Translate

Friday, July 27, 2012

በአንዋር መስኪድ ከግማሽ ሚሊዮን በላይ የሚሆን ህዝብ ትግላችን አይቀዘቅም አለ::

ሐምሌ ፳ (ሀያ) ቀን ፳፻፬ ዓ/ም
ኢሳት ዜና:- የአዲስ አበባው ዘጋቢያችን በስፍራው ተገኝቶ እንደተመለከተው ዛሬ ለተቃውሞ የወጣው ሙስሊም ኢትዮጵያዊ እስከዛሬ ከተሳተፈው ሁሉ በቁጥር በእጅጉ የሚልቅ ነው።
ዋና ዋና መሪዎቹ በማእከላዊ እስር ቤት በአሰቃቂ ድብደባ ምርመራ እየተካሄደባቸው መሆኑን የኢሳት እንዲሁም የአምነስቲ ኢንተርናሽናል መረጃዎች ይፋ ባደረጉ ማግስት፣ አንዳንዶች አንድ ሚሊዮን ሌሎች ከ700 ሺ እስከ 800 ሺ የሚገምቱት ህዝብ ተቃውሞውን በዝምታ፣ በጭብጨባና እጆቹን ወደ ላይ በማንሳት አሰምቷል።

አልሞተኳሽ ወታደሮች በየህንጻው ስር ሆነው ማንኛውንም ነገር ለመቆጣጠር በተጠንቀቅ ሲጠባበቁ ቢቆዩም፣ ሙስሊሙ ኢትዮጵያዊ ምንም አይነት ለግጭት መንስኤ የሚሆን ነገር ባለማሳየቱ ተቃውሞው በሰላም ተጠናቋል።
አንድ ወጣት ሙስሊም ለኢሳት እንደተናገረው ” ዛሬ ሙስሊሙ እስልምና የሰላም ሀይማኖት መሆኑን አሳይቷል። መሪዎቹ እንዲፈቱለት እጅግ ሰለማዊ በሆነ መንገድ፣ ምንም ኮሽታ ሳያሰማ በሚያስደነግጥ ዝምታ ተቃውሞውን ገልጧል። መሪዎቹ ሰላማዊ መሆናቸውን እጁን በማውጣት አሳይቷል።” ብሎአል።
ወጣቱ አያይዞም ” ሙስሊሙ መንግስትን እያስተማረው ነው። ከመንግስት ቀድሞ ሄዷል። መንግስት የራሱን ደህንነቶች አስርጎ በማስገባት ፣ የመንግስት ደጋፊ የሆኑትን አሰጋጅ ለማስመታትና የተወሰኑ ሰዎችን ለማሳሰር አልሞ የነበረ ቢሆንም፣ ሙስሊሙ ራሱ በራሱ በወሰደው ጥንቃቄ አንድም ግጭት እንዳይፈጠር አድርጓል ሲል አክሏል።”
የዛሬው የሙስሊሞች ተቃውሞ የፌደራል ፖሊስ ኮሚሽን ኮሚሽነር የሆኑት ወርቅነህ ገበየሁ የሙስሊሙን ተቃውሞ በአስተማማኝ ሁኔታ ተቆጣጥረነዋል በማለት መግለጫ በሰጡ በማግስቱ የተከናወነ ነው።
ኮሚሽነሩ የሙስሊሙን አመራሮች ወደ እስር ቤት ከወረወሩ በሁዋላ ፣ ፖሊስ ተቃውሞውን በአስተማማኝ ሁኔታ ተቆጣጠሮታል በማለት የሰጡት መግለጫ ሙስሊሙ በዛሬ ተቃውሞ በብዛት እንዲወጣና ተቃውሞን እንዲያሰማ እንዳደረገው ነው ዘጋቢያችን ተሳታፊዎችን አነጋግሮ የዘገበው።
የኢህአዴግ መንግስት ሙስሊሙ ያቀረበውን ጥያቄ ለመፍታት ወኔው እየከዳው እንደመጣ ነው አስተያየት ሰጪዎች የሚናገሩት። ከሙስሊሞች ጥያቄ ጋር በተያያዘ በድርጅቱ ውስጥ መከፋፈል መፈጠሩንም መንጮች ጠቁመዋል።
የሲቪል ሰርቪስ ሚኒስትር የሆኑት አቶ ጁነዲን ሳዶ ዛሬ በቁጥጥር ስር መዋላቸውን በአዲስ አበባ ውስጥ በስፋት እየተነገረ ነው፡፡ ሰሞኑን ሚሚ ስብሀቱ በራዲዮ ጣቢያዋ አቶ ጁነዲን መታሰር አለባቸው በማለት ቅስቀሳ ስታደርግ ነበር። አቶ ጁነዲን ባለቤት በቅርቡ በቁጥጥር ስር መዋላቸው ይታወሳል። ኢሳት የአቶ ጁነዲንን የእስር ዜና ትክክለኛነት ለማጣራት ሙከራ በማድረግ ላይ ነው። ተጨማሪ መረጃ እንደደረሰን እናቀርባለን።

No comments:

Post a Comment