Translate

Sunday, July 29, 2012

ህገ መንግስቱ ጠቅላይ ሚኒስትሩ እንዲሞቱ አይፈቀድላቸውም!?

ትላንት ፕሮፌሰር አለማየሁ ገብረማሪያም ከአሜሪካ ድምፅ ራዲዮ ጋር የጠቅላይ ሚኒስተሩን መያዝ እና ምትካቸውን አስመልክቶ ቃለ ምልልስ አድርገው ነበር። ዛሬ ደግሞ ተወዳጇ ዞን 9 ብሎግ “ባልቻን ፍለጋ” በሚል አንድ ወግ አስነብባናለች።
ሁለቱም እንደጠቆሙት በህገ መንግስቱ ላይ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ቢሞቱ ወይም ደግሞ በሆነ ምክንያት “ከጥቅም ውጪ” ቢሆኑ ማን ይተካቸዋል? እንዴት ይተካሉ? ለሚለው ጥያቄ ህገ መንግስቱ መልስ የለውም።
ህገ መንግስታችን አንቀፅ 74 ስለ ጠቅላይ ሚኒስትሩ የስራ ድርሻ በአንድ ገፅ ተኩል ያህል ይዘረዝራል። (በቅንፍ እናደንቃለን፤ ጠቅላያችን ይሄንን ሁሉ ኖሯል ሃያ አንድ አመት ሙሉ ሲሰሩ የኖሩት…? መድከም ይነሳቸው እንዴ…!? አንዱ ስብሰባ ላይ ክልትው ብለው አለመቀረታቸውም በእውነቱ ብርታታቸውን ያመለክታል!)

በአንቀፅ 75 ላይ ደግሞ የምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩን የስራ ድርሻ ይናገራል። ቆይ እዝች ጋ ፍሬን ያዝ እናድርግ እና ህገ መንግስቱን እናንብብ፤
ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤
1 በጠቅላይ ሚኒስትሩ ተለይተው የሚሰጡትን ተግባሮች ያከናውናል።
2 ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማይኖሩ ጊዜ ተክቶ ይሰራል።
ከዛም በነጥብ ሁለት ላይ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ ተጠሪነቱ ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ይሆናል። ብሎ ያበቃል። እንግዲህ በተራ ቁጥር 2 ላይ ባለው መሰረት “ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማይኖሩ ጊዜ ምክትሉ ተክቶ ይሰራል።” የሚል ከመገለፁ ውጪ ጠቅላይ ሚኒስትሩ አይበልባቸውና አንድ ነገር ቢሆኑ የሚተካቸው ሰው ማንነት አልተገለፀም።
አሁን በቅርቡ ግንባር መሆኑን ያሳወቀው መድረክ ቀጣዩ ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ኃይለማሪያም ደሳለኝ መሆን አለባቸው ስልጣኑን ሊረከቡ ይገባል ብሎ መጠየቁ ሲሰማ የኢህአዴግ ቀሪ ባለስልጣናት ህገመንግስቱን ጠቅሰው ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ የሚተኩት ለአጭር ጊዜ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማይኖሩ ወቅት እንጂ ከናካቴው ሳይኖሩ ሲቀር አይደለም። ብለው መከራከራቸውን ሰምተናል። (ወሬ መቼም አይደበቅ!)
እሺ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ቢሞቱ ወይም አጓጉል ሆነው ቢቀሩ ቀጣዩ ጠቅላይ ሚኒስትር ማን ይሆናል። የህገ መንግስቱን 142 ገፆች ቢያገላብጡ ምንም ምላሽ የለውም። ስለዚህ በህገ መንግስቱ መሰረት ጠቅላይ ሚኒስትሩ መሞት አይችሉም ማለት ነው?
ጉድ እኮ ነው!
http://www.abetokichaw.com/2012

No comments:

Post a Comment