Translate

Friday, April 19, 2013

“እያንዳንዱ ዜጋ ከራሱ ጋር ይነጋገር” አርቲስት ታማኝ በየነ

images
በታም ገዳ
በኢትዮጵያ ውስጥ እየተካሄደ ያለው አስከፊ የሰብአዊ መብት ረገጣ ይቆም ዘንድ እያንዳንዱ ዜጋ የበኩሉን አሰተዋጽኦ ሊያበረክት እንደሚገባው እና ከራሱ ጋር መነጋገር እንዳለበት ተገለጸ፡፡ይሄ የተገለጸው እርቲስት እና እክቲቬስት ታማኝ በየነ የኢትዮጵያ ሳተላይት ቴሌቭዥን ኢሳት የተመሰረተበት 3ኛ አመት እና ጣቢያውን ለማጠናከር ባለፈው ቅዳሜ ሚያዚያ 13 2013 እኤአ በ አሜሪካው የካሊፎርኒያ ግዛት በሎሳንጀለስ ከተማ በተደረገው የገቢ ማሰባሰቢያ ፕሮግራም ላይ በመገኘት ለተሰበሳቢዎች እና ለኢሳት አጋሮች በሰጠው አሰተያየቱ ነው፡፡
በተለይ አርቲስት ታማኝ የህብር ራዲዮ ዘጋቢ ከሆነው ከዚህ ጸሃፊ (ከታምሩ ገዳ )ጋር ከገቢ የማሰባሰብ ፕሮግራሙ በሁዋላ ባደረገው ቃለምልልስ “ሌላው ቢቀር ልጆቻችን አገራቸውን ጥለው እንዳይሰደዱ እና በአገራቸው ተደላድለው እንዲኖሩ ለማድረግ በአገር ቤት በመካሄድ ላይ ያለውን የግፍ ቀንበር ልንሰብረው ይገባናል፡በሶስት ሺህ ዘመን አለም በተለያዩ የኢኮኖሚ እድገት ላይ ሲገኝ እኛ ግን ከሁሉ አገር በታች በደመ ነፍስ በሚነዳ እና ህግ በሌለበት ብቸኛ አገር ውስጥ እንገኛለን፡፡” ያለው አርቲስት ታማኝ ሁሉም ዜጋ የበኩሉን ጥረት ማድረግ እንዳለበት አስረግጦ የተናገረ ሲሆን አስተያየቱን ሲያራዝምም “እኛ እናልፋልን ነገር ግን ቢያንስ ልጆቻችን ተድላድለው እንዲኖሩ ይህን በደል የማስቆም የሞራል ግዴታ አለብን፡ እነ ታማኝ ወይም እነ እገሌ ምን አደረጉ? የሚባልበት ወቅት ሳይሆን ለምንድን ነው አገሬ ውስጥ ዘወትር ችግር ብቻ የምሰማው? እንደሌሎች አገሮች መሆን የተሳነን ለምንድን ነው? ሲል እያንዳንዱ ዜጋ እራሱን እንደዜጋ ሊጠይቅ ግዴታ አለበት፡፡”ብሏል፡፡

አርቲስት እና አክቲቬስት ታማኝ በየነ
ኢሳትን የመሳሰሉ ነጻ የመረጃ ምንጮች ይስፋፉ ዘንድ ምን መደረግ እንዳለበት የሚያስተላልፈው መልእክት ካለ ተብሎ ከህብር ራዲዮ ለቀረበለት ጥያቄ አርቲስት እና አክቲቬስት ታማኝ ሲመልስ” ይህ አይነቱ ሃሳብ ነው ሊበረታታ የሚገባው ከዛሬ ሶስት አመት በፊት ኢሳት አልነበረም:: ዛሬ ግን ጋምቤላ ውስጥ ችግር ሲፈጠር በኢሳት አማካኝነት ትሰማዋለህ :፡የአማራ ክልል ተወላጆች ከተለያዩ እካባቢዎች በግፍ ሲባረሩ ኢሳት ላይ ወዲያውኑ ትሰማዋለህ:: በሙስሊም ወገኖቻችን ላይ በደል ሲደርስ እንደዚሁ ኢሳት ላይ መረጃውን ትሰማዋለህ፡፡በመረጃ የተደገፈ ዜና ለማግኘት ህዝቡ አስተዋጽኦ ማድረግ አለበት፡፡የህቺ እንግዲህ በሶስት አመት ውስጥ የተገኘ የሁላችን የጥረት ውጤት ነው ፡፡ ሶስት አመት በጣም ትንሽ ጊዜ ነው ፡፡ኢሳት የሶስት አመት ልጅ ነው ፡፡ ልጅን ስናሳድግ ደግሞ ይታመምብናል: ምግብ አይስማማውም፡ብርጭቆ ይሰብራል ይሄን ሁሉ እየተከታተልክ አይደል ልጅህን የምታሳድገው?ኢሳትም እንዲሁ ደካማ ሊሆን ይችላል ነገር ግን ሁሉም ሰው በመተባበር የተሟላ የሚዲያ ተቋም ሊያደርገው ይችላል፡፡ለዚህ መሰሉ በጎ ተግባራት አስተዋጽኦ ማድረግ የእያንዳንዱ ዜጋ ግዴታ ነው፡፡” ብላል፡፡ በስተመጨረሻም የተጠናከረ ስራ ለማካሄድ ምን መደረግ አለበት? ለሚለው ጥያቄ ሲመልስ “ አያንዳንዱ ዜጋ ከራሱ ጋር ይነጋገር:: ወደዚህ ምድር ላይ የምጣሁበት ተልኮዮ ምንድን ነው ? ምን አድርጌ ነው የምሄደው? በእየ ወሩ ለቤተሰቤ 300 ወይም 400 የአሜሪካ ዶላር መላክ? በ ተሻለ ቤትውስጥ ለመኖር ወይም ዘመናዊ መኪና ለማሽከርከር የተሻለ ልብስ ለመልበስ ነው ወደዚህ አለም የመጣነው? እንደእኔ እምነት አገራችን ወደ ተሻለ ደረጃ እንድትሸጋገር ጥረት ማድረግ እያንዳንዱ ዜጋ በሚችለው እና አቅሙ በፈቀደው መጠን ብሄራዊ ግዴታውን ሊወጣ ይገባል ፡፡ቁጭ ብሎ መተችት ለውጥ አያመጣም፡፡አስተዋጽኦ ማድረግ አለብን፡፡በምናምንበት መንገድ በምንም ይሁን የእኔ ፍላጎት እና ስሜት የሚያደላው በዚህ ላይ ስለሆነ እስተዋጽኦ ማድረግ እፈልጋለሁ ብሎ በጉልበት ይሁን በእውቀት በምክር ሊሆን ይችላል ፡፡ይሄ የጥቂት ወገኖች እህላፊነት ተደርጎ መወስድ የለበትም ፡፡ የሁሉም ወገን እርብርቦሽ ሊሆን ይገባል ፡፡” ብሏል::
በዚህ የገቢ ማሰባሰብ ፕሮግራም ላይ ለተገኙ በመቶዎች ለሚቆጠሩ የሎሳንጀለስ ከተማ ነዋሪዎች የገዢው የኢሃአዲግ መንግስት የፕሮፓጋንዳ መሳሪያዎች የሆኑት የመገናኛ ብዙሃናትን ጨምሮ ከተለያዩ የአገር አቀፍ እና የአለማቀፍ የዜና አውታሮች ያሰባሰባቸው በምስል እና በጽሁፍ የተደገፉ ማስረጃዎችን ለታዳሚዎቹ በማቅረብ በኢትዮጵያ ወገኖች ላይ በ ሀገር ውስጥ ሆነ በውጪ ሀገራት የደረሱት እና በመድረስ ላይ ያሉትን ዘግናኝ የሆኑ የሰብአዊ መብት ጥሰቶችን ለግንዛቤ ማስጨበጫነት ይረዳ ዘንድ ያቀረበ ሲሆን ሁሉም ኢትዮጵያዊ ዜጋ ለአንድ አፍታ ቆም ብሎ የት ላይ እንደሆንን እና በወገኖቻችን ላይ ምን አይነት ግፍ እየትፈጸመ እንደሆነ ሊያስተውል ይገባል ሲል ወገናዊ ጥሪውን አቅርቧል፡፡
ወጣት ሄኖክ የሼጥላ ግጥሙን ለታዳሚዎች ሲያሰማ (ከግራ ወደ ቀኝ ሃጄ ነጂብ መሃመድ እና አርቲስት ታማኝ በየነ)
በገቢ ማሰባሰብ ፕሮግራሙ ላይ የኢትዮጵያ ሙስሊሞችን በመወከል ንግግር ያደረጉት እውቁ የሰብአዊ መብት ተሟጋች ሃጂ ነጂብ መሃመድ “ ህገመንግስታዊ መብታችን ይከበር ያሉ ሙስሊም ወገኖቻችን ካለፈው አንድ አመት ትኩል ጀምሮ በአገዛዙ የጸጥታ ሃይሎች ለእስራት ፡ ለግርፋት እና ለስደት የተዳረጉበት የመብት ጥያቄያቸው ስር ሰዶ እና የክርስትና እምነት ተከታይ ወገኖቻችን ድጋፍ አግኝቶ አሁን ካለንበት ደረጃ ደርሷል፡፡ከዚህ በሁዋላ ወደ ሁዋላ መመለስ ትልቅ ስህተት ስለሚሆን በተያያዝነው ሰላማዊ የመብት ጥያቄ ክርስቲያኑ እና ሙስሊሙ ማህበረሰብ እጅ ለእጅ ተያያዞ አገዛዙን በቃህ ሊለው የግድ ይላል፡፡” ብለዋል፡፡ ሃጂ ነጂብ ንግግራችውን በማራዘም “ነብዩ መሃመድ ተከታዮቻቸው በ1034 አመት በፊት በመካከለኛው ምስራቅ ግድያ እና እንግልት በበዛባቸው ወቅት ሴት ልጃቸውን ጨምሮ ወደ ኢትዮጵያ (ሃበሻ መሬት) ሄዱ በዚያ ማንንም ሰው የማይበድል ክርስቲያን መሪ አለ በማለት ጎረቤት አገሮች የሆኑትን አነ ሶሪያ እና የመንን ትተው ወደ ኢትዮጵያ እንዲሰደዱ አዘዋል ፡፡ ታዲያ የተገፉ ወገኖችን በመቀበል ለአለም አርያ የነበረች አገር ኢትዮጵያ ዛሬ በኛ ዘመን እንዴት አላህ ዋክበር!!( እግዜአብሄር ታላቅ ነው!!) ያሉ ዜጎች መብታቸው ተንፍጎ ይታሰሩባታል?” ሲሉ የወቅቱን የኢትዮጵያ የሰብአዊ መብት ሁኔታን ከቀድሞው እንግዶችን እንድ ራስ አድርጎ የመቀበል ጥሩ ባህል ጋር በማነጻጸር በጥያቄ መልክ ለመግለጽ የሞከሩ ሲሆን በቀርቡ የገዢው ፓርቲ ለፕሮፓጋንዳ መሳሪያነት የሚጠቀምበት ኢቲቪ “ጀሃዳዊ ሃራካት” በሚል ርእሱ እና መልእክቱ የማይጣጣም ፕሮግራም በማዘጋጀት በሙስሊም ወገኖች ላይ ለማላገጥ የተጠቀመበትን ዘዴ እርቃኑን መቅርቱን አጋልጠዋል፡፡ በአሁን ወቅትም የእገዛዙ የጸጥታ ሃይሎች የታሳሪዎች ቤተሰቦችን በመቅረብ ታሳሪዎቹ ይቅርታ እንዲጠይቁ የማግባባት ዘመቻ መጀመራቸውን ገልጸው “ ለመሆኑ የተበደለ እና መብቱን የተገፈፈ ሰው በየት አገር ነው ይቅርታ የሚጠይቀው ? ይህ አይነቱ አካሄድ በራሱ የአገዛዙ ኤፍትሃዊነትን ነው የሚያመላክትነው ፡፡ “ብለዋል፡፡
ሄኖክ የሺጥላ የተባለ በሎሳንጀለስ ከተማ የሚኖር ወጣት “ናፍቆት” በሚል ግጥሙ በአገዛዙ የጸጥታ ሃይሎች ለእስራት የተዳረገው ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ እና ህጻን ልጁ ናፍቆትን የውስጥ ስሜትን በሚኮረኩር መልኩ በምናባዊ ግጥሙ አወድሷቸዋል፡፡ በተጨማሪም ወጣት ሄኖክ “ለምንድን ነው ዛሬ የምናደደው?” በሚለው በሁለተኛው ግጥሙ የአገዛዙ ቁንጮ የነበሩት መለስ ዜናዊን ኮንኗል፡፡
የጨረታ ስነስርአቱ ከመካሄዱ በፊት የሚያሳይ ፎቶ
ለኢሳት ማጠናከሪያ ይሆን ዘንድ መነሻ ዋጋው 500 ዶላር ሆኖ ለጨረታ የቀረበ አንድ ታብሌት ዘመናዊ ላፕቶፕ ከሰባት ሺህ የአሜሪካ ዶላር በላይ የተሸጠ ሲሆን አሸናፊው ግለሰብም በሳንዴያጎ ከተማ ለሜድረገው ተመሳሳይ የገንዘብ ማሰባሰቢያ ፕሮግራም ይውል ዘንድ ታብሌት ላፕቶፑን መልሰው ሰጥተዋል ፡፡አንዲት የሎሳንጀለስ ከተማ ነዋሪ በበኩላቸው ኢሳትን ለምደገፍ በሚደረገው ረብርቦሽ ላይ የበኩላቸውን አስተዋጽኦ ለማበርከት ሲሉ በእጃቸው የፈተሉትን ዘመናዊ ሙሉ የአገር ልብስ ለጨረታ እንዲቀርብላችው ለአዘጋጆቹ ሰጥተዋል፡፡ በሎሳንጀለስ ከተማ የኢሳት ድጋፍ ሰጪ አባላትም በስፍራው የተገኙት ሁሉንም ተሳታፊዎችን በማመስገን ኢሳትን በሁሉም መልኩ የመደገፍ ርብርቦሹ እንዲቀጥል ጥሪያቸውን አቅርበዋል፡፡ ( tamgeda@gmail.com)

No comments:

Post a Comment