Translate

Saturday, August 11, 2012

ፍትህ ጋዜጣ እንዳትታተም ተከልክላለች::


ከተመስገን ደሳለኝ
ፍትህ ጋዜጣ እንዳትታተም ተከልክላለች፡፡ ግራ የገባኝ ግን ጋዜጣዋ የታገደችው በዝግ ችሎት መሆኑ ነው፡፡ እንድትወረስ የተወሰነውም በዝግ ችሎት ነው፡፡ ዛሬ ደግሞ በከፍተኛው ፍርድ ቤት ሶስተኛ ወንጀል ችሎት (በዝግ ችሎት) ሶስት ክስ እንደተመሰረተብኝ በሬዲዮ ሰማሁ፡፡ፍትህ ጋዜጣ እንዳትታተም ተከልክላለች፡፡
ነገሩ እንዲህ ነው፡- ዛሬ ከሶስት ጓደኞቼ ጋር ምስ እየበላሁ ሳለ በምግብ ቤቱ የሬዲዮ ፋና ዜና እየተላለፈ ነው፡፡ ዜናው ቀጥሏል፡፡
“የፍትህ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ ተመስገን ደሳለኝ ሶስት ክሶች ተመሰረቱበት፡፡

ማስተዋል የህትመትና ማስታወቂያ ስራ ድርጅትም በተመስገን ላይ በቀረቡ ክሶች በዋና ወንጀል አድራጊነት ተካፋይ በመሆን ሁለተኛ ተከሳሽ ሆነዉ ጉዳያቸዉ
በፌዴራሉ ከፍተኛ ፍረድ ቤት 16ተኛ ወንጀል ችሎት ታይቷል፡፡
የፌዴራሉ አቃቢ ህግ በፌዴራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት 16ኛ የወንጀል ችሎት ክስ የመሰረተባቸው በፍትህ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ ተመስገን ደሳለኝ እና በማስተዋል የህትመት እና ማስታወቂያ ስራ ድርጅት ላይ ነው።
አቃቢ ህግ በተመስገን ደሳለኝ ላይ ሶስት ክሶችን የመሰረተ ሲሆን ፥ ክሶቹም 1ኛ ወጣቶች በአገሪቱ መንግስትና ህገ መንግስታዊ ስርአቱ ላይ እንዲያምጹ የመገፋፋትና ግዙፍ ያልሆነ የማሰናዳት ተግባር፣ 2ኛ የሀገሪቱን መንግስት ስም ማጥፋት እና የሀሰት ውንጀላ እንደሁም 3ኛ የሀሰት ወሬዎችን በማውራት ህዝብን በማነሳሳት ወይም አስተሳሰባቸውን ማናወጥ የሚሉ ናቸው።
የቀረበበት የክስ መዝገብ እንደሚያስረዳው በጋዜጣው የነሃሴ 23 ቀን ቅጽ 04 ቁጥር 149 እትም ላይ ሞት የማይፈሩ ወጣቶች በሚል ርዕስ የአጼ ሃይለስላሴን ስርአት ወጣቶች እንዴት እንዳፈረሱት እና አሁን ያለው ስርአትም አፋኝ እና ጨቋኝ መሆኑን በመግለጽና አሁንም ሞት የማይፈሩ ወጣቶች መኖራቸውን ጠቅሶ በአረቡ አለም የተከሰቱ የህዝብ አመጾችን በሀገራችን እንዲተገበር በማሰብ ወጣቶች አደባባይ ለአመጽ እንዲወጡ በጽሁፍ ቀስቅሷል።
በሌላ በኩል የካቲት 23 2004 ዓ.ም በተሰራጨው የፍትህ ጋዜጣ ቅጽ 05 ቁጥር 177 እትም የፈራ ይመለስ በሚል ርዕስ ኢትዮጵያውያን በአድዋ ጦርነት ላይ ያሳዩትን ጀግንነት ካተተ በኋላ ሞት የማይፈሩ ወጣቶች ሆ ካሉ ማንንምና ምንም እንደማይፈሩ አስታውሶ በአሁኑ ወቅት ያለውን የኢትዮጵያ ሁኔታ ከመፍራት ይልቅ እንድትቆጣ የሚገፋፉ ነው በማለት በጋዜጣ ህዝቡ በሀገሪቱ መንግስትና በህገ መንግስታዊ ስርአቱ ላይ እንዲያምጽ እንዲሁም ስርአቱ እንዲፈርስ በጋዜጣው አማካኝነት በመቀስቀስ የመገፋፋትና ግዙፍ ያልሆነ የማሰናዳት ተግባር ፈጽሟል የሚል ነው።
በጋዜጣው ሌላ ዕትም ላይ ደግሞ የሁለተኛ ዜግነት ህይወት በኢትዮጵያ እስከመቼ? በሚል ርዕስ የሀገሪቱን መንግስት ስም ያጠፋ፣ የሀሰት ውንጀላ ጽሁፍ ጽፏል የሚል ይገኝበታል።
በቅጽ 5 ቁጥር 179 መጋቢት 7 2004 ዓ.ም ዕትም መጅሊሱና ሲኖዶሱ የአብዮታዊ ዲሞክራሲ ማጥመቂያ በማለት የክርስትናና የእስልምና መሪዎችን የኢህአዴግ ካድሬዎች በማለት ህዝብን በማነሳሳት ወይም አስተሳሰቡን በማናወጥ የሚሉ ክሶች በተመስገን ደሳለኝ ላይ ቀርበዋል።
በተጨማሪም በማስተዋል ህትመትና ማስታወቂያ ስራ ድርጅት የፍትህ ጋዜጣ እትሞችን በማሳተምና በማከፋፈል የወንጀል ድርጊቱን የቀሰቀሰ በመሆኑ በዋና ወንጀል አድራጊነት ተካፋይ በመሆን በፈጸመው የመገፋፋትና ግዙፍ ያልሆነ የማሰናዳት ተግባር ወንጀል መከሰሱን ለፍርድ ቤቱ የቀረበው የክስ መዝገብ ያስረዳል።
ችሎቱ ተከሳሹ ተመስገን ደሳለኝ በግንባር ስላልቀረበ ነሃሴ 9 ቀን 2004 ዓ.ም ቀርቦ ምላሽ እንዲሰጥ ትዕዛዝ አስተላልፏል።”
የክስ ቻርጅም ሆነ መጥሪያ ሳይደርሰኝ ባሌለሁበት ነው ችሎቶ የታየው፡፡ መቼም ይህ በአለማችን የመጀመሪያው ሳይሆን አይቀርም፡፡ ፋናም ፍርድ ቤቱ ‹‹ለተከሳሹ መጥሪያ ደርሶታል ወይስ አልደረሰውም?›› የሚል ጥያቄ ዓቃቢ ህግን መጠየቅ አለመጠየቁን አልዘገበም፡፡ ወይም ሆን ብሎ ዘሎታል፡፡
የሆነ ሆኖ እነእስክንድር ነጋ ከታሰሩ አመት ሊሞላቸው በቀናት የሚቆጠር ዕድሜ ብቻ ቀርቷቸዋል፡፡ ብሶት የወለደው ኢህአዴግም ዓመቱን ጠብቆ ምሱን አየፈለገ ይመስለኛል፡፡

No comments:

Post a Comment