Translate

Thursday, November 22, 2012

ወይ አለማፈር… ከሥረጉተ ሥላሴ


ከሥረጉተ ሥላሴ 21.11.2012

መገረም ማለት አንዳንድ ጊዜ ከቃሉ በላይ ለሆኑ ድርጊቶች ገላጭ ሳይሆን ይቀርና ያናደኛል። ምን መናደድ ብቻ? ቁጭቴንም ይ – ነ – ድ – ለ – ዋ -ል …
መቼም እኔ ወጣት እያለሁ ተግቼ የማሌሊትን ራዲዮ ዝግጅት በትእግስት የማዳምጠው ሴትዮ አሁን ኢቲቪን አላዳምጠውም። ሙሉ ዕድሜ ላይ ትእግስት አጣሁ።  … ስለሆነም ለብዙ ነገር ወያኔ ሠርቷል ለሚባልለት ከአንጀት የማይደርሱ ሸረፍራፋ ነገሮች ሁሉ አዲስ ነኝ … ብዙዎቹን ምስላቸውን ያወቁኩት አሁን ነው። ነባሩ ጠ/ሚኒስቴር ሄሮድስ መለስ ዜናዊ አፈርን ለማጫወት ሲሄዱ ነው …
ለነገሩ የወያኔ ተለጣፊ የአሻንጉሊት ልማቶች መሰረታዊ የወያኔን ሴራ ሊመክት እንደማይችልም ስለምገነዘብ ጊዜዬን ማቀጠል አልሻም። በሚገባ አውቃቸዋለሁና …
ብቻ ሰሞኑን አንድ ዜና ከኢሰአት አደመጥኩ በሚኒስተርነት ማዕረግ የሚመራው „የኢትዮጵያ የዕንባ ጠባቂ ድርጀት“ ወያኔ አቋቁሞ እንደ ነበር። እና ለምስል የተጎለተው ድርጀት ልንደመጥ አልቻልነም ሲል  ሰሞኑን ተደመጠ … ይል ነበር ዜናው …

በእውነት መሳቂያ ነው … አይታፈር! … በእኔ በሥርጉት ሞት እስኪ ዕንባን እሰቡት … ዝም ብላችሁ ጠብታውን … በብዙኃን የወረደውን በአንዲት ቅጽበት የወረደችውን የአንድ  ሰዓቱን … ምን ያህል ጠብታ ሆነ? እሱን በ30 ቀናት አባዙት። እሺ! ከዛ …  በ30 ቀናት አባዛችሁት አይደል?  አሁን ደግሞ ውጤቱን በ365 ቀናት አባዙት። ጎሽ! እግዚአብሄር ይስጣችሁ የ365 ቀናቱን የዕንባ ጠብታ ውጤት አገኛችሁት አይደል። አዎን የ365 የዕንባ ጠብታ በ21 ዓመት አባዙት። አመሰግናችሁ አለሁ። …. ስንት ቸረቸራ … በርሚል ሆነ ….? እእ ወንዝ ነው የሚሆነው …  አዎን!  ከዚህ የዕንባ ወንዝ ላይ ነው  የወያኔ አላጋጭ የዕንባ ጠባቂ ድርጀት ተንሰራፍቶ ተደላድሎ ተመችቶት ድልቶት የኖረው። ታዲያ የማከብራችሁ ይህ ድርጅት የዕንባ ጠባቂ ሊባል ከቶ ይችላልን?
በዕንባ ደም እኮ ነው መህያው በዬወሩ እየተሰጠ ኑሮውን ሲያስፈርሽው የቆዬው – አስማሳዩ ምስል ድርጅት። ቀናት እዬቆጠረ በዕንባ ላይ ተቀምጦ ሲጨፍር ኖረ። በምንም መስፈረት ወያኔ የሚመራውና የፈጠረው የዕንባ ጠባቂ፤ ለብዙኃኑ ዕንባ ዋቢ፤ ጠበቃ ሊሆን ከቶውንም አይችልም። ቢሆን ደስታውን ባልቻልነው ነበር ግን ነገር ግን ስሌቱ አይመጣም። ሆድና ጀርባ ነው። የተገለበጣ የለበጣ ሂሳብ። በኣናቱ የተንጠለጠለ የሽንገላ ቀመር። የተሸበሸበ – ሽምቅቅ።
እኔ እምለው ሰዎችም እብን ናቸው እንጂ በዕንባ ላይ ወንበራቸውን አስቀምጠው ስለ ዕንባ እንጮኻለን ሲሉ ህሊናቸውን ሾለኮት ይሆን? እንጃ ግርንቢጥ ጉድ – ለእኔ።
እንዴት ዓይነት የተሰነጠረ ጨዋታ ነው ወያኔ የሚጫወተው። ይህ ድርጀት እኮ ወያኔ እራሱን የሚያይበት ግፉን የሚለካበትና የሚያቆምበትን ሁኔታ የሚታገል ድርጅት ተደርጎ መፈጠሩ እኮ ለውጪ ኃይሎች ለማላገጫ ነው። … ኢ- ሰባዕዊነት እንደ ሰባዕዊነት ለዛው አፍሪካዊነትም አለበት የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስተር „አፈሩ ይክበዳቸውና“ ሄሮድስ መለስ ዜናዊ ዘመናቸውን ያረዘሙበት ሁለት አፍ ያለው ማጭድ …። የውጪ ኃይሎችን ጆሮ መቀርቀሪያ …. ለህሊናቸው መሸወጃም – ዓይነ ርግብም ….
ዝም ብዬ ሳስበው … ለመሆኑ ድርጀቱስ እስከ ዛሬ ከቶ ዬት ነበረ? ዛሬ ነው ስለ ወያኔ ዕንባ …  መብት ተረገጠ፤ ፍትህ ተጓደለ የሚለው። እነ ሰማዕቱ አሰፋ ማሩ፤ ታዳጊ ነብዩ፤ ወጣት ሽብሬ በጠራራ ፀሐይ፤  ፕ/አስራት ወ/ዬስ በእስራት የዓይን ብርሃናቸው ማጣት ብቻ ሳይሆን እንዲሞቱ የተደረገበት የፍጡራን ጨዋታ፤ አረ ስንቱ? አፈር ሲሆን እራታቸው በሺህ የሚቆጠሩ የነፃነት አርበኞች የቅንጅት መሪዎች፤ ጋዜጠኞች፤ የሰባዕዊ መብት ተካራካሪዎች አዳራቸው የፊጢኝ ታስረው ጨለማ ሲሆን፤
ጋዜጠኛ ሰርካለም ፋሲል ነፍሰጡር እናት ዘጠኝ ወር ሙሉ በኽረ – እርግዝናዋን፤ ያራስ ወጓ፤ የትዳር ክብሯ፤ የማርያም አራስ … ጊዜዋን ሁሉ እስር ቤት ስታሳልፍ። አራስ ልጅ ከእናቱ ተንጥቆ፤ ተመንጭቆ እንዲያድግ ሲፈረድበት፤ የሃልዬ እናት ክብርት ዳኛ ብርቱካን ሜዴቅሳ በተደጋጋሚ እስር ቤት ስተማቅቅ፤  የእኔ ሰው ገብሬ በቤንዚን እራሱን አቃጥሎ ሲገድል፤  ዬአኟክ የጋንቤላ ንፁኃን  ጭፍጨፋ፤ እኛ የማናውቃቸው ስንት ታሪክ የሚያውቁ ዬኦሮሞ ብሄረሰብ አባ ወራዎች፤  በወልቃይትና ጠገዴ ዕድሜ ጠገብ ትውፊትን አዋቂ አዛውንታት የውሃ ሽታ ሆነው ሲቀሩ … ደመ -ከልብ ሲሆኑ፤ …ገዳያቸው ሳይታወቅ ወጣቶች በዬት/ቤቱ ቅጽር ግቢ ተገድለው ሲጣሉ …. እንደ ወጡ ሲቀሩ ….
በሚሊዮን የሚቆጠሩ የነገ ትውልድ ተረካቢዎች የወደቀ ለቅመው ለመብላት እንኳን ሳይችሉ ሲቀሩ። የወደቀ የሚበላው እኮ የሚጥል ሲገኝ ነው። ይህ እንኳን ጠፍቶ ለወደቀ ከቆሻሻ ለቅሞ ለመብላት ተሰልፎው ሲመገቡ ይህ ሁሉ የደም ዕንባ አይደልምን? እንዴት ያለ ቀልድ ነው የሚደመጠው …
ታዳጊ ወጣቶች እንደ አሻው ወያኔ በማር ልጅ በጨረታ እንደ ዕቃ እንደ አወጡ … ወያኔ ሲሸጣቸው ሲለውጣቸው … ሰርተው መኖር ስላልቻሉ በአረብ ሀገር በሺህ የሚቆጠሩ እህቶቻችን በእሳት ሲቀቀሉ፤ በፍል ውሃ ሲንገረገቡ፤ በዬጫካው ሲደፈሩ፤ የአሞራ ሲሳይ ሲሆኑ ይህ ዕንባ አይደለም … ን?
በበዙ ሺህ የሚቆጠሩ ወገኖች ተወልደው ካደጉበት አካባቢ በብሄረሰባቸው ብቻ ተምርጠው ውሃ እንዲባላቸው ሲደረግ። አሁን እንኳን በሃና ማራያም ነዋሪዎች በመዲናችን ህፃናት ሳይቀሩ ለሞት ሲዳረጉ … ኢትዮጵውያን ተገፈትው ለውጭ ዜጎች ቀያቸው ሲቸበቸብ፤ ግፍና በደል ሲደርስባችው ይህ ዕንባ አይደለንም – ን?
ዕንባን ሲጠጣ ሲባላ የኖረው ቢሮው እራሱ የተደረመሰ ነው። የግፍ ዕንብን የረገጣ በብዙኃን ዕንባ ሲሳላቅ የኖረ የግፍ አንባ ነው። እንዲያውም ተጠያቂ ከሚሆኑት ድርጀቶች ይህ ለሰባዕዊ ረገጣ በሽፋንነት ሲያገለግል የቆዬው ድርጅት ነው። ወግ አይቀር  ከፊት ለፊቱ ከቢሮው ደጃፍ እኮ ስሙ ተለጥፎ ይሆናል። አስመሳይ …. የበደል አጋፋሪ፤ … የወያኔ ግፍ – የገደል ማሚቶ።
ወያኔ እንዴት ያለ  ሸፍጠኛ፤ እንዴት ያለ መሰሪ፤ አንዴት ያለ ሌባ ነው  … እግኢዚአብሄር አምላክ  የእጁን ይስጠው። ብን አድርጎ ከሥር መሰረቱ ይሰርዘው …. የጥፋት ጦሮ! አሜን በሉ! ይሁን በሉ። ይደረግልን በሉ።
እግዚአብሄር አምላክ በቃችሁ ይበለን። አሜን!

No comments:

Post a Comment