Translate

Wednesday, July 25, 2012

ቅምሻ ጨዋታ “ሞተዋል እንዳልል ቀብርዎን አላየሁ፤ አሉም እንዳልልዎ ድምፅዎን አልሰማሁ…”

ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ምን ውስጥ እንደገቡ እስከ አሁንም የጠራ ወሬ አልሰማንም። በምትኩ የተምታታ ዜና እያዳመጥን ነው። ቅዳሜ እለት ለህትመት የበቃው እንግሊዘኛው “ፎርቹን” ጋዜጣ መለስ ወደ አዲስ አበባ መመለሳቸውን አስመልክቶ ፊት ለፊት ገፁ ላይ አስነብበቦን ነበር። ዛሬ ደግሞ ሪፖርተር ጠቅላይ ሚኒስትሩ ውጪ ሃገር በእረፍት ላይ ናቸው ብሎ ዘግቦልናል። ነገሩን ልብ ብለን ስናየው ዘጋቢዎቻችንም እየዘገቡልን ሳይሆን እያወዛገቡን ነው የሚመስለው።


የመንግስት ሰዎችም ሀቁ ይሄ ነው ብለው ሊነግሩን አልተቻላቸውም። እዝች ጋ ይሔኔ እርሳቸው ቢሆኑ ኖሮ… ብለን አጥብቀን እንቆጫለን! “አጎደሉን እኮ አጎደሉን እኮ…” ብለንም በሀዘን ዜማ እናንጎራጉርላቸዋለን።

ትላንት በዲሞክራትነታቸው የሚታወቁት የጋናው ፕሬዘዳንት “ሚልስ” በድንገተኛ ህመመም መሞታቸው ሲሰማ አንዳንዶች ኧረ ይሄ ነገር የታይፕ ግድፈት ነው የሚሆነው ብለው ተከራክረው ነበር። የምርም ግን እንደሚወራው ጠቅላይ ሚኒስትራችን እስከ አሁን ድረስ በህይወት ካሉ “እግረ ቀጭን እያለ እግረ ደንዳና ይሞታል” የሚለው የሀገራችን አባባል ሰራ ማለት ነው።

እውነት ግን ጠቅላይ ሚኒስትራችን የሆነ ነገር ውስጥ ተደብቀው እየሰሙን ይሆን!? ወይስ በሰማይ ከአባታቸው ዘንድ ቁጭ ብለው እየፀለዩልን ይሆን!
ሞተዋል እንዳልል ቀብርዎን አላየው፤
አሉም እንዳልልዎ ድምፅዎን አልሰማው
ምን ብዬ ልናገር ለጠየቀኝ ሰው…?
ለማንኛውም ዛሬም በጠቅላይ ሚኒስትሬ ጉዳይ እየተጨነቅሁ መሆኑን የእርሳቸውን ነገር ለአፍታም እንኳ ቸል የማልለው ጉዳይ መሆኑን ለማሳየት ያኸል ነው እንጂ ይሔ ጨዋታ አልተጠናቀቀም! “ቅምሻ” በሉት ሲጠናቀቅ ድጋሚ እንገናኛለን…!
Abe tokchaw

No comments:

Post a Comment