Translate

Thursday, November 15, 2012

ለዴሞክራሲ ያልበቃው የኢትዮጵያ ህዝብ/ኢህአዴግ ???

ዴሞክራሲ ለማንኛውም ሰብአዊ ፍጡር የተገባ ጤናማ የአስተዳደር ስርዓት ነው፡፡ የአንድ ህብረተሰብ የስልጣኔ ደረጃ ዴሞክራሲን ለመረዳትና ለመተግበር በሚደረገው እንቅስቃሴ ላይ የሚኖረው አስተዋፅኦ ይለያይ እንጂ ለዴሞክራሲ ብቁ ያልሆነ ህዝብ የለም፡፡ 
ቅርቡ የመወያያ አጀንዳ ሆነው ከሰነበቱ ፖለቲካዊ ጉዳዮች ውስጥ የሚጠቀሰው አንድ የህወሓት አንጋፋ ባለስልጣን “የኢትዮጵያ ህዝብ ለዴሞክራሲ ብቁ አይደለም” በማለት ህዝቡን መዝለፋቸውን የሚገልፀው መረጃ ነበር፡፡ እኚህ አንጋፋ ባለስልጣን በተለያዩ ጊዜያት የህወሓት/ኢህአዴግን እኩይ አላማና ፍላጎት ያለአንዳች እፍረት በይፋ በመናገር አነጋጋሪ መሆን ጀምረዋል፡፡ 
 ሰውየው ሆነብለውም ይሁን አምልጧቸው የሚናገሯቸው ሀሳቦች፣ የአምባገነናዊ ስርዓቱን እኩይ አስተሳሰብ ለአደባባይ እንዲውል የሚያደርግ ከመሆኑም በላይ የኢትዮጵያ ህዝብ ምን አይነት አስተሳሰብ ባላቸው አካላት እየተገዛ እንደሆነ እንዲገነዘብ የሚረዳ ነው፡፡

በመሠረቱ ዴሞክራሲ ለማንኛውም ሰብአዊ ፍጡር የተገባ ጤናማ የአስተዳደር ስርዓት ነው፡፡ የአንድ ህብረተሰብ የስልጣኔ ደረጃ ዴሞክራሲን ለመረዳትና ለመተግበር በሚደረገው እንቅስቃሴ ላይ የሚኖረው አስተዋፅኦ ይለያይ እንጂ ለዴሞክራሲ ብቁ ያልሆነ ህዝብ የለም፡፡
ዴሞክራሲ የሚሰጠው ነፃነት አስተዋይነትና የኃላፊነት ስሜትን አጣምሮ የያዘ መሆኑ የማይዘነጋ ሀቅ ነው፡፡ ነፃነትን ግዴታን ከመወጣት ጋር አስተሳስሮ ለመጠቀምም ስልጣኔ የማይናቅ ፋይዳ አለው፡፡ የኢትዮጵያ ህዝብ ለዘመናት በአምባገነናዊ ስርዓትቶች ስር እንደመኖሩ ገዢዎቹ ግዴታውን እየነገሩ መብቱ እየከለከሉት ኖሯል፡፡ 
ኢትዮጵውያን እንደነበረን የስልጣኔ ቀደምትነትና ታሪካዊነት የሰለጠነ ዴሞክራሲያዊ ስርአት አልገነባንም፡፡ አሁን በስልጣን ላይ ያለው ስርአትም ለህዝቡ የሚመጥን አይደለም፡፡ ዴሞክራሲያዊ ስርአት በሀገራችን ለዘመናት ሳይገነባ ለመቆየቱ ተጠያቂነቱ የሚያርፈው በተለያዩ የዘመን ምዕራፎች ህዝቡ ጫንቃ ላይ ተፈናጠው የኖሩ አምባገነን ገዢዎቹ ላይ እንጂ ህዝቡ ላይ መሆን የለበትም፡፡

የኢትዮጵያ ህዝብ ለዴሞክራሲ ያለውን ቅርበት ለማረጋገጥ ብዙ ታሪካዊ እውነታዎችን መመልከት የሚቻል ቢሆንም ከጥቂት ዓመታት በፊት በምርጫ 97 ህዝቡ ያሳየውን ዴሞክራሲያዊ ብስለት መመልከቱ በቂ ማስረጃ ነው፡፡

በወቅቱ ህዝቡ የተገኘውን አንፃራዊ ነፃነት እንደ እድል በመጠቀም፣ ያሳየው ለለውጥ የመነሳሳት እና በነቂስ ወጥቶ መንግስትን በምርጫ ካርድ የመለወጥ የደረገው ጥረት ዴሞክራሲያዊነቱን የሚያሳይ ነበር፡፡ በአንፃሩ አምባገነኑ የኢህአዴግ መንግስት በወቅቱ የህዝቡን የለውጥ ማነሳሳት ለመቀልበስ የወሰዳቸው ኢሰብአዊ የጭፍጨፋና የሰብአዊ መብት ጥሰት እርምጃዎች የባለስልጣናቱን በጠብመንጃ የማሰብ ኢዲሞክራሲያዊነት የሚያረጋግጥ ነበር፡፡

ኢህአዴግ አሁንም ከ21 አመት በኋላ ዴሞክራሲያዊነትን ለመላበስ አልቻለም፡፡ ይልቁኑም የአፈና ስርዓቱን በተለያዩ ዘዴዎች በማጠናከር አምባገነናዊነቱን ይበልጥ አግዝፎታል፡፡ እውነታው ይህ ሆኖ ሳለ የስርአቱ ሁነኛ ባለስልጣን “የኢትዮጵያን ህዝብ ለዴሞክራሲ ብቁ አይደለም” ማለታቸው 21 አመት ሙሉ ሲያስተዳድሩት የኖሩትን ህዝብ አለማወቃቸውን የሚያሳይ ነው፡፡ 
የኢትዮጵያን ህዝብ በቅርበት ለማየት ቢችሉ ህዝቡ ምን ያክል ለዴሞክራሲ ቅርብ እንደሆነና በአንፃሩ ኢህአዴጋውያኑከዴሞክራሲ ምንያክል እንደራቁ ለመገንዘብ በቻሉ ነበር፡፡ የኢትዮጵያን ህዝብ ንቀውና ረግጠው ሲገዙ የኖሩት ኢህአዴጋውያን ዘመን እንደተለወጠ፣ ለነፃነቱና ለብሔራዊ ክብሩ የትኛውንም መስዋዕትነት ለመክፈል የተዘጋጀ ትውልድ ኢትዮጵያ እንዳፈራች ሊገባቸው ያስፈልጋል፡፡
አምባገነናዊ ስርአትን ገንብቶ ህዝብን እየናቁና እያዋረዱ መግዛት ከአሁን በኋላ አያዋጣም፡፡ ለሁላችንም የሚበጀው በጊዜ ዴሞክራሲያዊ ስርዓት እንዲሰፍን የየበኩላችንን ጥረት ማድረግ ነው፡፡ ዴሞክራያዊ ስርአት ሳይሰፍን የሀገሪቱ ችግሮች ለመፍታት አይሞከርም፡፡ አምባገነኑ የኢህአዴግ መንግስትም ሊገነዘብ የሚገባው ለፓርቲውም ሆነ ለሹማምንቱ የሚበጀው ይኸው መሆኑን ነው፡፡
ታሪክ እንደዘከረውና የቅርብ ጊዜዎቹ የሰሜን አፍሪካ አምባገነኖች ፍፃሜም ፍንትው አድርጎ እንደሚያሳየው ለዘላለም ተረግጦ የሚኖርና ህዝብና ለዘላለም ረግጦ የሚኖር አምባገነን አለመኖራቸው ነው፡፡

No comments:

Post a Comment