Translate

Sunday, August 12, 2012

በማሌዥያ ጫት ይዛ የተገኘችው ኢትዮጵያዊ ተከሰሰች


ነሀሴ ፭ (አምስት) ቀን ፳፻፬ ዓ/ም
ኢሳት ዜና:-የተከለከለ ዕጽ  በማዘዋወር የተጠረጠረችው ኢትዮጵያዊቷ የቤት እመቤት ጫት ይዛ በመገኘቷ ትናንትና በፍርድ ቤት ክስ እንደተመሰረተባት የተለያዩ የማሌዥያ የዜና አውታሮች ዘገቡ።
የ36 ዓመቷ ሙና መሃመድ ኢብራሂም፣ እ.ኤ.አ ሃሙስ ኦገስት 2/ 2012 የማሌዥያው  ኬ.ኤል ዓለም አቀፍ አይሮፕላን ማረፊያ ውስጥ  90 ኪሎግራም የሚመዝን ካቲኖን የተሰኘ እፅ ወይንም ጫት ይዛ በመገኘቷ በቁጥጥር ስር እንደዋለች ታውቋል።

ነዋሪነቷ ካናዳ እንደሆነ የተገለፀው ወ/ሮ ሙና መሃመድ የሁለት ልጆች እናት ስትሆን፣ ጉዳዩን የያዘው ፍርድ ቤት የተገኘው እጽ በባለሙያዎች ተመርምሮ ሪፖርቱ እንዲቀርብለት በማዘዝ ከሁለት ወራት በኋላ ለኦክቶበር 16 ቀጠሮ መያዙ ታውቋል። ተከሳሿ እስከሚቀጥለው ቀጠሮ ድረስ በማረፊያ ቤት እንድትቆይ ፍርድ ቤቱ ወስኗል።
ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ከኢትዮጵያ ወደ ውጭ አገር የሚላከው የጫት መጠንና በከፍተኛ ሁኔታ እያደገ የመጣ ሲሆን፣ በዚህም የተነሳ “የአገር ውስጥ ፍጆታን ለመቀነስና ወደ ውጭ የሚላከውንየጫት ምርት ለማሳደግ ያስችላል” የተባለ ተጨማሪ የጫት ኤክሳይዝ ታክስ ህግ ተዘጋጅቶ ከሶስት ሳምንታት በፊት በሕወሃት/ኢሕአዴግ ፓርላማ መጽደቁ ይታወሳል።
በዚህ ሕግ መሰረት ለአገርውስጥ ፍጆታ በሚውለው ጫት ላይ በኪሎ ግራም 5 ብር የኤክሳይዝ ታክስ እንዲከፈልበት ተደንግጓል። ጫትን በአደገኛ አደንዛዥ እጽነት ፈርጀው ወደአገራቸው እንዳይገባ የከለከሉ በርካታ አገራት ቢኖሩም፣ የተቀነጠበ ትኩስ ጫት በየዕለቱ  ከኢትዮጵያ እየተጫነ አሜሪካን ጨምሮ በተለያዮ የዓለማችን አገሮች በሕጋዊ መንገድ ለሽያጭ እንደሚቀርብ ይታወቃል ሲል ቅዱስ ሃብት በላቸው ከአውስትራሊያ ዘግቧል።

No comments:

Post a Comment