Translate

Sunday, August 19, 2012

የደህንነት ሹሙ አቶ አቶ ጌታቸው አሰፋ “የጠቅላይ ሚኒስትሩን ህመም ተከትሎ ጎንበስ ቀና ማለቱ ያስተዛዝባል” አሉ


ነሀሴ ፲፪ (አስራ ሁለት) ቀን ፳፻፬ ዓ/ም
ኢሳት ዜና:-የኢሳት የብሄራዊ የመረጃ እና የደህንነት ምንጭ እንደገለጠው የደህንነት ዋና ሹሙ አቶ ጌታቸው አሰፋ ሰሞኑን ዋና ዋና የሚባሉ የኢሚግሬሽንና የውጭ መረጃ ሰራተኞችን እና በተለያዩ ተቋማት የተመደቡ የደህንነት አባላትን ሰብስበው በአቶ መለስ ዜናዊ የደህንነት ሁኔታ ላይ ገለጻ ሰጥተዋል።
ከስብሰባው በፊት በከፍተኛ የስልጣን እርከን ላይ ለሚገኙት የደህንነት አባላትና የመንግስት ባለስልጣናት ” የጠቅላይ ሚኒስትሩን ህመም ተከትሎ ጎንበስ ቀና ማለቱ ያስተዛዝባል” በሚል ርእስ  ባለሁለት ገጽ ደብዳቤ ጽፈው አሰራጭተዋል።

ዋና ዳይሬክተሩ አቶ ጌታቸው በደብዳቤያቸው ” አቶ መለስ ዜናዊ በህይወት መኖራቸውን፣ እንደማንኛውም ሰው መታመማቸውን፣ እንደማንኛውም ሰው እረፍት እንዳስፈልጋቸው እና በሀኪማቸው ምክር ከስራ እንደተገለሉ፣ ከዚህ ውጭ የሚናፈሰው ወሬ ትክክል እንዳልሆነ ፣ ህክምናቸውንም በአውሮፓ ውስጥ በጥሩ ሁኔታ እየተከታተሉ መሆኑን” ገልጠዋል።
ኢሳት በመጀመሪያ ወሬውን ካሰራጨ በሁዋላ በህብረተሰቡ ውስጥ  ብዥታ ሊፈጠር መቻሉን፤ በኢሳት ውስጥ የሚሰሩ ሰዎች ያላቸው  አመለካከትና ከእነማን ጋር እንደሚሰሩ የሚታወቅ መሆኑን” ደብዳቤው ያትታል።
ይህንን አጋጣሚ በመጠቀም ኢሳትና በኢሳት ዙሪያ ያሉ ሰዎች ለውጥ ይመጣል ብለው እንደሚያስቡ ካተተ በሁዋላ፣ አቶ መለስ ዜናዊ እንደ አንድ ግለሰብ እንጅ እንደ አንድ ፓርቲ መታየት እንደሌለባቸው ይመክራል ።
አቶ መለስን  እንደ አንድ ፓርቲ አድርጎ መቁጠሩ ስህተት መሆኑን የገለጡት ዋና ዳይሬክተሩ አቶ ጌታቸው፣ አቶ መለስ ከታጋዮች እና በትግሉ ዘርፍ ካሉ ታጋዮች መካከል እንደ አንዱ እንጅ የተለዩ ሰው ተደርገው መታየት እንደሌለባቸው ገልጠዋል።
ይህን ደብዳቤ ለመጻፍ የተፈለገው ማንኛውም በመረጃ መስሪያ ቤቱ ውስጥ የሚሰራ ሰራተኛና የመንግስት ባለስልጣን ማወቅ ስለሚገባው ነው የሚለው የዋና ዳይሬክተሩ ደብዳቤ፣ ይሁን እንጅ ” ሰራተኞች ብቻቸውን ማወቃቸው በቂ ባለመሆኑ በህብረተሰቡ ውስጥ በመግባት የማሳመን ስራ መስራት እንደሚገባቸው ያሳስባል።
ደብዳቤው የተላከው ለተወሰኑ ሰዎች ብቻ በመሆኑ ኢሳት የመረጃ ምንጩን ደህንነት ለመጠበቅ ሲል ለጊዜው ደብዳቤውን ይፋ ከማድረግ ይቆጠባል።
አቶ ጌታቸው ይህንን ደብዳቤ ለመጻፍ የተገደዱት ነባር የህወሀት ታጋዮች የሚያምኑባቸው ሰዎች ባህሪ መለዋወጥ፣ በድርጅቱ ውስጥ የሚታየው የስልጣን ፉክክር እንዲሁም በደህንነት መስሪያ ቤቱ ውስጥ የሚታየው ሁኔታ ስላሳሰባቸው ነው።
የደህንነት ሹሙ የጻፉት ጽሁፍ የህወሀት መስራቹ አቦይ ስብሀት በመገናኛ ብዙሀን እየቀረቡ ከሚናገሩት ጋር ተመሳሳይነት አለው።  በሌላ በኩል ግን አቶ በረከት ስምኦን  በመገናኛ ብዙሀን እየቀረቡ ስለአቶ መለስ ዜናዊ ልዩ የአመራር ችሎታ ፣ በፓርቲው ውስጥ ስላላቸው ልዩ ሀላፊነት ከሚናገሩት ጋር የሚቃረን ነው። አቶ በረከት አቶ መለስን ልዩ ችሎታ ያላቸው ሰው አድርገው በማቅረብ የግል ዝናቸውን እየገነቡ ሲሆን፣ የህወሀት አመራሮች በበኩላቸው የአቶ መለስን ሚና ዝቅ በማድረግ እያቀረቡ ነው።

No comments:

Post a Comment