Translate

Saturday, August 4, 2012

አበበ ገላው ጫማ ወርውሮ ቢሆን ኖሮ የለቅሶ ቤት ወግ ከጋና


ከ ቹቹቤ
እንዴት ሰንብታችሁልናል? እኛ ደህና ነን። የምንለው ጠፍቶ ሳይሆን የምንልበት ጊዜ አንሶን ሰነበተ። መልዕክተ ቹቸቤ መጽሀፍ ሆኖ ሊወጣ ነው ብለን ቃል በገባነው መሰረት ስራው እየተቀላጠፈ ነው። ሁሉም ነገር እንዳሰብነው ከተሳካ በጽሁፍና በድምፅም ማለትም ጥቂቶቹን መርጠን በሲዲ እናደርግና ለንባብና በድጋሚ ለመደመጥ እንዲበቃ እናበረክተዋለን። ገቢው ደግሞ ኢሳትን ይረዳል። በቅርቡ ደግሞ በአዲስ አቀራረብ እንቀርብላችሁና አብረን ጥቂት ሳምንታት እንሰነብታለን። ጨርሶውኑ ላለመጥፋትና ከመናፈቅ ወደአበበ ገላው ጫማ ወርውሮ ቢሆን ኖሮ የለቅሶ ቤት ወግ ከጋና
ለወሬ ነጋሪ የሚሆን ሁነኛ አበሻ ያልገባበት የለም።
ለነገሩ ምድርንስ የሞላው ከአበሻ መሬት የተነሳው አይደለምን? እና ጋና መሪ ሞቶባት በሀዘን ተውጣለች ። እናቱ የሞተችበትና ውሀ ልትቀዳ የወረደች እኩል ሊያለቅስ አይገባም እንዲሉ ኢትዮጵያ የሞት ወሬ እንጂ የተረጋገጠ የመሪ ሞት የለምና ስለሀዘን አይወራም። እኛ እኮ ሞትም ቢሆን ለዘመድ አዝማድ ተነግሮ ሁሉም ተሰባስቦ ነው እርም የምናወጣው። ሞትን እንዲህ እንደዋዛ መች እናየውና። መቸም በሞቱ የሚጨፈርለትና የሚለቀስለት ይለያያልና የኛን የሚጨፈርለትን ትተን የሚለቀስለትን እናስብ። ያላሰቡት ለቅሶ ላይ ተቀምጠው ያሉት ወገኖች ከምድረ ጋና ያደረሱኝ አድርጌ በሀሳቤ ያለውን ላውጋችሁ። እንደምታውቁት ጋና የኛን አረንጓዴ ቢጫ ቀይ ገልብጣ ቀይ ቢጫ ረንጓዴ አደረገችና ጥቁር ኮከብ ጣለችበት ለጥቁር አፍሪካ መታሰብያ፣ ያ የሆነው በስልሳዎቹ ነበር። ወደር አልባው ኮራጅ አቶ መለስ ደግሞ ከግማሽ ምዕተ አመት በሁዋላ የሁዋልዮሽ ከጋና የኮከብ ሀሳብ ተዋሱና ጨው የቋጠሩበትን ሰንደቅዓላማችንን ባለጨረር ሰማያዊ ኮከብ አስጫሩበት ። የመኮረጅ ችሎታቸው ከመቃብራቸው በላይ የሚውል ነው፣ እሳቸውም የሚኮሩበት። እናም ከመንፈስ አባታቸው ከሙሶሎኒ የጎሳ መንግስትን ወረሱ፣ ሕገ መንግስትን ደግሞ እርጥባን ከሚሰጣቸው ከካናዳ አስገለበጡ፣ የሽብር አዋጅን በስልጣን ካቆሙዋቸው ከአሜሪካና ከእንግሊዝ ቀዱ ነጠላ ሰረዝ አራት ነጥብ ሳያስቀሩ። ስማቸውንም ከሟች መለስ ወስደው ለገሰን እንደ ጦስ ዶሮ አዙረው ጣሉት። አንድ ነገር ብቻ ትክክል አደረጉ። ለገሰ የሚለው ስም አይመጥናቸውም የሁዋልዮሽ መሄዳቸውን መለስ የተሻለ ይገልጠዋል። በዚህ እናድንቃቸውና እሳቸውን ትተን ወደ ጋና እንሂድ። ከወዳጆቼ ጋር ለቅሶ መቀመጥ ወስነናል። ለቅሶ በስካይፕ ስቀመጥ የመጀመሪያዬ ነበርና በአክራ የተጠመዱት ሁለት ላፕቶፖች (የጭን ኮምፕዩተሮች) አካባቢውን ያስቃኙኛል። የለቅሶው ቤት ጭውውቱ እንዲህ ቀጥሎ ነበር……
“…. የመሪ ለቅሶ አምሮን መርዶ ስንጠብቅ ባላሰብነው ሁኔታ ይኸው የጋናው መሪ ጆን አታ በተመሳሳይ መዝገብ ጥሪ ተደርጎላቸው ኖሮ ለቅሶ እዚሁ ተቀምጠናል።” ይላሉ እነዚህ ወዳጆቼ። ከክፉ ሰው ጎን ተቀምጠው ጠሱ ለሳቸውም ተረፈ አይደለም በርታ በሉ እንግዲህ ለሀጥአን የመጣ ይባል የለም። ምን ይደረግ ወዳጆቼ እያልኩ ማጽናናት ያዝኩኝ ወጉን ልጠብቅ ብዬ። እነዚህ ወዳጆቼ የአለም አቀፍ ድርጅት ዶላር እያስታቀፋቸው ኑሮአቸውን በአክራ ጋና ካዳረጉ አመታት እየተቆጠሩላቸው ነው ብለን እናስብ። አዎ እነሱን ስናነሳሳ አክራንም እናስባት የጸሀዩ ሙቀት ምቾት ያለው ሆኖ ከ25 እስከ 28ዲግሪ ሴልሺየስ ይላል ሰሞኑን። አልፎ አልፎ ይዘንባል እናም አቧራ የለም። እርግጥ ነው አጨናናቂው የመንገድ ትራፊክ እንደተለመደው እልህ አስጨራሽ ቢሆንም የጋና ሕዝብ ትዕግስተኛና መልካም ስነምግባር ያለው በመሆኑ እንደ አዲስ አበባ ሾፌር ከመንጃ ፈቃዱ ጋር የስድብ ፈቃድ አልተሰጠውም። በጎዳና የሚጓዙ ኮረዳዎችም እንደ አዲስ አበባው የውበት ጨረር እየፈነጠቁ ወንድ ማለት መኪና የሚነዳ ነው የሚሉ አይመስሉም። እናም መሪ ጨባጩን ትምክህተኛ አያደርጉም። ለነገሩ መሪ የምናባልግስ እኛው አይደል ሽቅብ አውጥተን? እሱን እንተወው አክራ ግን እንደዚህ ነች ረጋ ያለ ሕዝብ የሚኖርባት። የተነሳነው ስለዚህ ለማውጋት አይደለም ግን እንደዚህ ያለ መንገድ እያቆራረጡ ነበር ሶስቱ ያገራችን ልጆች የባለጸጎች በሆነችው ሰፈር የሚገናኙት። የአንደኛው ቤተሰብ ሰው መጋበዝ ደስ ይለዋል፣ እናም ሌሎቹ የሚጠጣ ተሸክመው ይቀላቀላሉ። የማያከብሩት በዐል የለም ጉዳያቸው ከበዐሉ ሳይሆን ከመብሉና ከጨዋታውም ነው። ፍቅር አይለየን እያሉ የሚያንጎራጉሩ ይመስለኛል እንደ ፀሀዬ ዮሃንስ።
የጸሃዬን ዘፈን እዚህ ጋ ብናስገባ?
እና የዛሬው መሰባሰብ ለቅሶውን በተመለከተ ነው። ለቅሶ ተቀምጠን ስለ ጆን አታ ህየወት ምስጋና እናቅርብ ብለው ነው መገናኘታቸው። ቅዱስ ሀሳብም ነው ብዬም ነበር ለቅሶ በስካይፕ መድረሴ። አዎ እናም ምግቡ እስኪቀርብ ድረስ ጊልደር ክለብና ካስትል በጋና የሚመረቱ አማራጭ ጠላዎች ናቸውና እነሱን እየተጎነጩ በረንዳው ላይ ይንጎራደዳሉ። ከፊት ለፊታቸው የተመቻቸው ጤናአዳሞች አመድማ መልክ ይዘው ይታያሉ ነጭ እርግብ የመሳሰሉ ነጫጭ በጣም ትናንሽ ትንኞች መንደር መስርተው ጤና አዳሙ ላይ ይኖራሉ። ሮዝሜሪም ችምችም ብሎ ይታያል። ድግስ ያለ ቀን ስለሚቀነጣጠሱ ጊቢው በቆንጆ መዐዛ ታጥኖአል። ሚስት ያለበት የአበሻ ቅጥር ጊቢ ጤናአዳምና ሮዝሜሪ አያጣም አንዳንዱ ኮሰረትም ጌሾም አለው። አበሻ ሲጓዝ አገሩንም ይዞ ነው የሚሄደው መባሉ እውነት ነው።
አቤቱ ፈጣሪ ሆይ ልጅህ በምድር ከምግባረ ጥፉው መለስ ጎን እንደተቀመጠው ሁሉ በሰማይም አብረው እንዳይሆኑ ፍርድህ የዘገየ አይሁን። ለሀጥአን የመጣ ለጻድቃን ይተርፋል እንዲሉ ለመለስ የመጣው መሪአችንን ጆን ሚልስ አታንም ስላገኘብን ብናዝንም አንተ አዋቂ ነህና እንደፈቃድህ ይሁን። አቤቱ ሀገራችንን ከዚህ ቅሌት ስላወጣህ ተመስገን ብለው ጋናውያን ሲጸልዩ ስማው ስማው አሉኝ። ምናልባት በቴሌቭዥን አንድ ፓስተር እየጸለዩ ይሆናል ብዬ ጠረጠርኩ። እኔም ሀዘኑ ተሰማኝ። ከክፉ ሰው ጎን መሆን ክፋቱና ጥፋቱም ታየኝ። አቤት የወያኔ አጋሮች ሀፍረትና መሸማቀቅ ብዬ ትካዜም ተሰማኝ።
ወዳጆቼ ለጋና የስራ ባልደረቦቻቸው የሀዘን መግለጫ በየመስሪያቤታቸው ስለፃፉ አሁን በተረጋጋ መንፈስ ሰውየውን ሊያስቡ ቢፈልጉም የማያረጋጋው የአቶ መለስ መንፈስ ደግሞ ወሬያቸው መሀል አየገባ አስቸግሮአቸዋል። አንደኛው ከትከት ብሎ ሳቀና እሱ አያረገውም አይባልም አለ ለራሱ። ምን ሆንክ አሉ ጓደኞቹ አሁንም ብቻውን ይስቃል። የበለዙ ጥርሶቹ አርግጥም ሲጋራ ማጨስ መጥፎ መሆኑን ይመሰክራሉ። የሱ ሳቅ ግን እንደተላላፊ እየሆነ ነው። እናም ቀጠለና መለስ እኮ እግዜር ፊት ቀርቦ ስለራሱ ጥያቄ ቢጠየቅ ስለ ጋናው መሪ ቅዱስነት ነው የሚመልሰው እያለ ይንከተከታል። መቲ ሙች እሱ እሱ እኮ ለጌታም አይመለስም ይዋሻል እያለ ይስቃል። መታሰቢያ የአንደኛው ወዳጃችን ባለቤት ነች፣ መቲ ይሏታል ሲያቆላምጧት። ታድያ መቲ እንኳን የሚያስቅ አግኝታ እንዲሁም ፍንክንክ ነች፣ ሳቁ ተላላፊ ሆነና ሁሉም ያስነኩት ጀመር በስተመጨረሻ “ ወይኔ እየሳቅሁ አነባሁት” አለች መቲ። “ለማን? አሉ ሁሉም “ለ ጆን አታ ነዋ!” ብላ ሁሉንም እያየች እንደገና ሳቅዋን ቀጠለች። አንድ ወቅት የኛው መለስ ማንን ለማሽሟጠጥ ነው ፊስካል ለማለት ፈልገው ነው ሲላቸው አቶ መለስን አዎን እንዳንተ ኤፍ ላይ አላፏጨሁበትም እንጂ…. ብለው መልሰው መሳቂያ ያደረጉትን ባሰበች ቁጥር ስትስቅ ነበር የከረመቺው።
ሳቅ ስለምትወድ የሚያስቁ ነገሮች አሳደው ያገኟታል። በቀደም አንዲት አያት መለስ የከሳው ሱባዔ ገብቶ ነው፣ አባታችን አባ ጳውሎስ መክረዋቸው ለሕዝባቸው ሲጸልዩ ነው የከሱት። እግዚአብሄር አክራሪ እስላሞችን እንዲይዝልን እየጸለዩ ነው ብለው ሰው አገኘሁ ብለው ያጫወቷትን አምጥታ የእማሆይ ቅስቀሳን እየደገመች ስታስቃቸው ነበር አሉ። ምን ያድርጉ ልጃቸው የወያኔ ባለሟል ሆኖባቸው ነዋ!!
እኔም በተነገረኝ እየሳቅሁ ስለ ጋና ጸጥታ ለማወቅ በመፈለጌ ለመሆኑ አገሩ ሰላም ነው? ስልጣን በሰላም ተሸጋገረ? ጸጥታው እንዴት ነው? አልኳቸው አዎን ምክትሉ ስልጣኑን ተረክበዋል ከሀዘን በቀር ሁሉም ሰላም ነው። እርግጥ ነው ትንሽ ፓርቲ ውስጥ ትንሽ ችግር አለ በተረፈ ሰላም ነው። አዬ ለሰላም እንኳን እኛ ጋ የሚደርስ የለም አልኳቸው። እንዴት ማለት? ይኸው ያለመሪ በሰላም እየኖረ አይደለም የሀገራችን ሰው? እንኳን ሰላም ሆነላችሁ አሳስቦኝ ነበር በሉ እየጠጣችሁ ብዬ የኔን ብርጭቆም አነሳሁ። የጆን አታን ነብስ ይማር አልንና ወሬ ቀጠልን።
የድርሻዬን ወሬ ማቀበል እንዳይቀርብኝ አረ አንድ ሄኖክ የሚባል ገጣሚም እንደናንተው ለቅሶ አማረኝ ብሎ ግጥም ሲያሰማን ነበር። ቃል በቃል አላስታውሰውም ግን መንፈሱ እንደዚህ ነው።
“ …እባክዎ ይሙቱ
ከንበል ይበሉና ሚስትዎ ደረት ይምቱ።
በልክዎ ላሰራ ሳጥንዎን የሬሳ….
ራቅ አርገን እንድንቀብርዎት ኖትና ነቀርሳ።
አይነት ግጥም አስደምጦናል። ይገርማል እኮ አበባ ልግዛሎት የሬሳ ሳጥን ልምረጥሎት ይላቸዋል? የርስዎ ነገር አይታወቅምና በሞትዎ እንኳን አይዋሹኝ ከዚህ ወዲያ ምን ቀረብዎት ገድለዋልና ሞተው ይመልከቱት ይላቸዋል። ሃይለኛ ገጣሚ ለኛ ተነስቶልናል ለሳቸው ደግሞ ተነስቶባቸዋል። ደግሞ እሱ ውሸት ያስተማራቸውን ሰዎችንም ይለምናቸዋል እባካችሁ ሰውነቱ አብጦ ምስጥ ሲያፈርሰው ልመልከት ሬሳውን አሳዩኝ እያለ ይለምናል። እውነትም እነ በረከት መለስ በግሉኮዝ ገመድ ተተብትቦ ከሞት ጋር ሲፋጠጥ ስፖርት እየሰራ ነው ገመድ ጉተታ ላይ ነው እያሉ የተጉረጠረጡ አይኖቹን ያሳዩ ነበር ለደደብ አባሎቻቸው ይቅርታ ደደቢት ለማለት ነው። እኔ እምለው ደደቢት ኮሌጅ ውስጥ የውሸት ስልጠና ይሰጥ ነበር ማለት ነው? ስላቸው እንደሱ ሞት የተቀለደበት የለም። እሱ እኮ ቢድንም ይሄንን አንብቦ ራሱን ማጥፋቱ አይቀርም እያልን ስናወካ ሌላ ተረብ ደግሞ ተነሳ። እውነት የለቅሶ ቤት ተረብ እኮ በሳቅ ይገድላል።
በነገራችን ላይ አለ ጉዋደኛችን በአንድ እጁ የውስኪ ብርጭቆ በሌላኛው ሲጋራ ይዞ። ካሜራውን አጠንክብኝ እባክህ አንተ ሰው አልኩት። ደሞ ገዳዮችህን ነው በእጅህ ያያዝከው አንዱ ለሳንባህ ሌላው ለጉበትህ አልኩት። ያንን ጎረቤት ድረስ የሚሰማ ሳቁን እየሳቀ አቦ አታስፈራራኝ እንዲያውም ካንሰር አለም አቀፍ ኮንፈረንስ አቶ መለስ ላይ እያኪያሄደ ነው አሉ ብሎ ሲናገር “ወይ አንተ መዐተኛ!!” አለች እስካሁን ዝም ብላ ታዳምጥ የነበረቺው። እሷ ሆደ ቡቡ ናት ሁሉን ለእግዜር መስጠት ነው ትላለች። በሷ አጠራር ከሆነ ቁልቢ ገብርዔል ከእግዜርም ይበልጣል። ገብርዔልዬ ስትል በእርግብ ተመስሎ የምትወደውን ባልዋን የመረጠላት ነው የሚመስለው። ግፍ አትናገር እባክህ ሰይጣን የሚያነግስብን ራሱ ስለሆነ በሰዐቱ ይገላግለናል ብላን ልታረጋጋን ፈለገች። አጅሬ ጮክ ብሎ “እንዴ አንች ደግሞ ፈርተነው ኖርን ደፍረነው በምንስቅበት ሰዐት ደግሞ ምን አመጣሽብን?” አለ ወሬ የጀመረው ወዳጃችን። እውነቴን ነው እኮ የካንሰር ኮንፈረንስ እኮ ነው። የጉረሮ ካንሰር፣ የጉበት ካንሰር፣ የአንጎል ካንሰር፣ የደም ካንሰር ሲሉን ምን ልበል ታድያ? አይገርማችሁም? ይሄ ሁሉ አንድ ሰው ለመግደል አይመስለኝም ስብሰባ ነው እንጂ። እያለ ስቆ ለማሳቅ የሁሉንም ፊት ያያል። የካንሰር ብሄር ብሄረሰቦች እንበልልህ እያለች መቲ በሳቅ ስታግዘው ያለ መሳቅ የሚያስቀጣ ይመስል ሁላችንም አስነካነው። እግዜር ይቅር ይበለን አይደል?
ሳቁ መብረድ የለበትም በሚል መነሳሻ ነው መሰል መቲ የመንደርደርያ ሳቅዋን ካስነካችው በሁዋላ እኔ እምለው ለመሆኑ ቡሽ ላይ ጫማ እንደወረወረው የኢራቅ ጋዜጠኛ አበበ ገላው ጫማ ወርውሮ ቢሆን ኖሮ አሁን በሁለት የሀገር መሪዎች ህይወት መጥፋት ተጠያቂ ይሆን ነበር ወይስ አይሆንም? ከህግ አንጻር ይህ እንዴት ይታይ ይሆን? ይሄ ጦሰኛ!! እናቴ ትሙት ጦሰኛ ነው እኮ ብላ ማለቂያ የሌለውን ሳቅ ስትስቅ ኔት ወርኩም ጨከነና እግዜር ያጽናችሁ ሳልላቸው ተለያየን። ከዚያ በሁዋላ የተወራውን አይነት የሕግ ትንተና እዚህ እኛው ልናደርገው እንችላለና በዚህ መዝናናትን አድርጉ እያልኩ ልሰናበታችሁ። በቅርቡ ቹቸቤ ከቀናቶቹ አንዱን ተረክቦ አብሮአችሁ ጥቂት ሳምንታት ይሰነብታል። በሙሉ ሀይል እስክንመለስ እንመራረቃ።
ሄኖክ እንደተመኘው እኛም እንደጸለይነው ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትራችንን ራቅ አድርገን እንቀብር ዘንድ ልመናችን እግዜር ይስማን
ዘርፈው የከበሩ አገር የመዘበሩ የሬሳ ክምር ይሁኑልን።
ደህና ቆዩን
ቹቸቤ
chuchebe@hotmail.com

No comments:

Post a Comment