Translate

Wednesday, November 28, 2012

በናዝሬት በአንድ አመት ውስጥ ብቻ 4 ከንቲባዎች ተቀያየሩ


ኢሳት ዜና:-በቅርቡ በተደረገ ግምገማ ላለፉት አራት ወራት በስልጣን ላይ ቆይተው የነበሩት የናዝሬት ወይም የአዳማ ዋና ከንቲባ እና ከእኝሁ ባለስልጣን ጋር ግንኙነት አላቻው የተባሉት የከተማዋ የኦህዴድ የድርጅት ጉዳይ ሀላፊ ከቦታቸው እንዲነሱ ተደርጓል።ገምጋሚዎቹ የኦሮሚያ ክልል ባለስልጣናት የነበሩ ሲሆን ግምገማውም በመልካም አስተዳዳር፣ በከተሞች እድገት፣ በኪራይ ሰብሳቢነትና በልማት ሰራዊት አደረጃጃት ላይ ያተኮረ ነበር።

የከተማው ከንቲባ የነበሩት አቶ ጉታና የከተማው የልማት ሀላፊ የነበሩት አቶ ከፍያለው የከተማዋን መሬት በመቸብቸባቸው ፣ ህዝብ ያሰማውን ሮሮ ተከትሎ እንዲወርዱ ተደርጓል።

ከእርሳቸው በፊት የነበሩት 3ቱ ከንቲባዎችም እንዲሁ መሬት በመቸብቸብና በሙስና ከሀላፊነት መነሳታቸው ይታወቃል። ከንቲባው አቶ ጉታ የፓርላማ አባል ሲሆኑ፣ በከተማዋ ውስጥ የሚታየውን የአስተዳዳር ብልሹነትና ስር የሰደደውን ሙስና እና መሬት ዝርፊያ ያስቆማሉ ተብሎ እምነት ተጥሎባቸው ነበር። ይሁን እንጅ ባለስልጣኑ ከሌሎች ግብረአበሮቻቸው ጋር በመሆን ከፍተኛ ሙስና ውስጥ መግባታቸው ለማወቅ ተችሎአል።
የድርጅት ቢሮ ሀላፊው አቶ ሳዳት በበኩላቸው በአዳማ ውስጥ ባሉ የሀላፊነት ቦታዎች ላይ የሚገኙ ሰዎችን እንዲመደቡ ያደረጉዋቸው ከአርሲ አካባቢ የተወለዱትን ብቻ ነው በሚል በዘርኝነት ተገምግመው ወርደዋል።
አንድ የኦህዴድ የማእከላዊ ኮሚቴ አባል ለኢሳት እንደገለጹት የድርጅቱ መሪዎች ከላይ እስከታች በሙስና የተዘፈቁ በመሆናቸው ፣ በየአካባቢው እየተገመገሙ የሚወርዱ የከተማ ከንቲባዎችና የድርጅት አመራሮች ወደ ሌሎች ቦታዎች ተመልሰው ይመደባሉ። በዚህም የተነሳ ሙስና ውስጥ የተዘፈቀ ባለስልጣን ምንም ችግር ሳይገጥመው ወደ ሌላ አካባቢ ሄዶ ይመደባል ብለዋል። በናዝሬት ውስጥ የሚታየው አይን ያወጣ የመሬት ዝርፊያ ፣ ነዋሪውን በእጅጉ እያሳሰበ ይገኛል።

    No comments:

    Post a Comment