Translate

Wednesday, January 23, 2013

ወ/ሮ አዜብ የመለስ ፋውንዴሽንን በፕሬዚዳንትነት ይመራሉ ተብሎ ይጠበቃል


ኢሳት ዜና:-የኢትዮጵያ ፓርላማ  ባለፈው ሳምንት ሐሙስ  ዕለት  ያጸደቀውና  በቢሊየን  ብር  የሚቆጠር  ዓመታዊ በጀት ይኖረዋል ተብሎየሚገመተው የመለስ ፋውንዴሽንን ወ/ሮ አዜብ  መስፍን  በፕሬዚዳትነት ይመሩታል ተብሎ እንደሚጠበቅ ለጉዳዩ ቅርበት  ያላቸው  ምንጮች አመለከቱ፡፡ ባለቤታቸውን  በድንገት በነሐሴ ወር 2004 አጋማሽ በሞት ካጡ በኋላ  ከአራት ወራት በላይ በተመረጡበት የፓርላማ ወንበር ላይ ተቀምጠው ያልታዩት ወ/ሮ አዜብ  መስፍን  ይኸን  ሃላፊነት   እንዲረከቡ  የተፈለገው ከአቶ መለስ ጋር  የተያያዙ ብዙ ሥራዎች  የቤተሰባቸውን  ዕውቅናና ፈቃድ  የሚፈልጉ  በመሆናቸው   ነው  ተብሎአል፡፡ በዚሁ መሰረት ወ/ሮ አዜብ  ፋውንዴሽኑን  እንዲመሩ አስቀድሞ የማግባባት ሥራ መጀመሩን  ምንጫችን አመልክቷል፡፡


በጸደቀው አዋጅ መሰረት የሚቋቋመው ፋውንዴሽን ጠቅላላ ጉባዔ፣ቦርድ፣ፕሬዚዳንት እና ምክትል ፕሬዚዳንት
ይኖሩታል፡፡ ከ13  ተቋማት 45 ያህል የጠቅላላ ጉባዔ አባላት ያሉት ሲሆን በውክልና ደረጃ ከአቶ መለስ ቤተሰብ
አራት ያህል ተወካዮች በጠቅላላ ጉባዔ ውስጥ እንዲካተቱ ተደርጓል፡፡በተጨማሪም ከመከላከያ ሶስት፣ከገንዘብና
ኢኮኖሚ ልማት ፣ከውጪ ጉዳይ ፣ከትምህርት፣ከጤና ጥበቃ ሚኒስትር መ/ቤቶች፣ከመንግስት ኮምኒኬሽን ጽ/ቤት፣ከቅርስ
ጥናትና ጥበቃ ባለስልጣን፣ከወጣቶች እና ሴቶች ማህበራት  ከእያንዳንዳቸው አንድ ከፍተኛ አመራር አባል የጠቅላላው
ጉባዔ አባላት ሲሆኑ ከመንግስት ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት አምስት፣ከእያንዳንዱ ክልል አምስት ተወካዮች ይኖሩታል፡፡
በአዋጁ መሰረት የፋውንዴሽኑን ሰባት አባላት በጠቅላላ ጉባዔ ለአራት ዓመታት  የሚመረጡ ሲሆን የአቶ መለስ ዜናዊ
አራት የቤተሰብ አባላት ግን በቀጥታ ያለምርጫ ቦርዱ ውስጥ እንዲገቡ አዋጁ ይፈቅዳል፡፡ ቦርዱ ደግሞ የፋውንዴሽኑን
ፕሬዚዳንትና ምክትል ፕሬዚዳንት መርጦ ይሾማል፡፡በዚሁ መሰረት በፋውንዴሽኑ ቦርድ ውስጥ ወደ ግማሽ የሚጠጋ ድምጽ
የያዘው የአቶ መለስ ቤተሰብና ወዳጆቻቸው ወ/ሮ አዜብን በፕሬዚዳንትነት ይመርጣሉ ተብሎ እየተጠበቀ ነው፡፡


አራት ክፍሎችን፣ሃያ አራት አንቀጾችንና በርካታ ዝርዝር ጉዳዮችን የሚደነግጉ ንዑስ አንቀጾችን የያዘውና በጠ/ሚኒስትሩ ጽ/ቤት ተረቅቆ ፓርላማው ያጸደቀው ይኸው አዋጅ ስለፋውንዴሽኑ ዓላማ ሲገልጽ “የፋውንዴሽኑ ዓላማ ክቡር አቶ መለስ ዜናዊ በሕይወት ዘመናቸው ሲታገሉለት የነበሩትን የልማታዊና ዴሞክራሲያዊ መንግስት ፣የሰዎች ዴሞክራሲያዊ ግንኙነት፣እኩልነት ክብርና ብልጽግና እንዲረጋገጥ የሰውና የተፈጥሮ ግንኙነት ሚዛናዊ እንዲሆን የሚያደርግ የህብረተሰባዊ ለውጥ አስተሳሰብ እና ሰላም ፈለግ ማስቀጠል እና መርሆቻቸውን ማስፋፋት ይሆናል” ይላል፡፡

የፋውንዴሽኑ የገቢ ምንጮች ከውርስ ፣ከስጦታ እና ከዕርዳታ ከሚገኝ ገንዘብና ንብረት፣ከልዩ ልዩ የገቢ ማስገኛ
ዝግጅቶች፣ከመንግስት ከሚሰጥ ድጎማ እና ከመሳሰሉት እንደሚሆን ተደንግጓል፡፡ ለፋውንዴሽኑ ሥራ የሚያስፈልጉ
ዕቃዎች በሙሉ ያለምንም ገደብ ከቀረጥ ነጻ እንደሚገቡም በአዋጁ ተመልክቷል፡፡

ኢሳት በቅርቡ ያገኘው መረጃ እንደሚያመለክተው በርካታ የኢህአዴግ አባላት የአቶ መለስ ፋውንዴሽን የሚዘልቀው ኢህአዴግ በስልጣን ላይ እስካለድረስ ብቻ መሆኑ እየታወቀ በቢሊዮን ብር ወጪ ማውጣቱ ጠቀሜታው ምንድነው በማለት ይጠይቃሉ።

No comments:

Post a Comment