Translate

Sunday, July 29, 2012

‹‹ዘምሟል ጎራዴው››?

ከጋዜጠኛ ተመስገን ደሣለኝ
ዘመኑ ግንቦት ሺህ ዘጠኝ መቶ ሰማንያ ሶስት ነው፡፡ ‹‹ብሶት ወለደኝ›› የሚለው ጀግናው ኢህአዴግ አዲስ አበባን ‹‹ከወታደራዊ መንግስት›› ወደ ‹‹ታጋይ መንግስት›› ለማዘዋወር ጥቂት ቀናት ብቻ ቀርተውታል፡፡ በዚህ መሀልም የእንግሊዝ አምባሳደር ታጋዮቹ አዲስ አበባ ሲደርሱ ሊፈጠር በሚችለው ወታደራዊ ግጭት ስጋት ገብቷቸው ኢምባሲውን ለዘበኞችና ለኢትዮጵያዊያን ሰራተኞች ሀላፊነት ሰጥተው ወደሀገራቸው ሄዱ፡፡ ሀገራቸውም በደረሱ ጊዜ የኢትዮጵያ ሁኔታ ትኩረቱን የሳበው ቢቢሲ የተባለው አለም አቀፍ ሚዲያ አምባሳደሩን ‹‹የኮለኔሉ መንግስት እንዴት ነው?›› ሲል ጠየቃቸው፡፡ እሳቸውም እንዲህ ሲሉ መለሱለት ‹‹አይተርፍም! ዘምሟል ጎራዴው፡፡››
እነሆም ይህ ከሆነ ከሃያ አንድ ዓመት በኋላ የሀገሪቱ መንፈሳዊ አባት ፕሮፈሰር መስፍን ወልደማሪያም ሰኔ 8/2004 በታተመችው ፍትህ ጋዜጣ ላይ እንዲህ ሲሉ ፃፉ ‹‹በእኔ አመለካከት በአለፉት ሃያ አንድ ዓመታት የወያኔ/ኢህአዴግ አገዛዝ ውስጥ አንዳንዴ ቢሰናከልም ትልቁና ዋናው ጥቅም የጽሕፈት እገዳው መነሣት ነው፤ ይህ ነፃነት ሲጠፋ ጥፋቱ ሁሉ ሙሉ ይሆናል።››
እነሆም ከሐምሌ 13/2004 ዓ.ም ጀምሮ የመፃፍ መብት ሙሉ በሙሉ ተሰርዟል፡፡ ይህ የሆነው ደግሞ በገዥው ፓርቲ ውስጥ እየተፈጠረ ያለውን የሀይል ትግል ተከትሎ እያሸነፈ የመጣው ቡድን ለደጋፊዎቹ፣ ለአብዛኛው ካድሬ እና የየትኛውም ተፎካካሪ ቡድን ደጋፊ ላልሆኑት የኢህአዴግ አመራሮች ፍትህን ‹‹መስዋዕት›› (እጅ መንሺያ) ወይም በፖለቲከኞቹ አነጋገር ‹‹ድጋፍ ማሰባሰቢያ›› በማድረጉ ነው፡፡ ይህንን ሁኔታ በቀላል አማርኛ ስንገልፀው ደግሞ ‹‹በቀጣይ የአቶ መለስን ከስልጣን ገለል ማለትን ተከትሎ ሊፈጠር ይችላል ብለው የገመቱትን ‹የደህንነት› እና ‹ያለመረጋጋት› ስጋት ከአብዛኛው የስርዓቱ ተጠቃሚዎች አእምሮ ውስጥ እንዳይሰርፅ ለመከላከል ሲሉ ነው›› የሚል ሆኖ እናገኘዋለን፡፡ ለዚህም ነው ፍትህ ባለፈው ሳምንት በ‹‹ህግ››፣ በዚህ ሳምንት ደግሞ ‹‹ተቋም››ን በመጠቀም ሙሉ በሙሉ እንድትዘጋ የተደረገው፡፡
የሆነ ሆኖ እንደአክራሪ ሀይሉ አቋም ከሆነ ከዚህ በኋላ ፍትህን ልናሳትም እንደማንችል በገደምዳሜ እየተነገረን ነው፡፡ እናም ሁኔታው ሁሉ በደርግ ግብዓተ መቃብር ዋዜማ ‹‹አይተርፍም! ዘምሟል ጎራዴው›› ያሉትን ዲፕሎማት አያስታወሰኝ ነው፡፡ …ደህና! በሚቀጥሉት ጊዜያት የሚከሰተውን አዲስ ነገር አብረን እንጠብቅ፡፡

No comments:

Post a Comment