Translate

Wednesday, August 29, 2012

እንግዲያስ የመለስ ገዳይ ማነው… ኢህአዴግ አይደለምን!?


ለጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ህመም ዋና ምክንያት ሆኖ ከመንግስት ባለስልጣናት የተነገረን “የስራ ጫና እና ረጅም ግዜ የቆየ የስራ ኃላፊነት ነው።” እኛም አምነናቸዋል። እንኳንስ ይሄንንና “መለስ ከመስከረም በፊት ይመጣል” ሲሉም “አምነናቸዋል” እነርሱም የሚሆነውንም የማይሆነውንም ነገር የሚነግሩን “እንደምናምናቸው” ርግጠኞች ስለሆኑ ነው። ታድያ ለምን እናሳፍራቸዋለን…!? “እንመናቸው” እንጂ!
ሰባኪው ኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ስብከቱን ቀጥሏል።
“መለስ ጌታ ነው!” እያለን ይገኛል። “ሁሉ በእርሱ ሆኗል።”  በማለትም የተለያዩ “ማስረጃዎችን” ሊነግረን እየተጋ ነው። እንግዲህ የዚህ ጥቅሙ ምን ይሆን!? በስማቸው ቤተስኪያን እንድናቋቁም ታስቦ ይሆንን? ግራ ነው የሚያጋባው፤ ብቻ የሆነው ሆኖ በኢትዮጵያችን የሁሉ ነገር ፈላጭ ቆራጭ መለስ እንደነበሩ ቴሌቪዥናችን አረጋግጦልናል።

ግድብ ሰሪው መለስ፣ ጤና ኤክስቴንሽን ሰራተኛው መለስ፣ የትምህርት ፖሊሲ ቀራጩ መለስ፣ መንገድ ዘርጊው መለስ፣ ህንፃ አናፂው መለስ ጥቃቅን እና አነስተኛ አደራጁ መለስ በአጠቃላይ በሀገሪቱ ውስጥ የተደረጉት እንቅስቃሴዎች በሙሉ ሲሰሯቸው እና ሲያቅዷቸው የነበሩት መለስ እንደነበሩ ኢቲቪ ደጋግሞ እየነገረን ነው።
አሰብኩት ለሃያ አንድ አመታት በሁሉም ነገር ላይ ፈላጭም ቆራጭም ሆኖ መቆየት ምን ያህል አድካሚ እንደሆነ በደንብ አሰብኩት “ሳስበው ሳስበው ደከመኝ”
አለም አቀፍ ተሸላሚው ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ በአንድ ወቅት የፖሊስ ኮሚሽነሩ ጠርተው “አንተን ማሰር ሰለቸን” ያሉት ለጠቅላይ ሚኒስትሩ አንድ ግልፅ ደብዳቤ በላከ በጥቂት ቀናት ውስጥ ነበር።
እስክንድር በግልፅ ደብዳቤው ላይ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከስልጣናቸው በአስቸኳይ እንዲለቁ መክሯቸው ነበር። እንደ እስክንድር አባባል “ጠቅላይ ሚኒስትሩ ይሄንን ያህል ጊዜ በስልጣን ላይ መቆየታቸው የፈለገ “እውቀት ጢቅ” ቢሆኑ በጊዜ ብዛት አዕምሯቸው ደክሞ ስራቸውም ላይ ጤናቸውም ጉድለት ማምጣቱ እንደማይቀር በማስታወስ ነበር።
ይኸው እስክንድር “እረፉ” ሲላቸው አልሰማ ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትር እግዜሩ ሲላቸው ግን በግድ አረፉ! ለመሆኑ ለዚህ ተጠያቂው ማነው? ያለን እንደሆነ ሁሉንም ስራ ካልሰራሁ ብለው መከራቸውን ሲያዩ “ተው የስራ ክፍፍል እናድርግ… ይሄንን ለኛ ተውልን… ግዴየለህም…” ማለት የተሳናቸው የኢህአዴግ አባላትን አናገኛለን።
ኢህአዴግ ድርጅቱ እና አባላቱ አውቀው ወይም ሳያውቁት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ላይ ስራ ሲከምሩባቸው ነበር። እርሳቸውም “አይ ይሄንንማ እናንተው ስሩት” ብለው ሳይሉ ወይ ትህትና ይዟቸው፣ ወይ ደግሞ “ከኔ በላይ ላሳር” ባይነት ይዟቸው የመጣውን ስራ ሁላ ሲያስኬዱ ይኸው የስራ ክምር ለሞት አበቃቸው።
እንግዲህ ይህንን ሁሉ የምንለው ኢህአዴግን ይበልጡንም ደግሞ አቶ በረከትን አምነን ነው ጠቅላይ ሚኒስትሩ የታመሙት “ረጅም ጊዜ በቆየ የስራ መደራረብ የተነሳ ነው” ብለውናል።  እኛም አምነናል።
አንድ ዋና የሚባል ከእኛ የበለጠ የጠቅላይ ሚኒስትሩ አሳቢ በፌስ ቡክ ግድግዳው ላይ የለጠፈውን ስናይ በርካታ የኢህአዴግ አባላት በነገሬ እንደሚስማሙ ያሳያል ምን ይላል መሰልዎ “እንደሸንኮራ መጠው ለሞት አበቁት ወንድሜ ትንሽ ቢያርፍ ምን ነበረበት?” ብሎ ጥያቄ ምልክት ጨመርመር አድርጎ ቁጭቱን ተናግሯል።
እንደ አውነቱ ከሆነ እርሳቸውም ቢሆኑ በራሳቸው ላይ ያንን ሁሉ ስራ መቆለል አልነበረባቸውም። (ለአሁኑ ግን እርሳቸው ገና አፈር ያልቀመሱ ሙት ናቸውና ወቀሳውን እናቆይላቸው) ድርጅታቸው ኢህአዴግ ግን ይሄንን ሁሉ ስራ ሲሰሩ “ተዉ…” ብሎ ሊገመግማቸው ይገባ ነበር። ነገር ግን ይህን አላደረገም። በዚህም የተነሳ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በስራ ናዳ ለሞት በቁ!
እንግዲያስ የጠቅላይ ሚኒስትሩ ገዳይ ማነው!? ኢህአዴግ አይደለምን!?

No comments:

Post a Comment