳል:: በለመደው የሽሽት ባህሪው አገር የመምራት ሓላፊነት የነበረው ሰው የት እንደፈረጠጠ ለትግል ጓዶች እንኳን ሳይነግር ሁለት ወራትን አስቆጠረ::
በሚኒሊክ ቤተመንግስት
በጫካ ቤተመንግስቱ የሰራው ደባና ተንኮል ጎምርቶ የሃገርመሪነትን ስልጣን ከወሰደ በኋላ ለኢትዮጵያና ሕዝቧ እድገትና ልማት ከማምጣት ይልቅ ሕዝብን ከሕዝብ በጎሳ በሃይማኖት በቀየ በዘር ሃረግ ሸንሽኖ በሕግ ሽፋንና በአዋጅ እያደናገረ እርስበርሱ እንዲፋጅ[2] የጥፋት አውታሩን በመላ አገሪቱ ዘረጋና ተገበረ:: አንዳንድ ሰወች መንግስቱ በሰው ላይ ዘመተ መለስ ግን በከፋ ደረጃ በሰውና በሃገር ላይ ዘመተ:: ሰው መግደል በማንኛውም መመዘኛ የሚወገዝ ቢሆንም ሰው ቢሞት ሰው ይተካል ተብሎ ሊታሰብ ይችላል:: ሰውንና አገርን መግደል ግን ከሁሉ የከፋ ነው:: ምክንያቱም አገር ከሞተ እትዮጵያዊነትም አብሮ ስለሚሞት ዘላለማዊ ሞት ይሆናል:: ከሞቶች ሁሉ የከፋ ሞት የሚሆነው ሁለቱም ሲሞቱ ነው::
የኢትዮጵያን አንድነትና ሉዓላዊነት አስደፍሮ አገሪቱን ለዓለምና ለራሱ ቡችሎች መሳለቀያ አደረገታ:: ኤርትራን ከናት አገሯ አስገንጥሎ አገሪቱን ወደብ አልባ አደረገ:: መሬቷን እየቆረሰ ለባእዳን አገሮች አስረከበ:: የራሱን ክፍለሃገር ትገንጠልልኝ መሬቷም ተቆርሶ ለጎረቤት አገር ይሰጥልኝ ብሎ የተባበሩት መንግስታትን የጠየቀና ያስፈጽመ የሃገር መሪ   የሃያአንደኛው ክፍለ ዘመን ብቸኛ ሻምፒወና ሆኖ በታሪክ የበቃ ሆኖ ተመዘገበ:: የሃገሪቱን አንጡራ ሃብት ከነግብረ አበሮቹ ዘርፎና አዘርፎ ለራሱ ጎሳና አዎራጃወች መጠቀሚያ አስደረገ::
መርዝ መትፋት በተካነው ምላሱና አንደበቱ የኢትዮጵያን ህዝብ ከተራ ዱርየ በማይተናነስ ደረጃ  እየተሳደበ አዋረደ:: የሃገሪቱን ባንዲራ ተራ ጨርቅ ብሎ በማዋረድና በማቆሸሽ ተሳለቀ:: ሌላውን ብሔረሰብ ደንቆሮ አድሃሪ አህያና ደድብ ብሎ ተሳደበ አሰደበ:: በአንጻሩ እርሱ የፈለቀበትን ብሔረሰብና ጎሳ ወርቅ በማለት ከዚህ ወርቅ ብሔረሰብ መወለዱን እያወደሰ ሌላውን የኢትዮጵያ ሕዝብ ግን መዳብ ብሎ ተሳለቀበት :: ሚስቱንና ሌሎች ባለስልጣናትን[3] መጠቀሚያ እያደረገ የሃገሪቱን አንጡራ ሃብት ወደ ውጭ ሃገር አሸሸ አስሸሸ::
ኢትዮጵያዊነት በምታስተምረዋ የኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያንና  ተከታዮቿ ላይ ሌሎች ሃይማኖቶች እንዲዘምቱባትና እንድትዳከም በቀጥታም ሆነ በተዛዋሪ ፈቃድ ሰጦና አስተባብሮ አስዘመተባት::  ቤተክርስቲአኗን ማጥፋት ቢአቅተውም በእጅጉ እንድትዳከም አደረገ:: ይህ አልሳካ ቢለው የመንግስት አውታሩን ተጠቅሞ በገዳማቷና በመነኮሳቷ ላይ ቀጥተኛና ኦፊሳላዊ ዘመቻ አደረገ[4]:: በተግባርም ፈጸመ::
የተቃዋሚ ፖለቲክ ድርጅቶችን አጥፍቷል መሪወቻቸውን አስሯል ገሏል::የታወቁት የቀዶ ጥገና ሃኪም ፕሮፌሰር አስራትን አስገደለ::  የሲቢክ ማህበራትን አጥፍቷል ወይም እንዳይንቀሳቀሱ አሽመድምዷቸዋል:: በጸረሽብርተኝነት ስም በእስልምና ሃይማኖት ተከታዮችና በነጻ መገናኛ ብዙሃን ላይ መጠነ ሰፊ አፈና ግድያና እስራት ፈጽሟል::
ሰላማዊ የፖለቲካ ታጋዮችን በግፍ አሰረ:: ሰላማዊ ሰልፈኞችን ከናዚ ጭካኔ ባልተናነሰ ሁኔታ ጨፈጨፈ[5]:: ንጹሃን ጋዜጠኞችን የውሸት ወንጀል በጓዳው እየፈለፈለና የሃሰት ምስክሮችን በማባበል አለያም በማዘዝ አለያም በማስፈራራት እያስመሰከረ አሳሰረ ገደለ ወይም ከሃገር አሰደደ:: በጋምቤላ በንጹሃን ዜጎች ላይ የዘር ማጥፋት ወንጀል ፈጸመ አስፈጸመ:: በአርባ ጉጉ ንጹሃን የአማራ ዜጎችን በራሱ ቀጥተኛ ተእዛዝ አስጨፈጨፈ[6]:: ህጻናትን እናቶችንና አረጋዊያንን ከነሕይወታቸው ወደ ጉድጓድ አስወርውሮ በሚዘገንን ሁኔታ ያስገደለ የዲአቢሎስ ዋና ተምሳሌት ሆነ:: በኦሮሞና በኦጋዴን ህዝብ ላይ መጠነ ሰፊ የሆነ የዘር ማጥፋት የግድያና የእስራት ግፍ ፈጽሟል[7]::
በሲዳሞ ክፍለሃገር ጉራፈርዳ በተባለ አካባቢ ሰፍረው ንብረትና ቤተሰብ መስርተው ከአካባቢው ህዝብ ጋር ተዛምደውና ተጋብተው በሰላም ይኖሩ የነበሩትን አማር ሰፋሪወች አፈናቀለ:: ይህን እኩይ ተግባር በጋሻጃግሬውና የክልሉ ፕሬዚደንት በሆነው በሽፈራው ሸንቁጤ ኦፊሲአላዊ ትእዛዝ  ሃብታቸውን ዘረፈ አስዘረፈ:: ቤት ንብረታቸውን አቃጥሎ አረመኔአዊና ኢሰባዊ ወንጀል ፈጽሟል[8]:: ወደ መጡበት ጎጃምና ሸዋ ክፍለሃገር በብዙሺ ኪሎሜትር በእግራቸው አስጉዞ መልሷል:: ወጣቶችንና ህጻናትን ከትምህርት ገበታቸው አፈናቅሏል::
ከአፓርታይድ ባልተናነሰ ደረጃ የተለያዩ የትምህርት ፓሊሲወችን እይቀየሰ በየክፍለሃገሩ ወጥነት የሌለው መርሃግብር እየዘረጋ በተግባር ፈጽሟል አስፈጽሟል:: ለምሳሌ በትግራይ ክልል ወጣቶች የሁልተኛ ደረጃ ትምህርታቸውን የሚአጠናቅቁት ከአስራሁለተኛ ክፍል ሲሆን በአማራው በደቡቡና በሌሎች ከልሎች ከአስረኛ ክፍል እንዲ ጨርሱ በማድረግ የትምህርት አፓርታይድ ፕሊሲ ፈጽሟል:: በአማራው ክልል አደንዛዥ እጾች በተለይም የጫት ምርትና አጠቃቀም እንዲስፋፋ በማድረግ የወጣቱን ዐእምሮና ባህል እንዲላሽቅ ብሎም የባለስልጣናቱ ሃብት እንዲዳብር አድርጎ በትግራይ ክልል ግን ይህን በመመሪያ ከልክሏል::
የመለስና ግብረአበሮቹ ድርጊትና የጥፋት ዘር ተዘርዝሮ የማያልቅ ስለሆነ ሾላ በድፍኑ ሳይሻል አይቀርም[9]:: ባጭር ቋንቋ ግን ግለሰቡ የተዋጣለት ዲአቢሎስ ነበር ቢባል ሲአንሰው እንጅ ማጋነን አይሆንም::ይህ ሁሉ ግፍ የተፈጸመበት ሕዝብና አገር ግን  ፊቱን ወደሰማይ እያቀና ፈጣሪውን ሲለምን ኖረ:: በደም እንባ የታጠበውም ሕዝብ ፍርዱን ለእግዚአብሔር በመተው እየጸለየ ከእጅ ወደ አፍ ኑሮውን ቀጠለ:: ጸሎትና ልመና የሕዝብ ፍርድ ግን የእግዚአብሔር ነውም አለ::ይህን ሁሉ የዲአቢሎስ ተግባር የፈጸመ ሰውየ ግን መንገዶች አዝርግቷል ጤና ጣቢያወች አስፋፍቷል የትምህርት ደረጃው ያዘቀጠ ትምህርት የሚስፋፋባቸው ትምህርት ቤቶችን ገንብቷል:: በየከተማው ፎቆች ቆልሏል:: ድህነት ርሃብ ኋላቀርነት ስራአጥነትና ቦዘኔነት ግን ስርሰዶ ተስፋፍቷል:: በአንደበተ ረእቱነቱና የመረጃ አሃዞችን (statistics) እንደፈለገው መፈብረክ ባለው ብቃት  ሲታወስ ይኖራል::
የጫትና የካናቢስ ተጠቃሚነት ግብረሰዶምን የአስረሽ ምችው የእርቃን መጨፈሪያ ቤቶች  ተስፋፍተው የወጣቱን ስነልቦና ባህል የሚበክሉ ገጸባሃሪያት በአብዛኛው የሃገሪቱ ክልሎች  እንዲስፋፋ አድርጓል:: በአንጻሩ ግን እርሱ ከወርቅ ለሚአመሳስለው ህብረተሰብ ግን እንደዚህ ዓይነት ምግባረ ብልሹ ባህሪያት እንዳይካሄዱ በመመሪያና በተእዛዝ አግዷል::  በዚህ ስራው የአፓርታይድ ፖሊሲውን ምንነት በተጨባጭ ደግሞ ደጋግሞ አስመስክሯል:: ለዚህ እኩይ ስራው አንዳችም የመጸጸት ስሜትና ባህሪም አላሳየ:: በተለይ የአደንዛዥ እጽ ተጠቃሚነትን በግንባር ቀደምትነት አራያና ተጠቃሚ እራሱ በመሆን ለሕዝቡና ለቤተሰቡ አስተምሯል:: በማንኝውም መመዘኛ የሃገር መሪነት ባህሪ ሳይሆን የተራ ወሮበላና የሽፍታ ስራን በሃገራችን ላይ ለ37 ዓመታት በተቀነባበረ መልኩ ሲተገብር የኖረ በመሆኑ ይታወሳል::
በባድሜ ጦርነት አማራውንና የሌላው ጎሳ ሰራዊት ከፊት ለፊት አሰልፎና አዝምቶ በማስጨፍጨፍ የኤርትራን ጦር አሸንፎ ትግራይን ከውድመት አድኗል:: ከሰባ ሽህ ሕዝብ በላይ በጦር ሜዳ ማግዶና አስጨርሶ የተገኘውን ድል በዓለም አቀፍ ደረጃ ተስማምቶ ሕዝቡ ተዋድቆ ያዳናትን ባድሜንና ሌሎች መሬቶችን ለኤርትራ አስረከበ:: ውጤቱ ይህ መሆኑን እያወቀ ለምን የኢትዮጵያን ህዝብና ሰራዊት ያስጨረሰበትን ምክንያት የሚአውቀው እሱና እራሱ  ብቻ ነው:: አሁን መለስና ግብረአበሮቹ የዘሩትን ከሚአጭዱበት ወቅት ላይ ደርሰናል:: መለስ ያጨደውን ግን ሳይከምርና ሳይወቃ ምርቱንም ሳይበላ ሊአልፍ በቋፍ ላይ ይገኛል::
በኢትዮጵያሕዝብዘንድየሚታወሰውስበምን
ዛሬ ከ38 ዓመት በኋላ በምንም ምክንያት ይሁን በምን ዓይኑ ተሰውሮ በሞት አፋፍ ላይ  እንደሆነ ወይም እንደሞተ ይወራል:: ይህ ዜና እውነት ሊሆንም ላይሆንም ይችላል:: በአንድ ነገር ግን እንስማማለን:: ፈጠነም ዘገየም መሞቱ አይቀርም:: የሚአሳዝነውና አስቸጋሪ የሚሆነው ግን ያቆሸሸውን ለማጽዳት የተከለውን አሜኪላ ለመንቀል ብሎም ለማስወገድ ብዙ ጊዜና ትውልድ መፍጀቱ ነው:: ሙት ይዞ ይሞታል ማለት ይህ ነውና::
ታሪክና ህዝብም እሱን ማስታወሱ አይቀርም:: በምን እንደሚታወስ ግን ለሁላችንም ግልጽ ሆኖ የሚታወሰን ይህ ሰው በኢትዮጵያ ምድርና በሕዝቧ ላይ ወደር የሌለው የጥፋት ዘር የዘራ ሰውም አገርም በማጥፋቱ የታወቀ የዘመናችንና የአሃጉራችን የለየለት አጥፊ ሆኖ በኢትዮጵያዊያን ዘንድ ሲታወስ ይኖራል:: ለሃያ አንድ ዓመታት በስልጣን ላይ ለአስራ ሰባት ዓመታት በሽፍትነት በኖረበት ዘመን ሁሉ ከመልካም ምግባር ይልቅ የጥፋት ውሃን ሲረጭና ሲአስረጭ ከጠቅላላው ሕይወቱ ውስጥ 67% በመቶውን የጥፋት የተንኮል የእብሪትና የግድያ ዘርን በመዝራቱ ይታወሳል:: ሁለተኛ እድል ቢሰጠው ይህን ተግባር በተጠናከረ መልኩ ለመፈጸም ወደኋላ የሚል ዓይነት ሰውም አይመስልም::
በአንጽሩ የኢትዮጵያም ሕዝብ ለዘመናት ሲዘራው (እስላሙና ክርስቲያኑ ሁሉም በአንድነት) የኖረው የጥሩ ሕዝብ ስነምግባርንና ፈሪሃ እግዚአብሔርን ነበር:: ስለሆነም ጥኋት ማታ ጸሎቱን ለሃያሉ እግዚአብሔር ሲአቀርብ ኖረ :: ጌታም ጸሎቱን ሰምቶ የበደሉትን ሁሉ የቀጣለት መሆኑን ሁልጊዜ ሲአስታውሰው ይኖራል:: ኢትዮጵያም እጆቿን ወደ እግዚአብሔር እንደዘረጋች ትቀጥላለች:: ነጻነቷንና ሙሉ ኩራቷን ከነውበቷ የምትጎናጸፍበት ጊዜ ከመቸውም በላይ ቅርብ ሆኖ ይታየናል::
ከላይ የተጠቀሱት ዘርፈብዙ ወንጀሎቹና ግፎቹ እጅግ የሚዘገንኑ በመሆናቸው የሰብዓዊ  አዘኔታችንን አሟጦ ወስዶብናል:: ቅዱስ መጽሓፍ የሚአደርጉትን አያውቁምና ይቅርበሏቸው ብሎ አስተምሮናል:: ከዚህ አንጻር ይቅር ለማለት ሊከጅለን ይችል ይሆናል:: መለስ ግን የሚአደርገውንና የሚሰራውን ጠንቅቆ የሚአውቅ ለጥፋት ዘሩም ልዩ ቀመር ተጥቅሞና አስተባብሮ የፈጸመ ያዋቂ አጥፊ ለመሆኑ ምንም ብዥታ ሊኖር አይገባም::
ስለሆነም አቶ መለስ ታሞም ከሆነ እግዚአብሔር ምረቱን ይላክለት ሞቶም ከሆነ አፈሩን ያቅልለት:: በየትኛውም አቅጥጫ ይሂድ መንገዱን ጨርቅ ያርግለት ከማለት በስተቀር እንባ ሊወርደን ደረት ሊአስመታን የሚችል አይሆንም::
ሁላችንንም የነገ ሰው ይበለን
ነሃሴ 8, 2004

[1] በሃገራችን ባህል አንድ ሰው አንቱ ተበሎ የሚጠራበት ባህሪያት አሉት::  በእድሜው ጠና ያለ በከፍተኛ የመንግስትና የህዝብ ወንበር ላይ ተቀምጦ ሕዝብን የሚመራና የሚአስተዳድር  በእድሜው ትልቅ ያልሆነ ግን ጥሩ ስራና መልካም ግብረሰናይ ያለው ከሆነ ብዙ የማያቁትን ሰው ድንገት ካገኙት ወየም ከተዋወቁት አንቱ ተብሎ ይጠራል:: መለሰ ይህን ጸሓፊ በድሜ አይበልጠውም በስልጣኑ ግን ከፍተኛ ቦታ ላይ ያለ ስለሆነና ከጸሓፊው ጋር በአካል ስለማይተዋወቅ አንቱ ብሎ መጥራት ባስፈለገኝ ነበር:: የመለሰን ገጸባህሪያት ስመረምረው ግን አንቱ ብዬ በዚህ ጽሁፌ መግለጽ ስለተሳነኝ አንተ እያልሁ እንድጠራው ተገድጃለሁ:: ይህን ባደርግ እራሴንና አንባብያን እንደአታለልሁና እንደዋሸሁ ተሰማኝ ነው:: መንግስቱ ሃይለማርያምን አንተ እያልን የምንጠራው በገጸባህሪያቱና በድርጊቱ ነው:: እንዳውም ሁለቱ የኢትዮጵያ የጥፋት መሪወች ሲመዛዘኑ ማን  ለአንቱታ ሚዛን እንደሚደፋ ፍርዱን ለአንባቢያን እተዋለሁ::  መለስን አንተ ብየ በመጥራቴ አንባቢያንን ከወዲሁ ይቀርታ እጠይቃለሁ::  ይቅርታ የምጠይቀው ለአንባቢያን ካለኝ አክብሮት የተነሳ እንጅ በድርጊቴ ከመጸጸት የመነጨ እንዳልሆነ እንድትረዱልኝ አሳስባለሁ:: ባህሌን የሃገሬን ወግና ስርዓት አውቃለሁ ብዬ የማስብ ሰው ነኝና::
[2] http://www.cyberethiopia.com/warka4/viewtopic.php?p=472227&sid=af0271c2a572a0b1513712c47ab57639
[4] http://www.ethiotube.net/video/13233/-Must-Watch–Woyane-incited-killing-in-Jimma
[5] http://www.youtube.com/watch?v=FE3Nn6qWDVk
[6] http://www.youtube.com/watch?v=Ead0CJkviHk
[8] http://ecadforum.com/2012/04/05/ethiopia-a-campaign-of-ethnic-cleansing-against-amhara-voa/
[9] http://arefe.wordpress.com/2012/03/25/amharas-forcefully-evicted-from-guraferda/

No comments:

Post a Comment