Translate

Tuesday, August 14, 2012

አቦይ ስብሐት “አዲስ አድማስ ጋዜጣ ውሸቱን ነው መለስ በቤታቸው የሉም” አሉ


Abe Tokchaw
ስለ አቶ መለስ ዜናዊ ማውራት ደክሞኝ ነበር። ሳስበው ሳስበው እርሳቸው የሆኑትን ሆነው ደከመኝ ሳይሉ እኔ እንዴት ደከመኝ እላለሁ ብዬ ተፀፅቻለሁ። መቅደላዊት የተባለች ወዳጄም ከሪያድ በሰደደችልኝ አስተያየት ሀዘኑን እንረሳው ዘንድ ስለርሳቸው መጨዋወታችንን እንቀጥል እንጂ ድንኳን ሳይነሳ የምን ዝም ዝም ነው የሚል ወቀሳ ሰንዝራልኛለች። እኔም በሆዴ የምን ሀዘን ብዬ ሳበቃ  “እውነት ግን ምን ነካኝ…!” ብዬ ሂሴን ውጫለሁ!

አሁን በቅርቡ ከኔ በላይ ውስጥ አዋቂ ላሳር ያለው አዲስ አድማስ ጋዜጣ፤ “ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ በቤተ መንግስት እያገገሙ ነው” በሚል ርዕስ ባሰፈረው ዘገባ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከአራት ባለስልጣናት ጋር እየተመካከሩ በቤታቸው ውስጥ የጠቅላይነት ሚናቸውን እየተወጡ ነው የሚል ሀተታ አቅርቦልን ነበር።
እርግጥ ነው በርካታ የአራዳ ልጆች የጋዜጣውን ዘገባ በጥርጣሬ ነበር የተመለከቱት። አንዳንዶቹም “ጠቅላይ ሚኒስትሩ በቤተ መንግስት እየገገሙ ነው ወይስ እያገገሙ!?” ሲሉ ጠይቀው ነበር። በአራዶች ቋንቋ “መገገም” ማለት እምቢኝ አልተውም፣ የመጣው ቢመጣ ዘወር አልልም፣ የያዝኩትን ከምለቅ ወገቤ ይላቀቅ ወዘተ. የሚል ትርጉም ቢሰጠው ብዙ አራዶች ይስማሙበታል። በዚህ የትርጉም አግባብ ታድያ አቶ መለስ በቤተ መንገስቱ እውነትም እየገገሙ ከሆነ ሞተውም ሆነ ድነው አይለቁንም ማለት ነው።
የሆነው ሆኖ ትላንት ለኢሳት ሬዲዮ እና ቴሌቪዥን ድርጅት (ኢሬቴድ) (እናንተዬ ኢሳት እና ኢቲቪ ስማቸው እየተመሳሰለ ያለበትን ሁኔታ ልብ አላችሁልኝ!?) እና አቦይ ስብሀት ለኢሳት ሲናገሩ አዲስ አድማስ ጋዜጣ መለስ ቤተ መንግስት ውስጥ ናቸው ያለው ውሸቱን መሆኑን ተናግረዋል!  አቦይ ስብሀትን አመስግነን አዲስ አድማስን “ሼ” ብለን ስለጠቅላይ ሚኒስትራችን ጉዳይ ዳግም ለማውራት ተነሳሽነታችን እንደመጣ በይፋ እንናገራለን!
በርሰቸው ጉዳይ ሌላም ጨዋታ አለኝ!

No comments:

Post a Comment