Translate

Wednesday, July 25, 2012

ህወሃት በምን ተጠምዶ ይሆን?

ይህ ጽሁፍ ኣቶ መለስ ታመዋል፤ ህመማቸው ለሞት ይሰጣል ወይም ቢድኑም ወደ መደበኛ ስራቸው ለመመለስ ኣይችሉም የሚሉትን መላምት የተመረኮዘ ኣስተያየት ነው። ታዲያ ይህ ዜና እውነት ከሆነ በዚህ ጊዜ ህወሃት በምን ሁኔታ ላይ ይገኝ ይሆን? ብለን እንድናስብ ማድረጉ ኣይቀርም።
ባለፈው ጊዜ “ኣቶ መለስ ሲሄዱ ምን ይፈጠር ይሆን?” በሚል ርእስ ስር ባነሳነው ግምት ላይ የ ጠቅላይ ሚኒስትሩ መሄድ ለለውጥ ትልቅ በር መሆኑን ጠቁመናል።ኣውሸልሽሎ የሚጀመር ኣስተዳደር ሩቅ እንደማይሄድም ጠቁመናል:: ብዙ ሰውም እንዲሁ ገምቱዋል። ታዲያ በኣቶ መለስ መሄድ የተፈጠረውን ክፍተት ለመድፈንና ስርዓቱ ሳይቀየር ኣውሸልሽሎም ቢሆን እንዲሄድ የሚሹ ኣንዳንድ ጽንፈኛ የህወሃት ኣባላትም ላይተኙ ይችላሉ።

ካለፉት ጊዚያት የህወሃት ባህርያት ተነስተን ስንገምት ባሁኑ ሰኣት ህወሃት በከባድ ሽምጥ ስብሰባ ላይ መሆኑ ይሸተናል ። ነባር የህወሃት ታጋዮችን ሳይቀር ካራቱም ማእዘናት ሰብስበው የተጣሉ ሁሉ ታርቀው በውይይት ላይ መሆናቸው ኣይቀርም። ታዲያ እንዴው ለህዝብ በተሰወረ ሁኔታ የሚያደርጉት ስብሰባ ላይ ምን ምን ጉዳዮችን ሊያነሱ ይችሉ ይሆን? ብለን ደሞ ማሰባችን ኣይቀርም። ክቻልን በዚህች ኣጭር ጽሁፍ የምናነሳው በዚህ ስበሰባ ላይ ሊነሱ ይችላሉ ብለን የገመትነውን ሲሆን መለወጥ እየፈለጉ ዋስትና ለሚፈልጉ ቡድኖች ደሞ ጥቂት የዋስትና ፍንጭ ለማሳየት እንሞክራለን።
በመጀመሪያ በኣጠቃላይ የህወሃት ስብሰባ ብዙ ሰው እንደሚገምተው ሁለት የተለያዩ ኣሳቦች የሚንሸራሸሩበት ሊሆን ይችላል። ኣንዱ ቡድን የተወሰነ ለውጥ ካላደረግን በዚህ መቀጠል ኣንችልም የሚል ሊሆን ሲችል ሌላው ደሞ በዚሁ መቀጠል ኣለበት የሚል ይሆናል። በኣጠቃላይ ያለፈውን ሀያ ኣመት ስራቸውን ሲገመግሙ ግን መቸም ጥሩ ሰርተናል የሚሉ ኣይመስልም። ምክንያቱም ጥሩ እንዳልሰሩ ያውቃሉ ህዝቡም ያውቃል። በሚዲያ ጥሩ ሰራን ቢሉም ለብቻቸው ሲሰበሰቡ ግን የሆድ የሆድ ሲያወሩ ግን ጥሩ እንዳልሰሩ መስማማታቸው ኣይቀርም። ታዲያ በዚህ ላይ ይስማሙ እንጂ በቀጣይ ጉዳይ ላይ ለሁለት መከፈላቸው ኣይቀርም። ከፍ ሲል እንዳልነው ኣንዱ እንለወጥ የተወሰነ እንራመድ የሚል ሲሆን ሌላው ቡድን ደሞ ለመለወጥ የሚያሰፈሩትን ጉዳዮች ኣንስቶ መከራከሩ ኣይቀርም። ለዛሬ ይሄ ቡድን ሊያነሳቸው ይችላል ብለን የገመትነውን ለውይይት ኣቅርበን ዋስትናዎቹን በጣም ውሱን በሆነ መልኩ እንጠቁማለን።
እነዚህ ወገኖች ከሚያነሱዋቸው ሃሳቦች መካከል
1) የሃብት ጉዳይ
እንደሚታወቀው በባለፉት ሃያ ኣመታት ጊዜ ውስጥ የህወሃትን የበላይነት ለማቆየት ከተመረጡት ዘዴዎች ኣንዱ የኢኮኖሚ የበላይነት ነው። ታዲያ በዚህ ጊዜ ኣንዳንዱ በደንብ እየታሰበበት ኣንዳንዱ ደሞ ድንገት ሰርኣቱ በፈቀደለት ክፍተት እየታገዘ ፍትሃዊ ባልሆነ መንገድ ከፍተኛ ሃብት ኣካብቱዋል። የኣገሪቱ ሃብትም በተለያዬ ዘዴ ወደ ኅወሃት ድርጅቶችና ደጋፊ ግለሰቦች የዞረበት ሁኔታ ጎልቶ ይታያል። በመሆኑም እነዚህ በያዘነው እንቀጥል የሚሉ ወገኖች እነዚህን ሃብት የተከማቸባቸውን ድርጅቶችና ግለሰቦች እናስጠቃለን ለውጥ ከመጣና ተቃዋሚዎች ስልጣን ከያዙ እነዚህን ሃብት የተጠራቀመባቸውን ድርጅቶች ያፈርሳሉ ማፍረስ ብቻ ኣይደለም ያላግባብ የበለጸግህ ነህ በማለት ሊያሰቃዩዋቸው ሊቀጡዋቸው ይችላሉ የሚል የስጋት ኣሳብ ሊነያነሱ ይችላሉ።
ዋስትናው
ለነዚህ ወገኖች ስጋት ዋስትና ኣለ። ይህ ዋስትና በቃ ያለፈው ኣልፉዋል የያዝከውን ይዘህ በየቤትህ እደር ከሚል ጀምሮ እነሱ እንደሚያስቡት ልክ ለውጥ እንደመጣ ባለፉት ሃያ ኣመታት ውስጥ ከመንግስት ጋ ንክኪ ኖሮት ያላግባብ የበለጸገውን ሁሉ ማንቁርቱን እየተያዘ ሃብቱን የሚያስረክብበት ሁኔታ ላይ ያተኮረ ኣይደለም። እነዚህ ሁለቱም ኣስተሳሰቦች ትንሽ ኣርቆ የማሰብ ችግር ያለባቸው ሳይሆኑ ኣይቀሩም።
ዋስትናው ይሄ ኣይደለም። ለነዚህ ወገኖች ትልቁ ዋስትና ኣዲስ የሚፈጠረው ስርዓት ሃብትን በችኮላ የሚበጣጥስና የሚያፈርስ ኣይሆንም። እነዚህ ያላግባብ በለጸጉ የተባሉ ቡድኖችም ሆኑ ግለሰቦች ችግር ችግሩ የግለሰቦቹ ወይም የቡድኖቹ ሳይሆን የስርዓቱ በመሆኑ ይህ ነገር የሚስተካከለው በሌላ ሰርዓት ነው።
በደርግ ጊዜ ኣንድ ታሪካዊ ስህተት ተፈጽሟል። ይሄውም የነበረውን የሃገሪቱን ሃብት ሲያዛውር በስርነቀል መልክ ስለ ነበረ ጥበብ በጎደለው መልክ ተከናውኗል። ያላግባብ በጭቁኑ ደምና ላብ በልጽጋችሁዋል የተባሉ ሁሉ እስር ቤት ገቡ ተገደሉ ሃብታቸውን ቀበሌ ወሰደው። እንዲህ ኣይነት የሃብት ዝውውር ካሁን በሁዋላ በሚመጣ ለውጥ ጊዜ ኣስፈላጊ ኣይደለም። እንዳልነው ብልጽግናው ከስርዓት ችግር ጋር ተያይዞ የመጣ መሆኑን መረዳት ተገቢ ነው። በዚህ ወቅት ያላግባብ የበለጸጉ ብቻ ሳይሆን ያላግባብ ባድሎ የትምህርት እድል እያገኙ የተማሩም ይኖራሉ። ኣዲሱ ስርዓት ያላግባብ ተምረሃልና መልስ ወይም ወንድምህ ኣይማርም ኣይልም። ይልቅ ኣዲሱ ስርዓት ሊያደርግ የሚገባው ምንድነው በኣንድ ኣካባቢ የተከማቸውን ሃብት በተለያዩ የሃብት ስርጭት ዘዴዎች (distribution of wealth mechanisms ) በመጠቀም ተመጣጣኝ እድገትን ማምጣት ነው። ይህ የሃብት ስርጭት ፖሊሲ ያለውን ሰፊ የሃብት ልዩነት እያጠበበ ደሞ የተከማቸውን ገንዘብ ወደ ልማት እንዲዞር ሁኔታዎችን እያመቻቸ የሚሄድ ስርዓት ነው። በመሆኑም በውስጣቸው ለውጥ እየተሰማቸው ነገር ግን ይህን ስጋት ያዳበሩ ሁሉ የሚመጣው ለውጥ በግብታዊነት የሃገሪቱን ሃብት የሚያፈራርስ እንደማይሆን መገመትና ለዚህም መታገል ነው ዋስትናው። ይህ ስጋት ያለባቸው የህወሃት ደጋፊዎችና ኣባላት የሚመጣው ለውጥ በዚህ መንገድ ተሳልጦ እንዲሄድ ቢያደርጉና ለዚህ ቢሰለፉ ስጋቱን ቀንሰው የረጋ እንቅልፍ ይተኛሉ።በኣዲሱ ስርዓት የሃብት ዝውውሩ የኣሁኑን ትውልድ ብቻ ሳይሆን የሚመጡትን ትውልዶች ሁሉ ያገናዘበ መሆን ኣለበት። ሃገር ከገንዘብ በላይ ነው። ገንዘበ ኣላፊ ጠፊ ነው፡፡ በሃቀኛ ካፒታሊሰት ስርኣት ውስጥ ኣንድ ሰው ሃበታም ሰለሆነ ባንድ ጊዘ ዘጠኝ ልብስ ለብሶ ኣይሄድም፡፡ ሃብታም ሆነ ማለት ሃላፊነት ተሸከመ ማለት ነው፡፡ ደሞ ከሁሉም በላይ ይህቺ ኣገር የኛ ብቻ ኣይደለችም ገና ሊመጡ ያሉ እልፍ ትውልዶች ሁሉ የሚኖሩባት ናት። በመሆኑም ባለፈው ሃያ ኣመት በተነጣጠቅነው ገንዘብ ኣስረክብ ኣላስረክብም ኣገር ኣይፈርስም። ከዚህ ይልቅ ከፍ ሲል እንዳልነው የተለያዩ ፍትሃዊ የሃብት ስርጭት ዘዴ በመጠቀምና የተጠራቀመውን ገንዘብ በልማታዊ ስራ ላይ እንዲውል በማበረታታት ስጋቱን መቀነስ ይቻላል፡፡
2) የብሄሮች ማንነት ጉዳይ
ይሄም መልኩን ለውጦም ይሁን በቀጥታ ሊነሳ የሚችል ሃሳብ ሊሆን ይችላል። በኣንዳንድ ቅን ኣባላት ዘንድ ህወሃት ለ ብሄሮች ማንነት የሞተ ሲሆን ተቃዋሚ ፓርቲዎች ስልጣን ከያዙ በኣንድነት ስም የብሄሮች ማንነት ሊጨፈለቅ ይችላል ይህም የሞትንለትን ኣላማ ያፍርሳል የሚል ይሆናል። እንደነዚህ ወገኖች እምነት የባህላዊ ቡድን ኣስተዳደር(Ethnic federalism) የተሻለ ሲሆን የሚመጡት ተቃዋሚዎች ግን ይህን ኣይቀበሉም የሚል ስጋት ይኖራል ።
ዋስትና
ለዚህ ዋስትናው ሃገሪቱ በሁለቱም ኣቅጣጫ የምታድግበትን ስርዓት መዘርጋት ነው። ወደላይ የተለያዩ ብሄሮች ባህላቸውን ቋንቋቸውን ጠብቀው የሚያድጉበትን የትምህርትና የባህል ፖሊሲ መንደፍ ወደጎን ከሌሎች የሃገሪቱ ብሄሮች ጋር እሴት የሚካፈሉበትን ፖሊሲ መዘርጋት ነው። ዋናው መረዳት መሆን ያለበት ለውጥ ሁል ጊዜ በህብረተሰብ ላይ ይሰራል። ለውጥ በባህል በቋንቋ ይሰራል። ይህን ታሳቢ ያላደረገ የፖለቲካ ቅንዓት ሳይንሳዊነትና ተፈጥሮዓዊነት ስለሚጎለው ለውጥን መቀበል ያስፈልጋል።
3) ለውጡን ተከትሎ የስነ ልቡና ችግር ሊፈጠር ይችላል የሚል ስጋት
ህወሃት ሁልጊዜ ራሱንም ሆነ ሌላውን ህዝብ የሚያየው ከውስጥ ወደ ውጭ ብቻ ነው። ይህ ተፈጥሮው ህዝብ ያላሳበውን እንዲያስብ በህዝብ ልብ ውስጥ የሌለውን ኣለ ተቀብሮ ነው ብሎ እንዲሰጋ ያደርገዋል። ባለፉት ኣመታት ኣብዛኛው ድል የኣንድ ኣካባቢ እንደሆነ ኣድርጎ የማቅረብ ኣዝማሚያ ታይቱዋል። ይህ ስነ ልቦና በርግጥ በተወሰነ ደረጃ ወደ ተራው ህዝብም ሳይሄድ ኣልቀረም። ካጠቃላዩ የፖለቲካ ድባብ ኣንጻር ዜጎች ራሳቸውን የሚገልጹት በብሄራቸው ሲሆን ይህ ስነ ልቡና ወደ ምን ኣመራ የኣመራር ችግሮች ሲከሰቱ የባለስልጣናቱ ኣካባቢ ሰዎች በግድ እንዲደግፍ ወይም ነቀፌታዎቹን እንዲደብቁ እንዲያፍሩ ያደርግ ጀመር። ከዚህ የተነሳ በኣስተዳደር ጉድለት ዙሪያ የሚነሱ ውይይቶች ሁሉ ወደ ብሄር እየሮጡ እየተጣበቁ ስለሚያስቸግሩ ኣምክህኖታዊ ውይይት ጠፋ። ኣሁንም ለውጥ ቢመጣ የህወሃት ደጋፊዎች በሌላው ዘንድ ከዘር ጋር በተያያዘ መሳለቂያ እንሆናለን። ተቃዋሚዎች ስልጣን ሲይዙም በተለይ በኛ ባህላዊ ቡድን ላይ ከፍተኛ የስሜት ስብራት ይደርስበታል ብለው የሚከራከሩ ይኖራሉ።
ዋስትናቸው
በመጀመሪያ ደረጃ ይህ ችግር ህወሃት በራሱ መነጽር ሲያየው የተጋነነ ያደርገዋል እንጂ የሚፈራውን ያህል በህዝቡ ልብ ውስጥ ኣይኖርም። የኢትዮጵያውያን ጥያቄ ወልደ ኪዳን መጣ ኣየለ ወይም ድሪባ ኣይደለም። ህዝቡ የሚሻው ከድህነት የሚያላቅቀው በቀን ሶስቴ የሚበላበትን መንገድ የሚያሳየውን መሪ ነው። ይህ ልቡ በተለያዩ ጊዚያት ታይትዋል። ከህወሃት ሰዎች የተሻሉ የሚላቸውን የሚደግፍበት ኣንዱ መነሻ ህወሃት የሚያየውን ያህል ህዝቡ በዘር ፖለቲካ መነጽር የሚያይ ኣለመሆኑን ነው። ሌላው ዋስትና ህወሃት ራሱ ኣዲስ ለሚመጣው ለውጥ ሲሰለፍና ለለውጥ ሃዋርያ ሲሆን ይሄ ከለውጥ በሁዋላ ሊከሰት ይችላል ተብሎ የሚፈራው የስነ ልቦና መጎዳዳት ይጠፋል። ድሉ የሁሉም የጋራ በመሆኑ ማንም በማንም ላይ ለመሳለቅ የሚስችል ከባቢ ኣይኖረም፡፡
4) የባንዲራ ጉዳይ
ይሄም የሚነሳ ሊሆን ይችላል። ኣንዳንድ ወገኖች መለወጡን የመንግስት ሽግሽጉን ኣምነው ነገር ግን ባንዲራው እንዲቀጥል የሚፈልጉ ይኖራሉ። ይህ ባንዲራ ቀድሞ በነበረው ላይ ሌላ ምስል ተልጥፎበት ይገኛልና በህይወት እያለን ሊለወጥ ኣይችልም የሚል ስሜት ይኖራል። የትግላቸው ተምሳሌት ኣመጣን ለሚሉት ለውጥ ታሪክ ኣድርገው የሚያዩ ሁሉ የሚመጣው ተቃዋሚ ይህን የመለወጥ ፍላጎት ሊኖረው ይችላል የሚል ነገርም ሊነሳ ይችላል።
ዋስትና
በመሰረቱ ደርግም ሲመጣ የሃይለ ስላሴን ባንዲራ ቀይሯል። ሁሉም በታሪክ መዝገብ ይመዘገባል። ዋናው በታሪክ መዝገብ መቀመጡ ሲሆን ትውልድ እያለፈ ትውልድ ሲተካ የሚሆነውን ኣናውቅም። ዋናው ግን ህዝብ በዚሀ ላይ ልቤ ያርፋል ካለ ማስገደድ ኣይቻልም። በመሆኑም የባንዲራ ጉዳይ ሲናገሩ ጎሮሮኣቸው ላይ ሳግ የሚተናነቃቸው ካሉ ሃላፊነቱ የህዝብ መሆኑን ማወቅ ነው ልባቸውን ሊያሳርፍ የሚገባው።
5) እልህ
ሌላው ኣገራችንን የጎዳው ትልቁ ችግር መንግስት እንደ መንግስት ያለማሰቡ ነው። ኣንዳንድ ግለሰቦችም ይሁኑ ቡድኖች በመንግስት ላይ ነቀፌታ ሲሰነዝሩ መንግስት መንግስትነቱን ወዲያ ይወረውርና በግለሰቦች ብሽሽቅ ውስጥ ገብቶ ይታያል። ለዚህም የመንግስትን ተቋማት ሳይቀር መሳሪያ እያደረገ ሲጠቀም መቆየቱ ያሳዝናል። መንግስት ልበ ሰፊ ሆኖ እንደ መንግስት ካላሰበ በዚህ ቀላል በሚመስል ብሽሽቅ ኣገር ሊፈርስ ይችላል። ኣሁንም በዚህ በህወሃት ስብሰባ ላይ ኣንዱ በግለት ሊነሳ የሚችለው ነገር የባህል ቡድንን ካባ ለብሶ ረግጠንም ቢሆን መግዛት ኣለብን የሚጮኸው የከሌ ብሄር ነው፣ እኛን ትግሬዎችን ንቆ ነው ወይ? የሚሉ ፉከራዎች ስብሰባውን ኣምክህኖታዊነት እንዳይኖረው መፈታተኑ ኣይቀርም። ለዚህ ነገር ምንምን ኣይባልም። ኣባካችሁ ይህቺ ኣገር የኛ ብቻ ኣይደለችም ኣገር በ እልህና በቁጣ ኣይፍረስ የሚሉ ሽማግሌዎችን እንዲሰጠን መጸለይ ነው። ሃገር ሲመሩ ከነዚህ ስሜቶች መራቅ ነው ትልቁ የሃላፊነት ስሜት መለኪያው።
እግዚኣብሄር ኢትዮጵያን ይባርክ!
ገለታው ዘለቀ
geletawzeleke@gmail.com

No comments:

Post a Comment