Translate

Thursday, August 2, 2012

ምናባዊ ቃለ-ምልልስ

Dereje habtewold
 
ምናባዊ ቃለ-ምልልስ
ደረጀ
ጥያቄ፦ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በምን ሁኔታ ላይ ይገኛሉ? የት ነው ያሉትስ?
መልስ፦ እነዚህ ወገኖች የትራንስፎርሜሽኑን እቅድ ይፋ ስናደርግ ፦”ፖለቲካዊ ውጥረቱን ለማርገብ የተቀየሰና ሊሳካ የማይችል እቅድ ነው እያሉ ፕሮፓጋንዳ ሲነዙ የነበሩ ናቸው”
ጥያቄ፦ ጠቅላይ ሚኒስትሩ አሉ? ወይስ የሉም? መቼስ ወደ ሥራቸው ይመለሳሉ?
...
መልስ፦”…ከዚያም የህዳሴውን ግድብ ስንጀምርም፤ በተመሣሳይ መንገድ ፦“መንግስት ይህን ታላቅ ግድብ እሠራለሁ ብሎ የተነሳው፤ በሰሜን ምስራቅ አፍሪቃ የተነሳው ዓይነት አብዮት እንዳይነሳበት የህዝብን አቅጣጫ ለማስለወጥ ነው የሚል ፕሮፓጋንዳ ማራገብ ጀመሩ…”
ጥያቄ፦ “ክቡር ጠ/ ሚኒስትሩ ደክመዋል፤ከዚያም አልፎ አርፈዋል የሚሉ ዘገባዎች እየወጡኮ ነው።
መልስ፦ “እህ … እነዚህ ወገኖች አሁንም የጠቅላይ ሚኒስትሩን ጤንነት በተመለከተ አሉባልታ እየነዙ ያሉት፤ ልማታችንን በማደናቀፍ የሚናፍቁትን የዓረብ አብዮት ለማስነሳት ካላቸው ከንቱ ምኞት በመነሳት ነው፤ይህ ግን እንደማይሳካላቸው ያውቁታል። የኢትዮጵያ ህዝብ ባለፉት 20 ዓመታት ያጣጣማቸውን የልማት ድሎች በተጨባጭ ተገንዝቧቸዋል። ከእንግዲህ ወደ ሁዋላ አይመለስም”
ጥያቄ፦”ክቡር ሚኒስትር፤ እስካሁን ስለ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ጤንነት ላቀረብኩት ጥያቄ የሰጡኝ ቀጥተኛ ምላሽ የለም”
መልስ፦”እህ. እ….ክቡር ጠ/ሚ/ሩ በጥሩ የጤንነት ሁኔታ ላይ ይገኛሉ።.. ከእንግዲህ በእርሳቸው ጤንነት ዙሪያ የሆነ ነገር በተባለ ቁጥር ፤መንግስት ለእያንዳንዷ ነገር መልስ የሚሰጥበት ሁኔታ አይኖርም”(ይህች ምላሽ ቃል በቃል ከኤርትራው ማስታወቂያ ሚኒስትር ከአቶ አሊ አብዶ የተወሰደች ትመስላለች) እናም… ሀኪም ያዘዘላቸውን እረፍት ጨርሰው ወደ ሥራቸው ይመለሳሉ ብለን እናስባለን።
ጥያቄ፦ እረፍቱ እስከ መቼ ነው?አቦይ ስብሀት በአስር ቀናት ውስጥ ይመሳሉ ቢሉንም ፤ያተረፍነው ነገር፦
<ትመጣለች ብዬ- ሳይ ማዶ ሳይ ማዶ
የልጅነት ዓይኔ- ሟሟ እንደ በረዶ> የሚለውን ዘፈን ማንጎራጎር ብቻ ነው። እርስዎ በትክክል ይንገሩን? እስከ መቼ እረፍታቸውን ጨርሰው -መቼ ወደ ሥራቸው ይመለሳሉ?
መልስ፦እሱን በትክክል መናገር አይቻልም።
ጥያቄ፦ ለምን?
መልስ፦ በዚህ ጉዳይ ላይ ግምት ለማስቀመጥ አልቻልንም፤ ነገሩ ከኢህአዴግ አቅም በላይ እየሆነ ነው።
ጥያቄለ፦ነገሩ ከኢህአዴግ አቅም በላይ ከሆነ፤ በማን ቁጥጥር ስር ሊሆን ይችላል?
መለስ፦ እ…እ..እ…በዋነኛው አለቃ ቁጥጥር ሥር ሳይወድቅ አልቀረም።
ጥያቄ፦ ከኢህአዴግ በላይ አለቃ አለ እያሉኝ ነው?
መለስ፦አዎ!
ጥያቄ፦ እንዴት ሊሆን ይችላል? ኢህአዴግ እኮ የፈለገውን የሚያስር፤ የፈለገውን የሚፈታ፤ ያሻውን የሚሾም ሲያሻው የሚሽር፤ ለወደደው የሚሰጥ፤ ከጠላው የሚነጥቅ ..ከሁሉም በላይ የሆነ ትልቅ ፓርቲ ነው። ተራሮችን ካንቀተቀጠው ትውልድ በላይ፤ ማን አለ ነው የሚሉኝ?”
መልስ፦ “ ተራሮችን የሚያጨስ”
ጥያቄ፦”ተራሮችን የሚያጨስ?!”
መልስ፦”አዎ! ትለቁ ተራራችንን ከቁጥጥራችን ውጪ በሆነ መልኩ እየጨሰብን ነው”
ጥያቄ፦ እኮ እሱ ማነው ተራራችንን እያጨሰ ያለው…?
መልስ፦በአማኞች መጽሐፍ ላይ <ተራሮችን በ ዓይኖቹ ብቻ የሚያጨስ > ተብሎ ተፃፈለት አካል መሆን አለበት ብለን እንገምታለን።
ጥያቄ፦ ከኛ ንጉስ በላይ እውቀትና ሀይል ያለው?
መልስ፦ አለው ሲሉ እንሰማለን?
ጥያቄ፦ ስሙን ማን እያሉ እንደሚጠሩት ሊገልጹልኝ ይችላሉ?
መልስ፦ የነገስታት ንጉስ!
አመሰግናለሁ!
-------------------------------------------…………--------------------------……..-----------------------------
<እንደ ንስር ወደ ሰማይ ብትወጣ፣ቤትህን በክዋክብቶች መካከል ብትሠራ፤ ከዚያ አወርድሀለሁ ይላል የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር>

No comments:

Post a Comment