Translate

Wednesday, August 29, 2012

የዋልድባ አብረንታንት መነኰሳት መሰደድ ጀምረዋል


  • ባለፉት ጥቂት ቀናት ከስድስት ያላነሱ መነኰሳት ተሰደዋል
  • “ታጋይ ገድላችኹ እናንተ አትኖሩም” (የፀለምት - ማይ ፀብሪ ወረዳ ሓላፊዎች)።
(ደጀ ሰላም፤ ነሐሴ 21/2004 ዓ.ም፤ ኦገስት 27/ 2012/ READ THIS NEWS IN PDF)፦ በዋልድባ አብረንታንት ገዳም መነኰሳት ላይ ባተኰረውና ካለፉት አራት ቀናት ጀምሮ እየተባባሰ በቀጠለው እስርና እንግልት ሳቢያ ከስድስት ያላነሱ መነኰሳት የፀለምት - ማይ ፀብሪ የፀጥታ ኀይሎች በሚያደርሱባቸው ግፍ ሳቢያ ወደ ሌሎች ገዳማት መሰደዳቸውን፣ በተቀሩትም አባቶች ላይ ድብደባ እየተፈጸመባቸው መኾኑን የሥፍራው ምንጮች እየገለጹ ናቸው፡፡
የዜናው ምንጮች እንደሚያስረዱት÷ የወረዳው ፖሊሶችና ታጣቂዎች በገዳሙ መነኰሳት ላይ የሚፈጽሙት እንግልትና ድብደባ የተባባሰው የጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ኅልፈተ ሕይወት መሰማቱን ተከትሎ ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ጽኑ ሕመም እና ኅልፈት ገዳማውያኑን ተጠያቂ በማድረግ ነው፡፡ ቀደም ሲል በየጊዜው እየታሰሩ በተለቀቁት አበው መነኰሳት ላይ ያነጣጠረው ይኸው ርምጃ በአሁኑ ወቅት ደግሞ መነኰሳቱ ጨርሶ ገዳሙን ለቀው እንዲወጡ ከማዘዝና ከማስገደድ ጋራ የተያያዘ መኾኑም ተመልክቷል፡፡

በወረዳው የጸጥታ ኀይሎች “ገዳሙን ለቃችሁ ውጡ፤ ታጋይ ገድላችሁ እናንተ በሰላም አትኖሩም፤” እየተባሉ መደብደባቸውን የተናገሩት የዋልድባ አብረንታንት መነኰሳት÷ በተለይም ከነሐሴ 18 ቀን 2004 ዓ.ም በሚፈጸምባቸው ድብደባ በርካታ አባቶች መጎዳታቸውን፣ ከተሰደዱት ስድስት መነኰሳት መካከልም አባ ገብረ ማርያም ጎንዴ እና አባ ገብረ ጊዮርጊስ የተባሉ አባቶች እንደሚገኙበት አስታውቀዋል፡፡

በአሁኑ ወቅት ማኅበረ መነኰሳቱ ከሰኔ 21 ቀን እስከ ኅዳር 8 ድረስ በሚዘልቀው የሱባኤ ወቅት ላይ ይገኛሉ፤ የመንግሥት ሓላፊዎችም በተለመደው አነጋገር “ዳዊታቸውን እንደ ዘቀዘቁ ናቸው፤ መቅሠፍቱም ይቀጥላል” ብለዋል በሚል የገባው በማይወጣበት፣ የወጣው በማይገባበት ይህን የሱባኤያቸውን ወቅት እንኳ ሳይታገሡ ነው ድብደባውንና እንግልቱን የሚፈጽሙት፡፡

በአቶ መለስ መሐንዲስነት እንደተቀየሰ በተነገረው የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ውስጥ የአንዱስትሪ ልማት ዘርፍ አካል ከሆኑት ዐሥር ግዙፍ የስኳር ፋብሪካ ግንባታዎች አንዱ የኾነው የወልቃይት ስኳር ልማት ፕሮጀክት÷ በገዳሙ ህልውናና ክብር ላይ ከሚያደርሰው ተጨባጭ አደጋና ታሳቢ ስጋቶች የተነሣ ሐዘናቸውን ወደ እግዚአብሔር በማመልከት የቆዩት አበው መነኰሳት የዋልድባ አብረንታንት ገዳም ዘቤተ ሚናስ ማኅበር አባላት ናቸው፡፡

ነሐሴ 15 ቀን 2004 ዓ.ም ከሌሊቱ 5፡40÷ በሚኒስትሮች ም/ቤት መለጫ መሠረት ድንገት በተከሠተ ኢንፌክሽን÷ ከዚህ ዓለም በሞት መለየታቸው የተሰማው የጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ጽኑ ሕመምና ኅልፈት “የመነኰሳቱ እንባና ሐዘን ወደ እግዚአብሔር ከመድረሱ የተነሣ የመጣብን ተግሣጽ ነው” ብለው የሚያምኑ ወገኖች ቁጥር በቀላሉ የሚገመት እንዳልሆነ በተለያዩ ማኅበራዊ ድረ ገጾች የሚታዩ የመረጃ ልውውጦች እና ከኅልፈታቸው ጋራ ተያዘው የሚደመጡ ፈርጀ ብዙ ትርክቶች እያጠየቁ ናቸው፡፡

ቸር ወሬ ያሰማን፤
አሜን፡፡

No comments:

Post a Comment