Translate

Saturday, August 25, 2012

ከአምባ ገነን ወደ “እንባ” ገነን!


ዘኢኮኖሚስት የተባለው ታዋቂ የእንግሊዘኛ መፅሔት የተከበሩ ሟች ጠቅላይ ሚኒስትራችንን “አምባ ገነንነት ተቀባይነት እንዲያገኝ ሲሰሩ የከረሙ ሰውዬ” ሲል ዘክሯቸል።
በነገራችን ላይ ይህ መፅሔት አቶ መለስ ዜናዊ “ከአዲስ ራዕይ” ቀጥሎ በጣም የሚወዱት መፅሔት እንደሆነ በአንድ ወቅት በገደምዳሜ ነግረውናል።
የሆነው ሆኖ ሙት ወቃሽ አያድርገኝ እና አቶ መለስ አምባ ገነን ነበሩ! አሁን ሲሞቱ ደግሞ ባለ ስልጣኖቻቸው “እምባ” ገነን እንዲሆኑ ታላቅ ስራ እየሰሩላቸው ነው።

አቶ በረከት ስምዖን ትላንት በኢቲቪ አንገታቸውን አሾልከው ሲነግሩን፤ “መንግስታችን አሁን ምንም አስቸኳይ ስራ የለውም! ዋናው ስራችን አቶ መለስን መሸኘት ነው።” ሲሉ ነግረውናል። ይሔ “ሽኝት” እስከሚቀጥለው ሳምንት እሁድ ነሐሴ 27/2004 ዓ.ም ድረስ ቀጣይ ነው።
አቶ መለስ የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር የነበሩ እንደመሆናቸው መጠን ተገቢ እና ደማቅ “የሽኝት” ስነ ስርዓት ቢደረግላቸው እኔም ደስታዬ ነው። (ወዲህም በጣም ወዳጄ ነበሩ!) ነገር ግን “ሽኝቱ” ገደብ እና ልክ ሊኖረው ይገባል። ምን ወዳጅ ቢኮን “ሸኚ ቤት አያደርስም”
የጠቅላይ ሚኒስትሩ አስከሬን አዲሳባ ከገባ ዛሬ አምስተኛ ቀኑ ነው። ገና ለሚቀጥሉት ስምንት ቀናት ከል ለብሰን ሀዘን ላይ እንድንቀመጥ ባለስልጣኖቻችንን ፈርደውብናል።
ከዚህ በፊት በራዮ በቴሌቪዥን እንዲሁም በተለያዩ አጋጣሚዎች የመንግስት ሰዎች “ህብረተሰቡ የለቅሶ ስርዓቱን ገደብ ሊያበጅለት ይገባል… ዕድር ለልማት” ሲሉ ይመክሩን የነበሩ ባለስልጣናት ሁሉ ዛሬ ራሳቸው የመከሩንን ማድረግ አልቻሉም።  በየ ሰፈሩ ያሉ ዕድሮችም በየአካባቢያቸው ድንኳን ጥለው ሀዘን እንዲቀመጡ አዋጅ ተነግሯል። ለመሆኑ ይህ ሁሉ ሀዘን ምን ርባና አለው…? ለመሆኑ ሀዘን የሚወልደው ሌላ ሀዘን አይደለምን!? ብለን ብንመክር “ጨካኞች እርኩሶች” በሚል ውግዘት ይደርስብናል! ነገር ግን የመጣው ይምጣ ብለን እንናገራለን… “ሀዘኑን በልክ ብናድርገው ምን ይለናል!?”
እስቲ ለማንኛውም ከዚህ ከለቅሶ ስርዓት መንዛዛት ጋር ተያይዞ አንድ የተስፋዬ ካሳን ቀልድ ልጋብዛችሁና ወደ በኋላ “ሞራሌን” አሰባስቤ ወሬም አሰባስቤ እመለሳለሁ!
http://www.youtube.com/watch?v=enczk4pD-Xc&feature=player_embedded

No comments:

Post a Comment