Translate

Saturday, January 26, 2013

የሃይማኖት መብቶች እንዲከበሩ ለሁሉም መብቶች የመታገያ ግዜው አሁን ነው!



ፍትህ፣ ነጻነት፣ እኩልነትና አንድነት የብዙ ሃይማኖቶች መሰረታዊ መርህ  እሴቶች ናቸው። እነዚህ ቲውፊቶች ለአለፉት 20 አመታት በዘረኛው ወያኔ እየተሸረሸሩና እየመነመኑ ዛሬ ከእነ አካቴው በሀገራችን ኢትዮጵያ ስለመሰረታዊ የሰው ልጆች መብት ነጻነት እንዳይወራ፤ ወያኔ የጥይት አፈ ሙዞች በእያንዳንዱ የህዝብ አገልግሎት ተቋማት ላይ በመደቀን የአምልኮ ቦታዎችን ሳይቀር በመዳፈር ህዝበ ምእመናኑ የእኔ የራሴ የሚለው የአምልኮት ቦታ እና ህግ እንዲያጣና እንዳይኖረው እያደረገ ነው።
በሀገራችን ኢትዮጵያ ከቀን ወደቀን እየተባባሰ የመጣው የእምነት ነጻነት እጦት ሁላችንንም ሊያሳስበን እና ሊያስተሳስረን የሚገባበት ጊዜ ላይ ደርሰናል። በተለይም በታሪካችን፡ የኢትዮጵያ ህዝብ በእምነት፣ በዘር፣ በፖለቲካ እስከ ቅርብ ጊዚያት ድረስ ሳይለያይ ተከባብሮና ተሳስቦ የሚኖር ህዝብ እንደሆነ የማይካድ ሃቅ ነው።
ይሁን እንጅ ከቅርብ ግዜ ወዲህ አምባገነኖች በፈጠሩት ህገ- አራዊት በሆነው የከፋፍለህ ግዛ እና የአንድ ዘር የበላይነት ፖሊሲ አማካኝነት የምንወዳት ሀገራችን ኢትዮጵያ፤ አበው ለአንድነቷ፣ ለህልውናዋ የሞቱላት፣ ዘውግ፣ ቋንቋና የሃይማኖት ልዩነት ሳያግዳቸው የገነቧት እማማ ኢትዮጵያ፤ የልጆቿ የኤሎሄ ማሰሚያ ስፍራዎች፣ ተቋማትና የገዳማት አባቶች በህወሃት የጥፋት አለንጋ እየተገረፉ ናቸው።

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን 4ኛውን ፓትርያርክ ከ1984 ዓ.ም ጀምሮ ከእምነቱ ቀኖና ህግ ውጭ በሆነ መንገድ ህጋዊውን ፓትርያርክ በማባረር በዘረኛው የወያኔ አስተዳደር ስርአት ውስጥ በማስገባት አባ ጳውሎስ እስከሞቱበት እለት ድረስ እና አሁንም ምእመናኑ በመከፋፈል የተሳካላቸው ወያኔዎች፤ በቅርቡ ሊደረግ የነበረውን የእርቀ ሰላም ሂደት በወያኔ ጀሌዎች እንዲሰናከል የስርአቱ አገልጋይ አባቶች የሆኑትን፤ ልሳናቸውን በመጠቀም የኦርቶዶክስ ተዋህዶን እምነት አሁንም በወያኔ ቁጥጥር ስር ሆና እንድትመራ የተደረገው አሳዛኝ ክስተት አንዱ ነው።
ወያኔ አንግቦ የተነሳው አላማ፤ ዜጎች በዜግነታቸው በሚኖሩበት ሀገር  ምንም አይነት ነጻነት እንዳይሰማቸው፣ የጥቃት ሰለባዎች እንዲሆኑና የዜጎች የማምለክ ነጻነትን በማዋረድ ጸረ – ሐይማኖታዊ ተግባሩን እንደሙስሊሙ ማህበረሰባችን እና እንደተቀረው የህዝብ ተቋማት ሁሉ የደም እጁን በማስገባት በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያንም ውስጥ ብሄርተኝነትን በማራመድ የተለመደ የፖለቲካ ስራውን እየሰራ ነው፡፡
በአንጻሩ ስለኢትዮጵያ አንድነትና ሰላም ቀን ከሌት የሚጸልዩትን አባቶች ደግሞ እንደጠላት በመፈረጅ ለእንግልትና ለስደት እያበቁ የእግዚያብሄርን ቤት የካድሬዎች ገዳም የፖለቲካ እድሜ ማራዘሚያ  ማድረጋቸው ለህዝበ ምእመናኑ እና ለቤተክርስቲያኗ ነጻነት ክብር እና ደንታ እንደሌላቸው የሚያሳይ  ሃላፊነት የጎደለው አምባገነናዊነት ነው።
ሰሞኑን ህጋዊው ሲኖዶስ ለህዝብ ይፋ በማድረግ ባወጣው መግለጫ፤ ሲኖዶሱ ለሀገራችን አንድነትና ሰላም ሲል የሞከረውን የእርቀ ሰላም ሂደት በማድነቅ፤  የወገናችሁ ጉዳይ አስጨንቋችሁ፣ አሳስቧችሁ ሁሉም ኢትዮጵያዊ በእምነት፣ በዘር፣ በጎሳና በፖለቲካ ሳይለያይ የሲቪሉም ሆነ የፖለቲካ ድርጅቶች በመተባበር በዜጎቻችን ላይ እየደረሰ ያለውን ግፍ  እንታገለው ዝንድ ያቀረባችሁትን ጥሪ ተቀብለን በማሰተዋልና በጽናት ዘረኛውን ወያኔ እንታገለዋለን፡፡ ለዚህም ከእናንተ ጋር ሆነን ለድል እንደምንበቃ አንጠራጠርም።
ወያኔ በሃይማኖታችን፣ በኑሮአችን ጣልቃ በመግባት እምነትን ለማዳከም የሚያደርገውን አፈናና ረገጣ እሰከ መጨረሻው ታግለን በማስወገድ ዜጎች ካለምንም ጣልቃ ገብነት የእምነታቸው ነጻነት ይከበር ዘንድ አብረን ከእናንተ አባቶቻችን ጎን በመሰለፍ ትግሉን ወደፊት ለማድረግ እኛ የግንቦት 7 ንቅናቄ አባላትና አመራር ወያኔን ለማስገደድ ወይም ለማስወገድ ዛሬም ቆርጦ መነሳቱን በድጋሜ ቃል ይገባል።
ድል ለኢትዮጵያ ህዝብ!!

No comments:

Post a Comment