Translate

Saturday, August 4, 2012

የኢትዮ ቻነል እና የሳምሶን ማስታወቂያ ድርጅት ባለቤት የሆነው ሳምሶን ማሞ ከነ ባለቤቱ ታሰረ

ሐምሌ ፳፯ (ሀያ ስድስት) ቀን ፳፻፬ ዓ/ም
ኢሳት ዜና:-የኢትዮ-ቻናል ጋዜጣ ማኔጂንግ ዳይሬክተርና የሳምሶን አድቨርታይዚንግ ዋና ስራ አስኪያጅ ጋዜጠኛ ሳምሶን ማሞ እና የኢትዮ-ቻናል ጋዜጣ አሳታሚ የዜድ ፕሬስ ዋና ስራ አስኪያጅ ወ/ሮ ዘውድነሽ ታደሰ ባለፈው ሐሙስ በፖሊስ ቁጥጥር ስር ውለዋል
ወደ 6 የሚሆኑ መለዮ የለበሱና ሲቪል የላንቻ ፖሊስ ጣቢያ አባላት ጋዜጠኛ ሳምሶን ማሞን አስገድደው የያዙት ሐሙስ ማለዳ ወደ ቢሮው በሚገባበት ወቅት ነበር፡፡
የኢትዮ-ቻናል ጋዜጣ ዋና ስራ አስኪያጅ ወ/ሮ ዘውድነሽ ደግሞ ባለቤቷን ጋዜጠኛ ሳምሶን ማሞን ለመጠየቅ ወደ ፖሊስ ጣቢያ ባመራችበት ወቅት በቁጥጥር ስር ልትውል ችላለች፡፡
ሁለቱም በላንቻ ፖሊስ ጣቢያ በእስር ላይ እንዲቆዩ ከተደረገ በኋላ በነጋታው (ትላንት አርብ) ፍርድ ቤት እንዲወሰዱ ተደርጓል፡፡ ይሁንና የከፍተኛ ፍርድ ቤት 17ኛው ችሎት ጠዋት በዋለው ችሎት ባልታወቀ ሁኔታ ጉዳያቸውን አልተመለከተውም፡፡
ታሳሪዎቹ ከሰዓት በኋላ እንደሚቀርቡ የተገለፀ ቢሆንም ለህትመት እስከገባንበት ሰዓት ድረስ አሁንም ምክንያቱ በውል ባልታወቀ ሁኔታ ችሎት ያልቀረቡ ሲሆን፤ ከእስርም አልተለቀቁም፡፡
ጋዜጠኛ ሳምሶን ማሞና ወ/ሮ ዘውድነሽ ታደሰ የተከሰሱበትን ምክንያት ፍርድ ቤት ባለመቅረባቸው በውል ለማወቅ አልተቻለም፡፡
እስካሁን በተገኘው መረጃ መሰረት ሳምሶን እና ባለቤቱ የታሰሩት ከንግድ ሚኒስቴር ጋር የተያያዘ ሳይሆን እንዳልቀረ ተጠቁሟል።
ስለ ጉዳዩ የተጠየቁት የንግድ ሚኒስቴር የህዝብ ግንኙነት ክፍል አቶ አብዱራህማን ሰዒድ፦ ‹‹በጉዳዩ ላይ በሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ደረጃ የደረሰን መረጃ የለም›› ሲሉ፤ የቂርቆስ ክፍለ ከተማ ንግድና ኢንዱስትሪ ጽ/ቤት ኃላፊ የሆኑት አቶ ነስረዲን ሻፊ ግን ጉዳዩን እንደሚያውቁ ቢናገሩም፤ ዝርዝር መረጃ ከመስጠት ግን ተቆጥበዋል፡፡

ሳምሶን ማሞ የገዥው ፓርቲ ጠበቃ ነኝ ይል የነበረ ከመሆኑም በላይ “ኢትዮ ቻነል” በተሰኘች ጋዜጣው ተቃዋሚዎችን ሲዘልፍና በጋዜጠኝነት ስም ቃለ-ጉባኤያቸውን እያወጣ ሲያትም የነበረ ግለሰብ ነው።
ዜናውን ያጠናከረው ደብረብርሀን ብሎግ ነው።

No comments:

Post a Comment