Translate

Thursday, November 15, 2012

የሁለት ብሄሮችን ግጭት ማስተዳደር አቅቶኛል ያሉ ሰውዬ በየትኛው ቀመር የ80 ብሄሮች ቀንበር ይሸከማሉ ???

ጥቅምት 10 2005 ዓ.ም. ለንባብ የበቃው የሪፖርተር ጋዜጣ ልዩ ዕትም ለአዲሱ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማሪያም ደሳለኝ የኋላ ታሪክ ሰፊ ሽፋን ሰጥቶ ብቅ ማለቱ ይታወሳል፡፡ የዘገባውን ተኣማኒነት ለማጎልበት ጋዜጣው የጠቅላይ ሚኒስትሩን የቀድሞ የሥራ ባልደረቦችንና ወዳጆች አግኝቶ ለማነጋገር ብዙ የደከመ ይመስላል፡፡ 

ዋ ዋ ዋ !!!ሕወሓቶች አርፋቹ ተቀመጡ ዋ!!ዋ!!!ዋ!!!ሆኖም ግን ሪፖርተር ጋዜጣ የአቶ ኃይለማሪያምን ጠንካራ ጎን ለመዳሰስ ባደረገው ጥረት፤የጠቅላይ ሚኒስትሩን የመጠቅለል ብቃትን በጥርጣሬ ዓይን የሚያዩ  ወገኖች በግብዓትነት ሊጠቀሙበት የሚችሉትን መረጃዎችን ሳያቀብል አልቀረም፡፡ 
በእኔ እምነት ዘገባው አንባቢያን ዘንድ ሲደርስ በአዘጋጆቹ ዘንድ ፈጽሞ ያልተጠበቀን ትርጉም (unintended interpretation) የመስጠት አቅም አለው፡፡ ለምሳሌ አንዳንድ ወገኖች የአቶ ኃይለማሪያምን ከደቡብ ብሄር ብሄረሰቦች ክልል ርዕሰ መስተዳደርነት ወደ ቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ቤተመንግስት ለመዛወራቸው በመንስኤነት የሚያስቀምጡት የአመራር ብቃታቸውን ማነስ ነው፡፡ 
ሪፖርተር ጋዜጣም ይህንኑ ግምት የሚያጠናክር መረጃን ነበር ይዞ ብቅ ያለው፡፡ የአቶ ኃይለማሪያም የእምነት ተምሳሌትና አማካሪ (Informal adviser) የነበሩ ቢሾፕ ሕዝቅኤል የሲዳማና የወላይታ ግጭት የአቶ ኃይለማሪያም አመራርን ክፉኛ ተፈታትኖት እንደነበረ በጋዜጣው ላይ በግልጽ ተናግረዋል፡፡ 
ጋዜጣው የቢሾፑን ምላሽ ያስቀመጠው እንደዚህ ነው፦ “አንድ ጊዜ በዚህ በሐዋሳ ጉዳይ አሁን አስቸጋሪውን ጉዳይ ለመወጣት እየሞከርኩ ነው ያለሁትና ጸልዩልኝ ብሎኝ ነበር፤የሚሉት ቢሾፑ አቶ
ኃይለማሪያም እንዴት ከክልል ወደ ፌደራል መንግስት በአቶ መለስ ዜናዊ ጥሪ መሠረት እንደሄዱ ያብራራሉ…..” በዚህ ጉዳይ ላይ በጣም ተቸግሮ ነበር፡፡ 
እናም ይህ የወላይታና ሲዳማ ጉዳይ እንዳስቸገረው ለመለስ ነግሬዋለሁ አለኝ፡፡ መለስስ ምን አለህ ብዬ ጠየቁት፡፡ አንተ እዚያው  እኖራለሁ ብለህ ካላሰብክ በል ሁሉንም ነገር አስረክብና ዛሬ ና ብሎኛል ሲለኝ በእሱ ልብ ውስጥ ገብተሃል ማለት ነው፤ ስለዚህ ብትሄድ ይሻላል አልኩት በማለት ያስታውሳሉ፡፡” እንግዲህ ከቢሾፕ ህዝቅኤል ማብራሪያ የምንረዳው አቶ ኃይለማሪያም በሲዳማና በወላይታ መካከል ለነበረው ችግር መፍትሄ መስጠት እንዳቃታቸው ነው፡፡
 ከዚህም የምናስተውለው አቶ ኃይለማሪያም ግጭቶችን የመስተዳደርና የመፍታት ብቃትን (conflict management and resolution) እንዳልተካኑ ነው፡፡ አሁን ደግሞ አቶ ኃይለማሪያም ከ80 በላይ ብሄር ብሄረሰቦች ያሉባትን ሀገር ለመምራት ቃለ-መሐላ ፈጽመዋል፡፡ ይሁንና የሁለት ብሄሮችን ግጭት ማስተዳደር አቅቶኛል ያሉ ሰውዬ በየትኛው ቀመር የ80 ብሄሮች ቀንበር ይሸከማሉ ብለን እንመን? መጽሐፉም የሚለው “በጥቂቱ የታመነ በብዙው ይሾማል” ነው፡፡

የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር መለስም ቢሆኑ እያፈሩ የነበሩት መሪዎችን ሳይሆን ተከታዮችን እንደነበረ ሪፖርተር ጋዜጣ ቁልጭ አድርጎ አሳይቷል፡፡ በእኔ እምነት የሲዳማና የወላይታ ግጭት የአቶ ኃይለማሪያምን አስተዳደራዊ ብቃት ለመገምገም ምቹ ሁኔታ ነበር፡፡ ለምሳሌ አንድ ሰው ስለ ዋና ጥበብ ብዙ መጽሐፍት አገላብጦ ብዙ ሊፈላሰፍ ይችላል፤ሆኖም ግን ዋናን ለመልመድ የግድ ውኃው ውስጥ ደፍሮ መግባት ግድ ይለዋል፡፡ 
በእኔ እምነት አቶ ኃይለማሪያም ስለ “ዋናው” ንድፈ ሐሳብ ብዙ መጽሐፍት ካገላበጡ በኋላ ውኃ ውስጥ ገብተው ለመዋኘት ሙከራ ሳያደርጉ አልቀሩም፤ በዚህም ሂደት ውስጥ በውኃው  ላይ መንሳፈፍ ሲያቅታቸው ስልካቸውን አንስተው አቶ መለስ እና ቢሾፕ ሕዝቅኤል (life savers) ጋ ደውለው የድረሱልኝ ጥሪ አሰሙ፤ አቶ መለስም ለአቶ ኃይለማሪያም ተግባራዊ የዋና ጥበብ ምን እንደሆነ እዚያው ከመዋኛው ገንዳ ውስጥ እያሉ እንደማስተማር ፈጥነው እንዲወጡ አዘዙአቸው፡፡
በእኔ እምነት እንደዚህ ዓይነት ርህራሄ (sympathy) የሚቸረው ለተከታይ እንጂ ነገ ለመሪነት ለሚታጭ ሰው አይደለም፡፡ ዕጩ መሪ እውነተኛው ማዕበል ውስጥ ገብቶ መፈተሽና መታየት ይኖርበታልና፡፡ ቢሾፕ ሕዝቅኤል የአቶ ኃይለማሪያምን የ”አመራር ዋና” ተግባርን አቋርጦ ወደ ፌዴራል መንግስት መዛወርን በቀጥታ ያቆራኙት መለስ ልብ ውስጥ ከመግባት ጋር ነው፡፡
 ስለዚህም ከክልል አመራርነት በፌዴራል ደረጃ ለበለጠ ኃላፊነት ለመታጨት “ዋናውን” ስኬታማ በሆነ መልኩ ማጠናቀቅ አይጠበቅም ማለት ነው፡፡ ቤተመንግስት ለመግባት ቅድመ ሁኔታው ሰውዬው ልብ ውስጥ መግባት ነው፡፡ “…በእሱ ልብ ውስጥ ገብተሃል ማለት ነው፤ ስለዚህ ብትሄድ ይሻላል አልኩት…”፦ ቢሾፕ ሕዝቅኤል፡፡ በእርግጥ የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር ልብ ውስጥ ለመግባት ሌላ እኛ የማናውቀው መስፈርት ይኖር ይሆናል፡፡ ያም ሆነ ይህ የኢህአዴግ የደህንነት ሰዎች ማንም ሰው የአሁኑን ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ኃይለማሪያምን አውቀዋለሁ በሚል ሰበብ አላስፈላጊና አዋኪ መግለጫ እንዳይሰጥ ብዙ መስራት እንዳለባቸው ይሰማኛል፡፡ 
አንዱ የቀድሞ የአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ ሹፌራቸው ሪፖርተር ጋዜጣ ላይ ዛሬም ጠቅላይ ሚኒስትሩን እንደ ጥንቱ በቀጣይነት “ጋሼ ኃይሌ” እያለ ለመጥራት ያሳያው ቁርጠኝነት የሚደነቅ ቢሆንም የፕሮቶኮሉ ጉዳይ ሊዘነጋ ዘንድ አይገባም፡፡ ሪፖርተር ጋዜጣ ግን ለአቶ ኃይለማሪያም መሾም ከቢሾፕ ሕዝቅኤል በተለየ መልኩ የአካዳሚክ ልዕቀታቸውን (academic excellence) እንደ አንድ ወሳኝ ቅድመ ሁኔታ ለማስቀመጥ አንድ ሐሙስ የቀረው ይመስላል፡፡ 
በእርግጥ ብዙዎች የአቶ ኃይለማሪያም የአመራር ክህሎት በርዕስነት በሚነሳበት ወቅት ፈጥነው በኩራት የሚያብራሩት ጠቅላይ ሚኒስትሩ በአረካ አከባቢ የማትሪክ ውጤት 3.80 በማግኘት ለማለፍ የመጀመሪያው ሰው እንደ ነበሩ ፤ከዚያም በአዲስ አባባ ዩኒቨርሲቲ የሲቪል ምህንድስና ትምህርትን በከፍተኛ ማዕረግ እንዳጠናቀቁ፤ ቀጥሎም ፊንላንድ ሀገር ሄደው የሳኒቴሽን ምህንድስናን የወርቅ ተሸላሚ በመሆን እንዳጠናቀቁ… ወዘተ ነው፡፡ 
በተለይ በአረካ አከባቢ “የመጀመሪያውና ታሪካዊው ከፍተኛ ውጤት (3.80) “ በተበሰረ ጊዜ የተንጸባረቀው ፌሽታና ጭፈራ በጋዜጣው ላይ የተተረከው በቅርቡ ከ31 ዓመታት በኋላ የኢትዮጵያ ብሄራዊ የእግር ኳስ ቡድን ባገኘው ድል ድባብ ውስጥ ሆኖ ይመስላል “…ኃይሌ 3.80 ነጥብ አመጣ ሲባል ጓዳኞቹና የአረካ ልጆች በመኪና አጅበውትና የመኪናው ጣራው ላይ አቁመውት ከሶዶ ሲመጡ እኛና የከተማው ህዝብ አስፋልት ላይ ወጥተን እየጨፈርን ነበር የተቀበልነው..በዚች ዕለት የኃይሌ ስም እንደ ደማቅ ኮከብ ፈክቶ ታየ…..ወዘተ፡፡” 
አቶ ኃይሌ ግን አሁንም ለወላይታና  ምናልባትም ለደቡብ “የመጀመሪያው” የሚያሰኛቸው አጋጣሚ ተፈጥሮ እንደ ያኔው ደማቅ ኮከብ ፈክተው ታይተዋል፡፡ የአመራር ሳይንስ ጠበብት ግን እንደ እኛ
የአካዳሚክ ልዕቀትን ለመሪነት እንደ ዋና መመዘኛ አድርገው አያስቀምጡም፡፡ አመራር ሥነ-ጥበብ ነው የሚል አቋም የሚያራምዱ ደራሲና የአመራር ሳይንስ ሊቅ ማክስ  ድ.ፕሪ “Leadership is an art” በተሰኘው መጽሐፋቸው ይህንኑ በተመለከተ እንደዚህ በማለት አስቀምጠዋል…”leadership is an art to be learned over time, not simply by reading books….The measure of leadership is not the quality of head, but the tone of the body” ደራሲው በአጭሩ ማስገንዘብ የፈለጉት የአመራር ክህሎት ገመድ የተገመደው ከአንድ የሙያ ዘርፍ ሳይሆን ከልዩ ልዩ ተዛማጅ የዕውቀትና የጥበብ መረቦች (networks of relationships) እንደሆነ ነው፡፡

ከላይ ከገለጽኩት ባሻገር የጥቅምቱ 10 ሪፖርተር ጋዜጣ የአቶ ኃይለማሪያምን የአመራር ውሳኔን አሰጣጥ የሚያስገመግም ሌላ ተጨማሪ እውነትንም ይፋ አድርጎልናል፡፡ ይህኛው ከአርባ ምንጭ ዩንቨርሲቲ ቆይታቸው ጋር የተገናኘ ነው፡፡ አቶ ኃይለማሪያም በዩንቨርሲቲው እያሉ ብዙ የግንባታ ሥራዎችን እንዲከናወን መንገድ ከፍተዋል፡፡ 
በዚሁ የግንባታ ሂደት ወቅት አንድ ኮንትራክተር ሥራውን አጠናቅቆ ካስረከበ በኋላ ለአቶ ኃይለማሪያም እጅ መንሻ ለመስጠት የሞከረበትን ሁኔታ ሪፖርተር ጋዜጣ እንደዚህ በማለት ያስረዳናል፦ ይህን አካሄድ የሥነ ምግባርና ፀረ-ሙስና ባለሙያዎች እንዴት እንደሚመለከቱት ባላውቅም በእኔ ዕይታ ግን ኮንትራክተሩም ሆነ አቶ ኃይለማሪያም በህግ ፊት ሊያስጠይቅ የሚያስችል ስህተት ሰርተዋል ባይ ነኝ፡፡ 
በመጀመሪያ ደረጃ ኮንትራክተሩ እጅ መንሻውን ስኬታማ በሆነ መልክ ሰጥተዋል፡፡ የአቶ  ኃይለማሪያም “እምቢ ለግሌ” ውሳኔ ያስቀያረው የእጅ መንሻውን ተቀባይ ብቻ ነው…..ከግለሰብ ወደ ዩኒቨርሲቲ ማህበረሰብ! በሙስና ሳይንስ ዘርፍ ላይ ጥናት የሚያደርጉ ባለሙያዎች እንደዚህ ዓይነቱን ሁኔታ “massive bribery” በማለት ይጠሩታል፡፡ በእኔ ግምት ኮንትራክተሩም ወደ ፊት የበለጠ ተጠቃሚ የሚሆነው እጅ መንሻውን ለአንድ ግለሰብ ከሚሰጥ ይልቅ ለማህበረሱ ቢሰጥ ነው፡፡
ሰፋፊ የመንግስት የኮንስትራሽን ሥራዎች በሚከወኑበት ወቅት ሙሰኛ ኮንትራክሮች ለባለሥልጣናት የእጅ መንሻ የሚሰጡበት ጊዜ በዋናነት በሁለት ምድብ የተከፈለ ነው፡፡ አንዳንዱ ገና ስራው ሳይጀመር የሥራውን ቅበላ ለማመቻቸት አስቀድሞ እጅ መንሻ ይሰጣል (pre- project implementation bribery):: ሁለተኛው ዓይነት ፕሮጄክቱ ከተጠናቀቀ በኋላ (post project implementation bribery) የሚሰጥ ነው (የአቶ ኃይለማሪያም ዓይነት)፡፡ የሁለተኛው ዓይነት የእጅ መንሻ ዓላማ ስውር ነው፤ ምንም እንኳን የእጅ መንሻው “ለቀናነታቸው፤ ለሥራ አክባሪነታቸውና ለአስተዳደራዊ ተግባራቸው” በሚሉ አዘናጊ ቃላት ተከሽኖ ቢቀርብም ተልዕኮውና ትርጉሙ ሌላ ነው፡፡ 
ብዙውን ጊዜ እንደዚህ ዓይነቱ እጅ መንሻ የሚሰጠው ውለታውን ተገን በማድረግ የአንድን ተቋም ደንበኝነት ዝንተ ዓለም ይዞ ለመቆየት ነው፡፡ ለምሳሌ በወቅቱ የአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ በሚኖሩት ቀጣይ ፕሮጀክቶች የሥራ ሂደት ውስጥ በማህበረሰቡ ዘንድ ቅድሚያ የሚሰጠው ለዩኒቨርሲተው ማህበረሰብ መዋለ ህጻናት ህንጻን በእጅ መንሻነት የሰጠው የቀድሞ ደንበኛ ነው፡፡ ከዚህም የተነሳ ሌሎች ኮንትራክተሮች ለማህበረሰቡ ባይተዋር የመሆን ዕድል ሊያጋጥማቸው ይችላል፡፡ ይህ ደግሞ ከሙስና ዓይነቶች አንዱ ለሆነው ለአድሎአዊነት (favoritism) የዩኒቨርሲተውን ህብረተሰብ አሳልፎ ይሰጣል፡፡ 
ስለዚህም አቶ ኃይለማሪያም የወሰኑት ውሳኔ ላይ ላዩን ሲታይ መልካም ቢመስልም ከህግና ከሞራል አንጻር ሲገመገም ተቀባይነቱ አጠያያቂ ነው፡፡ ደግሞም ሪፖርተር ጋዜጣ ከመዋለ ህጻናት ተቋሙ የመጀመሪያዎቹ ተመራቂዎች እነማን እንደነበሩ ያስቀመጠው በዚህ መልክ ነው፦ “….በዚህ አነስተኛ መዋለ ሕጻናት ውስጥ ከመጀመሪያዎቹ ተማሪዎች ውስጥ የራሳቸው የኃይለማሪያም ልጆችም የመጀመሪያዎቹ ተመራቂ ህጻናት ናቸው፡፡” ሰውዬው እጅ መንሻውን በቀጥታ ባይቀበሉም በልጆቻቻው አማካይነት በእጅ አዙር ተቀብለዋል ማለት ይቻል ይሆንs ሪፖርተር ጋዜጣ አቶ ኃይለማሪያም “ዛሬ በዚህ የማህበረሰብ ትምህርት ቤት የሚማሩ ተማሪዎች ዩኒፎርም ለብሰው፤ በከተማው ሲንቀሳቀሱ ሳይ ዕንባዬ ይመጣል” ብለው እንደ ተናገሩ ጠቅሶአል፡፡
 የዕንባ ኬሚካላዊ ውቅሩ አንድ ዓይነት ቢሆንም የሚፈስበት ምክንያት ግን ይለያያል፡፡ ዛሬ አቶ ኃይለማሪያም ለ”mass bribery” በወቅቱ በር መክፈታቸውን ሲያስተውሉ ዕንባ ይመጣ ይሆን? ሐሳቤን ከመቋጨቴ በፊት ቀጣይዋን ማንፀሪያ ላሣይና ልሠናበት፦ አንድ ባለጠጋ ሰው ወደ ውጪ ሀገር ለመሄድ የአይሮፕላን ቲኬት ቆርጦ የበረራው ቀን እንደደረሰ ማለዳ ተነስቶ ወደ አይሮፕላን ማረፊያ ለመሄድ ጎዙን አሰናዳ፡፡ የባለጠጋው የሌሊት ዘበኛ ግን ጉዞው ይሰረዝ ዘንድ ተማፀነ፡፡ 
የተማፅኖው ምክንያት ደግሞ ሌሊት ተኝቶ ያየው ህልም ነበር፤ ዘበኛው በህልሙ ያየው አለቃው ቲኬት የቆረጡበት አይሮፕላን በእሳት ሲጋይ ነበር፡፡ ባለጠጋው ሰውዬም ምክሩን በመስማት ጉዞውን ሰረዘ፤ ትንሽ ቆይቶም ልክ በዘበኛው እንደተነገረው ቲኬት የቆረጠበት አይሮፕላን በእሳት ሲጋይ በቴሌቪዥን ተመለከተ፡፡ ታሪኩን የሰማ ሁሉ በዘበኛው ህልም ዕውን መሆን ተገርሞ ከባለጠጋው ዘንድ የሚሸለመውን ሽልማት በጉጉት በሚጠባበቅበት ወቅት ባለጠጋው አንድ ፖስታ ይዞ ከተፍ አለ፡፡ 
ሁሉም የገመተው በፖስታ ውስጥ የብዙ መቶ ሺዎች ሽልማት የያዘ ቼክ እንዳለ ነበር፡፡ ዘበኛው  ፖስታውን ሲከፍተው ፈጽሞ ባልጠበቀው ሁኔታ ከሥራው እንደተባረረ የሚገልጥ የሥራ ስንብት ደብዳቤ ሆኖ ተገኘ! ለምን ቢባል ይህ የሌሊት ዘበኛ ህልሙን ያያው ማታ ተኝቶ ነው፤ በአለቃውና በዘበኛው መካካል የነበረው የሥራ ውል ስምምነት ደግሞ ይህን በፍጹም የማይፈቅድና ምናልባትም
ዘበኛው ተኝቶ ከተገኘ ያለአንዳች ማስጠንቀቂያ ከሥራ የሚያስባርር ነበር፡፡ አበቃሁ!!
የ”ጉዞ ኃይለማሪያም” አንድምታ “ቤተመንግስት ለመግባት፤መለስ ልብ መግባት” “የአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ ግንባታ ሲጠናቀቅ በወቅቱ የነበሩ ኮንትራክተር ለአቶ ኃይለማሪያም ምን  እናድርግልዎት? በማለት ለቀናነታቸው፤ ለሥራ አክባሪነታቸውና ለአስተዳደራዊ ተግባራቸው እንደ
ውለታ ተቆጥሮ እጅ መንሻ ይቀርብላቸዋል፤ አቶ ኃይለማሪያም ግን በግላቸው ለዋሉት ውለታ ምንም ነገር ተቀብለው ኪሳቸው ማስገባትን አልፈለጉም፡፡ ይልቁንም ለተቋሙ መምህራንና ለተራ ሠራተኞች ሳይቀር ለልጆቻቸው መማሪያ የሚሆን ግቢው ውስጥ መዋዕለ ሕፃናት እንዲገነቡላቸው ይጠይቃሉ፡፡ ኮንትራክተሩም ይህን ለማድረግ ወደ ኋላ አላሉም…”

No comments:

Post a Comment