Translate

Tuesday, April 2, 2013

አዲስ አበባ በነዋሪነት የማታውቃቸው ድምጽ ሊሰጧት ነው


ከእሁድ እስከ እሁድ

(የሳምንቱ አጫጭር ዜናዎች)
map of eritrea


በኤርትራ “ውስጣዊ ትርምስ” ያሰጋል ተባለ
በኤርትራ እየጎላ የሄደው ያለመረጋጋት፣ እየተገለለች የሄደችውን አነስተኛ ሀገር በውስጣዊ ትርምስ ውስጥ ሊከት ይችላል እንደሚችል የዓለም አቀፍ የቀውስ ቡድን International Crisis Group የተባለው ድርጅት ባወጣው ዘገባ ገለጸ። ለሰላማዊ የስልጣን ሽግግር የሚያመች ስርአት ባለመኖሩም ወታደራዊው ሀይል የመሪነት ሚና ሊጫወት እንደሚችል ስጋቱን አስታውቋል። ጎልጉል በኤርትራ መፈንቅለ መንግስት ይገመታል ሲል መዘገቡ ይታወሳል።
ባለፈው ዓመት የኢትዮጵያ ወታደሮች ሁለት ጊዜ ወደ ኤርትራ ለመግባት መቻላቸውና በያዝነው ዓመት ቀደም ሲል በሁኔታዎች ያልተደሰቱ ወታደሮች ለማመጽ መሞከራቸው ራሱ የኤርትራ ወታደራዊ ሃይል ያለበትን “ደካማ ሁኔታ” እንዳጋላጠው የቡድኑ የአፍሪቃ ፕሮጀክት ስራ አስኪያጅ ሴድሪክ ባርነስ መናገራቸውን ቪኦኤ አመልክቷል።
የፕሬዚዳንት ኢሳያስ የፖለቲካ አማካሪ አቶ የማነ ገብረአብ እንደተለመደው ሪፖርቱን “ከእውነታው ጋር የሚያገናኘው ነገር የለም” ሲሉ አጣጥለውታል። ኤርትራ ላለፉት ለአራት ተከታታይ ዓመታት በአካባቢው ኢኮኖሚያቸው እጅግ እያደገ በመሄድ ላይ ካሉት ሀገሮች መካከል እንደምትፈረጅ፣ በማህበራዊ ዘርፍም የሚደነቅ ስኬት ማስመዝገቧንና በአሁኑ ወቅት ሀገሪቱ የተረጋጋች እንደሆነች አመልክተዋል። እሳቸው ይህንን ቢሉም ዳቦ ለመግዛት በሌሊት ሰልፍ እንደሚያዝና ከቤተሰብ ቁጥር በላይ መግዛት እንደማይቻል፣ የኑሮ ውድነት፣ የወታደራዊ ግዳጅና አፈና ህዝቡን እንዳማረረው በስፋት አገሪቱን እየለቀቁ የሚወጡ ተወላጆች እየመሰከሩ ነው።
አዲስ አበባ በነዋሪነት የማታውቃቸው ድምጽ ሊሰጧት ነው

(ፎቶ: Guardian)
በሚያዚያ ወር ለሚካሄደው የአዲስ አበባና የወረዳ ምርጫዎች የተመዘገበው መራጭ ቁጥር ከተጠበቀው በታች መውረዱ ያሰጋው መንግስት፣ ከክልል ከተሞች የራሱ ደጋፊ አባላትን በማምጣት በምርጫው እንዲሳተፉ ለማድረግ ስልጠና እንደሰጠ ኢሳት መጋቢት 21 ቀን 2005 ዓ ም ባወጣው ዜና አስታወቀ።
ከክልል የመጡት ሰዎች በተለያዩ ወረዳዎች በሚገኙ የስልጠና ጣቢያዎች በመጪው ምርጫ እንዴት ድምጽ እንደሚሰጡ ስልጠና እየተሰጣቸው ነው። በንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ በነጻነት ትምህርት ቤት 600 ሰልጣኞች ዜናው በተዘገበበት ቀን ስልጠና የተሰጣቸው ሲሆን፣ አብዛኞቹ ሰልጣኞች ቴክኒካዊ የሆኑ ነገሮችን ሲማሩ መዋላቸውንና በምርጫው እለት ወደ አዲስ አበባ ሲመጡ ግር እንዳይላቸው አስፈላጊውን የሲሙሌሽን ትምህርት ሲማሩ መዋላቸውን በስልጠናው የተሳተፈ የድርጅት አባልን በመጥቀስ ኢሳት ዘግቧል። በስልጠናው በጥቅሉ ከ5 ሺህ በላይ በአዲስ አበባ ያልተመዘገቡ የኢህአዴግ አባላት እንደሚካተቱ ከዜናው ለመረዳት ተችሏል።
“ጸልዩ” ባራክ ኦባማ ለማንዴላ “ጸሎት” አደረጉ
እርጅና የተጫናቸው የአፍሪካ ምርጥ ልጅ ኔልሰን ማንዴላ ሆስፒታል መግባታቸውን ተከትሎ ሁሉም ያገራቸው ህዝብ መልካም ዜናቸውን ይናፍቃል። የነጻነት ታጋዩና አስተዋይነታቸው ጎልቶ የሚታየው ማንዴላ ለውጥ ማሳየታቸው ቢነገርም አሁንም ሆስፒታል ናቸው።
ያንን አሰቃቂ የአፓርታይድ ስርዓት ከተገላገሉ በኋላ ስልጣን በያዙ ማግስት ቂም በቀልን አራግፎ በመጣል፣ ለበደሏቸው ጭምር “አገር እናልማ” የሚል መልክት ያስታለለፉት ማንዴላ የደቡብ አፍሪካ ብቻ ሳይሆን የሁሉም አፍሪካ እንቁ ናቸው።
የአሜሪካ ሬዲዮ አማርኛው ክፍል እንደዘገበው የፕሬዚዳንት ጃኮብ ዙማ ቃል አቀባይ ማክ ማሃራጅ የማንዴላን ጤንነት አስመልክቶ ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ ደቡብ አፍሪካዊያን ለማዲባ እንዲፀልዩ መጠየቃቸውን ካበሰረ በኋላ፣ የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማና የቤተ መንግሥታቸው ባልደረቦች ለኔልሰን ማንዴላ ደህንነት ፀሎት ማድረጋቸውን አመልክቷል።
አንደበት
“ሙስሊሙ ሽብርተኛ አይደለም። ባገሬ ላይ ሙስሊም ሆኜ ጺሜን አስረዝሜ፣ ሱሪዬን አሳጥሬ፣ ሴቷም ጸጉሬን ተሸፋፍኜ፣ ገላዬን ሸፍኜ፣ ሀገሬን ወድጄ፣ ህጌን አክብሬ የምትኖርባትን ኢትዮጵያ፤ ማንም ክርስቲያኑም እምነቱን በነጻነት ባገሩ ላይ አውጆ፣ ዋቄፈታም ቢሆን እምነቱን እንደልብ ባገሩ ላይ አውጆ፣ ማናችንም ብንሆን ከህግ በምንወጣበት ጊዜ በህግ የምንጠየቅባትን ኢትዮጵያን እንፈልጋለን …”
ሼኽ ኢማን ካሊድ ኦማር/ Sheik Khaled Omar በሲያትል ከተማ ዋሺንግተን ጠቅላይግዛት ካደረጉት ንግግር የተወሰደ

“… ሱሪ ማሳጠር፣ ጺም ማሳደግ ይቻላል፡፡ መብታቸው ነው፡፡ ጺሙ ግን ቅጫም ካለበት ለራሱም ሆነ ለሌላው ጤና ስለማይሰጥ እንቆርጠዋለን፤ እናቃጥለዋለን … ”
አቶ መለስ በጋዜጣዊ መግለጫና በፓርላማ ከተናገሩት ለንጽጽር የተወሰደ፡፡

የመለስ አረንጓዴ ዘመቻ ተጠናቀቀ፤
“የኮበለሉ የዱር እንስሳቶች ተመለሱ”
ከአምስት ዓመት በፊት በአካባቢው ልምላሜ ብሎ ነገር አይታይም። በገጠር ቀበሌያችን የነበረውን የተፈጥሮ ደን አላግባብ መጠቀማችን በግልፅ ያመለክታል። የአካባቢያችን ደን ለማገዶና ለቤት መስሪያ ሲባል በእጅጉ አውድመነዋል። እንደ ጅብ፤ ነብር፤ ቆቅ፤ ከርከሮ የመሳሰሉትን የዱር አራዊቶች በአካል ቀርቶ ድምፃቸው ከጠፉ ቆይቷል። ከተራራማው ስፍራ የሚወርደው የክረምት ጎርፍ የእርሻ መሬታችን አፈርም ጭምር ሸርሽሮ ቁልቁል ስለሚወስደው የምናምርተው ሰብል እምባዛም ነበር በማለት በትግራይ ክልል ደቡባዊ ዞን የመለስ አረንጓዴ ዘመቻ ተጠቃሚዎች መናገራቸውን ኢዜአ ዘገበ።

(ፎቶ: ONE)
የሰብል ምርታችን በየዓመቱ እየቀነሰም የመንግስት እርዳታ እንድንጠብቅ ዳርጎን ነበር። በዚህ የተነሳ አብዛኛው የአካባቢያችን ሰው በሕገ ወጥ መንገድ የተሻለ ነገር ፍለጋ ወደ ጂዳ የመሳሰሉት የአረብ አገሮች መሰደድ እየተለመደ መጥቷል። ካለፉት አምስት ዓመታት ወዲህ መንግስታችን በቀየሰው የአካባቢ ጥበቃና ተፋሰስ ልማት አቅጣጫ በመሰለፋችን በገጠር ቀበሌያችን ከፍተኛ ለውጥ ማምጣት ችለናል። በእነዚህ ዓመታት ያከናወነውን የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራ ሁለት ጥቅሞችን አግኝተንበታል።
አንደኛ በአፈርና ውሃ ጥበቃው ሥራ ፀዳቂ ተክሎች እየተከልንበት በመሆኑ የአካባቢው ደን መልሶ እንዲያገግም አድርገናል። የምንተክላቸው እጽዋቶችና ዛፎች ከሰውና እንስሳት ንኪኪ ነፃ ሆኖ ስለምንከልለው የገጠር ቀበሌው የደን ሽፋን በአጭር ግዜ እንደለወጥ አግዞታል። በዚህ ምክንያት ካሁን በፊት መጠለያ አሳጥተናቸው ከአካባቢው ርቀው የነበሩትን የዱር እንስሳት ተመልሰው መስፈር ጀምረዋል። አሁን አሁን የዱር አራዊቶቹ በድምፃቸው ብቻ ሳይሆን በአካል ልናያቸው ችለናል። ዛሬ እንደ ጅብ፤ አቦ ሸማኔ፤ ቆቅ፤ ከርከሮ ቁጥራቸው እየተበራከተ ነው። የአካባቢው አርሶአደሮችም ለዱር እንስሳቱ ተገቢው ጥበቃና ከለላ እያደረጉላቸው እንደሆነ ተጠቃሚዎቹን ጠቅሶ ኢዜአ ዘግቧል።
ተገኝወርቅ በተመድ ከፍተኛ ሹመት አገኙ
የተባበሩት መንግስታት ዋና ጸሐፊ ባን ኪ ሙን ኢትዮጵያዊውን ተገኝወርቅ ጌቱን የጠቅላላ ጉባኤና የጉባዔዎች አስተዳደር ረዳት ዋና ጸሃፊ አድርገው መሾማቸው ባለፈው ሳምንት ከተዘገቡት ኢትዮጵያ ነክ ጉዳዮች በበጎ መልኩ ቀዳሚው ነው። በሹመቱ መሰረት አቶ ተገኝወርቅ የመንግሥታ ድርጅት በስሩ የሚያስተዳድርራቸውን 1200 ሰራተኞች ይመራሉ።
የተባበሩት መንግስታት ሹመቱን አስመልክቶ ያሰራጨው ዜና እንደሚያመለክተው አቶ ተገኝወርቅ ባሳዩት ብቃትና ባላቸው እውቀት እንደሆነ አመልክቷል። ላለፉት ሰላሳ ዓመታት በብሄራዊና በዓለም አቀፍ ደረጃዎች በልማት መስክ በመሰማራት ያስመዘገቡት ውጤት እንዲሁም በትምህርት፣ በመንግሥትና በግል ዘርፎች ያከናወኗቸው ሥራዎች ተመራጭ እንዳደረጋቸውም ታውቋል። የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የልማት ፕሮግራም የአፍሪካ ቢሮ ረዳት ዋና ፀሐፊ ሆነው ካለፉት አራት ዓመታት ወዲህ በመሥራት ላይ የነበሩት አቶ ተገኝወርቅ፣ የፕሮግራሙ ሥራ አስፈጻሚ ጽህፈት ቤት ዳይሬክተርና በናይጄሪያ የፕሮግራሙ ተጠሪ ሆነውም ሰርተዋል። በኮሎምቢያ፣ በሮቸስተርና በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲዎችና በሃንተር ኮሌጆች በመምህርነት ማገልገላቸውን በመጥቀስ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ለሹመቱ እንደሚመጥኑ ዘግቧል።
የአባይ ግድብ ሁለተኛ ዓመት ተከበረ
“የአባይ ግድብ እዳ አለብን ጠጋ ጠጋ በሉ”
“በራሳችን ሃብትና ጉልበት እንገነበዋለን” የተባለው የአባይ ግድብ ተሰርቶ እስኪጠናቀቅ በቁርጠኛነት አስፈላጊውን ሁሉ ለማድረግ አርቲስቶች ቃል መግባታቸውን ኢቲቪ አስታወቀ። የውሃ ሚኒስትሩ አቶ አለማሁ ተገኑ በማናቸውም የውጪ ተጽዕኖ ግንባታው እንደማይስተጓጎልና በተያዘለት ጊዜ እንደሚጠናቀቅ አስታውቀዋል።
በሌላ ወገን ደግሞ ለግድቡ ግንባታ ሰራተኞች ሳያወቁ ደሞዛቸው እንዲቆረጥባቸው መደረጉ ቅሬታ ፈጥሯል። ከተለያዩ ወገኖች እንደሚሰማው የኑሮ ውድነት ያስቸገራቸው ዜጎች ግድቡ እንዲገነባ ፍላጎት ቢኖራቸውም ከምኞት ማለፍ አይችሉም። የጀርመን ድምጽ ሬዲዮ ዘጋቢ በግድ ደሞዝ አምጡ የተባሉትን ካነጋገረ በኋላ “በድሬዳዋ የባጃጅ ታክሲ አሽከርካሪዎች ‘የአባይ ግድብ እዳ አለብን ጠጋ ጠጋ በሉ’ የሚል ማስታወቂያ ለጥፈው ማየቴ ታወሰኝ ያለው ትዝ አለኝ” በማለት ትዝብቱን አክሏል።

No comments:

Post a Comment