Translate

Saturday, January 12, 2013

“የመለስን ሌጋሲ ማስቀጠል የማንችል ከሆነ ህዝቡ እሳት ሆኖ እንዳያቃጥለን እንሰጋለን” ሲሉ የኢህአዴግ አባላት ተናገሩ


ጥር ፬ (አራት) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም
ኢሳት ዜና:-በሚስጥር የደረሰን በአዲስ አበባ  የኢህአዴግ ድርጅት ጽህፈት ቤት ያዘጋጀው ሚስጢራዊ ሪፖርት እንደሚያመለክተው  የኢህአዴግ አባላት ከመለስ ሌጋሲ እና ከልማት ጋር የተያያዙ በርካታ ጥያቄዎችን ማንሳታቸው ተመልክቷል።
የኢህአዴግ አባላት  ካነሱዋቸው ሀሳቦች መካከል “  መስመሩን ያላወቁ አባላት ባለበት እንዴት ሌጋሲውን ማስቀጠል ይቻላል? አባሎች ራሳቸው ጀርባቸው መጠናት አለበት፣ ንፋስ ወደ ነፈሰበት የሚነፍሱ ቁጥራቸው እየበዛ ነው፣ የመለስ ሌጋሲ ሊኖር የሚችለው ስርአቱ እስካለ ድረስ ነው፣ የሚስጥር ጠባቂነት ችግር በአመራሩ ከላይ እስከታች አለ፣ አመራሩ ኪራይ ሰብሳቢነትን አምርሮ አይታገልም፣ህወሀት ሀይለማርያምን ማስቀጠል የለበትም ምክንያቱም ታግሎ የመጣ ሰው ነው መምራት ያለበት”   የሚሉት ይገኙበታል።
በጥሩ ጎን ተብለው ከተጠቀሱት ሀሳቦች መካከል ” የመለስን ሌጋሲ ለማስቀጠል የማይፈልግ የሰማዕታትን አደራ ለመቀበል ዝግጁ ያልሆነ ሰው ነው፤ የመለስን ሌጋሲ ለማስቀጠል አመራር መሆን አያስፈልግም ፣ መለስ ትክክለኛ ሃገር ወዳድ ነው፣ ደፋር መሪ ነው፡፡ በሌሎች መሪዎች ያልተደፈሩ ተግባራትን የደፈረ ነው፡፡”  የሚሉት ተዘርዝረዋል።

የኢህአዴግ የሰራተኛ አባል መድረክ የአቶ መለስን ሌጋሲ ከማስቀጠል አንጻር ካነሱዋቸው ጥያቄዎች መካከል ደግሞ የሚከተሉት ተጠቅሰዋል ”  ስለ መለስ ብቻ ይወራል መለስን የፈጠረው ኢህአዴግ ስለሆነ የኢህአዴግን ሙሉነት ብናወራ አይሻልም ወይ፣ ከመለስ ብዙ እንማራለን በርካታ ጠንካራ ጎኖች አሉት፣ እኛ የሱን ሌጋሲ ለማስቀጠል የህብረተሰቡን ችግር ለመቅረፍ ምን ያህል ዝግጁ ነን፣ስለሌጋሲ እያወያያችሁን ነው፣ እናንተ እራሳችሁ ቁርጠኝነታችሁ እስከምን ድረስ ነው፣ ራስን ከማብቃት አንጻር ከመለስ ሌጋሲ የምንማረው አለ ሆኖም አመራሩም ሆነ አባሉ ችግር አለበት ማስተካከል አለብን” የሚሉት ተጠቅሰዋል።

የኑሮ ውድነቱን በተመለከተ አባሎች ካነሱዋቸው ነጥቦች መካከል ደግሞ ” በኑሮ ውድነቱ የመንግስት ሰራተኛው እየተጎዳ በመሆኑ የህዳሴ ጉዞአችንን ከማሳካት አንጻር አንዱን ሀይል እንዳናጣው እንሰጋለን፣ ያለፈው አመት ችግር በታየበት የአሁኑ እቅድ ከስፋት አንጻር ለማሳካት ይከብዳል” የሚሉት ይገኙበታል።

የኢህአዴግ ሰራተኛ አባላት በመለስ ሌጋሲ ላይ ካነሱዋቸው ጥያቄዎች መካከል ደግሞ ” ስለመለስ ሌጋሲ እናውራ ስንል በሙት መንፈስ መመራት አያስምስልም ወይ? የመለስ ሌጋሲ እያልን የምናወራው ሁሌ ጠንካራ ጎኑን ነው፣ ደካማ ጎን የለውም ወይ? ጠናካራ የሆኑ የተቃዋሚ ፓርቲ ፓርላማ እንዲገቡ ልምን አላዳረገም።” የሚሉት ተነስተዋል።
የአባላት መድረክ ካነሱዋቸው ነጥቦች ውስጥ ደግሞ  ”
- የመለስ ሌጋሲ ማስቀጠል ማንችል ከሆነ ህዝቡ  እሳት ሆኖ እንዳያቃጥለን እንሰጋለን ስለዚህ ሌጋሲውን ከማስቀጠል ውጭ ሌላ አማራጭ ሊኖር አይችልም
- ሌጋሲውን ለማስቀጠል አቅም ክፍተት አለብን
- የመለስ ሌጋሲን መውረስ ሲባል እሱን መሆን ሳይሆን ባለንበትና በተሰማራንበት የህዝብ አገልጋይነት ስሜት መፍጠር መላበስ ነው፣ ከመለስ ሌጋሲ አባሉ ሲመዘን እና የሰአት መስዋት መክፈል አንፈልግም እሱ ግን የህይወት መስዋትነት ከፍሎ አሳይቶናል” የሚሉት ይገኙበታል።
ግንባሩን በተመለከተም ” የአባላት የተሳትፎ ችግር አለ፣ የውስጥ ድርጅት ስራችን በጣም ተዳክሞአል፣ ድጋፍና ክትትል አካባቢ ያለው ስራም አናሳ ነው፣ አመራሩ የሚፈልገን ለዘመቻ ስራ እንጅ በቋሚነት የመደገፍ ችግር አለበት ፡” የሚሉት ተጠቅሰዋል።
በህዝብ መድረክ ከተነሱት ጥያቄዎች መካከል ደግሞ “ተማሪዎች በአጥር እየዘለሉ ጫትና ሺሻ ቤት እየገቡ ተቸግረናል፣ ሺሻ ቤት ከቀን ወደ ቀን ሲበራከት ለምን እርምጃ አትወስዱም ፣ ሺሻ ቤቶች ላይ እርምጃ ለመውሰድ ሲታሰብ ሚስጢሮች ከፖሊስና ከአስፈጻሚ በኩል ይወጣሉ፣ ከፖሊስ ሲጠሩ በወቅቱ አይመጡም፣ የጸጥታ ኮሚቴ ተብለው የተመደቡት እራሳቸው ችግር አለባቸው፣   የሚሉት ይገኙበታል።
በሪፖርቱ በርካታ ተያያዝነት ያላቸው ጉዳዮች የተዘረዘሩ ሲሆን ሙሉ መረጃውን እዚህ ላይ በመጫን ሊያነቡት ይችላሉ  EPRDF DOC

No comments:

Post a Comment