Translate

Sunday, August 19, 2012

የኢድን ሰላት ተከትሎ ሙስሊሙ የተቃዉሞ ድምፁን በአዲስ አበባ ስቴድየም አሰማ


ዛሬ ነሐሴ 14/2004 በአዲስ አበባ ስቴድየም የኢድን በዓል ለማክበር የወጣዉ ከፍተኛ ቁጥር ያለው ህዝበ ሙስሊም የኢድ ሰላት ከተጠናቀቀ በኃላ የተቃዉሞ ድምፁን በተለያዩ መንገዶች ያሰማ ሲሆን ፤ ተቃውሞውም በሰላም ተጠናቋል፡፡

Eid Mubarek Addis Ababa, Ethiopia
ከኢድ ሰላት በኃላ ህዝበ ሙስሊሙ ነጭ ሶፍት ፣ መሀረም….ወደ ላይ ከፍ በማድረግ ለ8 ደቂቃ ያዉለበለበ ሲሆን ቀጥሎም እጁን በካቴና እንደታሰረ በማስመሰል ሁለት እጁን አጣምሮ ወደ ላይ ከፍ አድርጎ ለ5 ደቂቃ አሳይቷል፡፡ በመቀጠልም ተክቢራ በማሰማት አጠናክሮ የቀጠለ ሲሆን ፤ አከታትሎም “ጥያቄያችን – ይመለስ!! ፣ ኮሚቴዉ – ይፈታ!! ፣ የታሰሩት – ይፈቱ!! ፣ ምርጫችን – በመስጂዳችን!! ፣ ኮሚቴዉ ሳይፈታ – በምርጫ አንሳተፍም ፣ በእምነታችን – ጣልቃ አትግቡ!! ” እና የመሳሰሉ የሚሉ ጥልቅ መልዕክት ያነገቡ የተቃዉሞ መፈክሮችን እጅግ በደመቀና ከዚህ በፊት ተደርጎ በማይታወቅ ሁኔታ አሰምቷል፡፡
እንደ ሌላው ጊዜ የተቃውሞ እንቅስቃሴውን የሚያስተባብሩ አካላት በሌሉበት ሁኔታ ህዝበ ሙስሊሙ በራሱ አነሳሽነት በፌስ-ቡክና በሌሎጭም የማህበራዊ ድህረ ገፆች መክሮ ባወጣዉ የተቃዉሞ መርሀ ግብር መሰረት በተሳካ ሁኔታ ተቃውሞውን ማካሄድ የቻለ ሲሆን ፤ ይህም የሙስሊሙ አቋም ምን ያህል ጠንካራ እንደሆነ በግልፅ አሳይቷል፡፡
ምንም እንኳን ተቃዉሞዉን ተከትሎ ከፍተኛ ግጭት ከፌደራል ፖሊስ ጋር ይፈጠራል ተብሎ ተፈርቶ የነበረ ቢሆንም ፤ ያ ሳይሆን ቀርቶ ሁሉም ነገር በሰላም ተጠናቋል፡፡ ህብረተሰቡም እንደተለመደዉ ሁሉ ጨዋነት በተሞላበት ሁኔታ በግሩፕ በመሆን አላህን እያወደሰ ወደ መጣበት ተበትኗል፡፡
ሆኖም መንግስት ባደረበት ከፍተኛ ስጋት ምክንያት ሙስሊሙ ህብረተሰቡ ከዚህ ቀደም እንደሚያደርገዉ ባንድ ላይ ተሰባስቦ በስቴዲየምና አካባቢዉ የኢድ ሰላት እንዳያደርግና ተቃዉሞዉን እንዳያሰማ በማሰብ በተለያዩ አካባቢዎች መንገዶችን በመዝጋት የማሰናከል ስራ የሰራ ሲሆን ፤ በብዙ ሺህ የሚገመቱ ሙስሊሞች በዋናዉ የበዓሉ ቦታ ለመድረስ ያደረጉት ጥረት ሳይሳካ ቀርቶ በየመንገዱ ላይ ለመስገድ ተገደዋል፡፡
ከዚህም በተጨማሪ በተለምዶ በ3 ሰዓት የሚጀመረዉን የሰላት ስነ-ስርዓት አስቀድሞ በጠዋት በማስጀመር በቶሎ እንዲጠናቀቅ የተደረገ ሲሆን ፤ የኢትዮጵያ ቴሌቭዥንም ስነ-ስርዓቱን ሙሉ በሙሉ እንዳያስተላልፍ ተደርጓል፡፡ ይህም ምንም እንኳን ተቃዉሞዉን ባይገታዉም የበዓሉን ድምቀት ግን በመጠኑም ቢሆን አደብዝዞታል፡፡
አንዳንድ በበዓሉ ላይ የተገኙ የህብረተሰብ ክፍሎች የተፈፀመዉ በዓሉን የማሰናከል ተግባር ከመንግስት የማይጠበቅና አሳፋሪ ነዉ ያሉ ሲሆን ፤ ሙስሊሙን ህብረተሰብም የበለጠ አስቆጥቶቷል ብለዋል፡፡
እነዚህ የህረተሰብ ክፍሎች አያይዘዉ መንግስት ተቃዉሞዉን ለማሰናከል ቢሞክርም በመቶ ሽህ የሚቆጠር ህዝብ ስታዲየም ተገኝቶ ድምጹን ከማሰማት አላገዱትም ሲሉ ተናግረዋል፡፡

No comments:

Post a Comment