Translate

Monday, January 26, 2015

በትንሹ የምንነግራችሁ ነገር ቢኖር… ይህ እየሆነ ያለው ኢትዮጵያ ውስጥ ነው!

11111
ጥቁር ሽብር …በኢትዮጵያ ምድር! (ዳዊት ከበደ ወየሳ እንደዘገበው)
(ኢ.ኤም.ኤፍ) በኢትዮጵያ ውስጥ በመንግስት ድጋፍ የሚደረገው የአሸባሪነት ተግባር እንደቀጠለ ነው። በከተሞች አካባቢ በህግ ሽፋን ዜጎች በአሸባሪነት ተፈርጀው ይታሰራሉ። ወደ ገጠር ስንሄድ ደግሞ፤ ኢትዮጵያውያን ያለምንም ጥያቄ በጠራራ ጸሃይ ተገድለው፤ ለአስከሬናቸው እንኳን ክብር ሳይሰጥ በአደባባይ ህዝብ እንዲያያቸው እና እንዲሸማቀቅ ይደረጋል። ይህ በኢትዮጵያ ታሪክ ውስጥ እጅግ ዘግናኝ የሆነ ጥቁር ሽብር እየተከናወነ ያለው፤ በዜጎች ላይ ነው። በፍርድ ቤት የሞት ፍርድ ተፈርዶባቸው ሳይሆን፤ የኢህአዴግ ደጋፊዎች ነን በሚሉ ሰዎች ድጋፍ የሚከናወን ነው – እንዲህ ያለው ግድያ።

አብዛኛው ግድያ ከመፈጸሙ በፊት ዜጎች ተደብድበው እና ተሰቃይተው ነው – የሚሞቱት። ለምሳሌ በዚህ ፎቶ ላይ የሚታየው ከተማ ውበቱ የተባለው ሰው ኢህአዴግን በመቃወሙ ነው የተገደለው። ሆኖም የታጠቀ ለማስመሰል ከገደሉት በኋላ ጠመንጃ እንዲያነግት ተደርጓል። ጠመንጃውም ሆነ አብሮት ያለው ዝናር ወይም ቦንብ ግን የከተማ ውበቱ ሳይሆን የራሳቸው የወያኔ ሰዎች ንብረት ነው። እንዲህ አይነቱ የቦንብ እና የባትሪ መያዣ በራሳቸው በወያኔ ሰዎች በእጅ እየተሰፋ የሚዘጋጅ፤ ሲሆን በፎቶው ላይ በሟች ከተማ ውበቱ ላይ ያንጠለጠሉት መሳሪያ እና የትጥቅ መያዣም የህወሃት ሰዎች መገልገያዎች ናቸው።
ሟች ከተማ ውበቱን ከነጓደኛው ከገደሉ በኋላ በዚህ አይነት የከተማው ህዝብ እንዲያያቸው ሲደረግ፤ ሟቾቹ ሽፍታዎች መሆናቸው ነው – ለህዝቡ የተነገረው። ከመሞታቸውም በፊት የታሰረው እግራቸው ከሞቱ በኋላም እንኳን አልተፈታም። አንድ ሰው ሽፍታ ከሆነ ሁለት እግሩን አስሮ አይዋጋም፤ በፎቶው ላይ በግልጽ እንደሚታየው ግን ከተማ ውበቱ እግሩ ታስሯል። ይህ የሚያሳየው …ከመገደሉ በፊት ታስሮ ሲሰቃይ እንደነበረ ነው።
በኢትዮጵያ ህገ መንግስት የሰብ አዊ መብት አያያዝ የተደነገገ ቢሆንም፤ በየእለቱ በኢህአዴግ ሰዎች በግልጽ ይጣሳል። በኢትዮጵያ ወንጀለኛ መቅጫ ህግ መሰረት፤ መግደል ብቻ ሳይሆን አስከሬንን አለማክበር ጭምር፤ አስከሬኑን አለማክበር ብቻም ሳይሆን አንድ ሰው ከሞተ በኋላ ራሱን መከላከል በማይችልበት ሁኔታ የሟችን ስም ማጥፋት ያስቀጣል። እየተደረገ ያለው ግን ከዚህ በተቃራኒ ነው።
የሟቾቹ አስከሬን መሬት ለመሬት እየተጎተተ ለህዝብ እንዲታይ ተደርጓል። ከሞቱም በኋላ… ያለሃጢያታቸው ስም ሰጥተው “ሽፍቶች ናቸው” ብለዋቸዋል። በነገራችን ላይ… ይህ ሁሉ የሆነው ከጥቂት ሳምንታት በፊት በሸዋ ክፍለ ሃገር በኦሮሚያ ክልል ውስጥ ነው። ቦታው ሰላሌ ውስጥ፣ ደራ አውራጃ፤ ጎሮ መስቀላ ከተማ ውስጥ ነው። ይህ አይነቱ በመግስት ድጋፍ የሚካሄድ ጥቁር ሽብር አዲስ ነገር አይደለም። ሆኖም “ሰልጥነናል፤ በኢትዮጵያ ውስጥ ሰላም እና ፍትህ ነግሷል” ብለው ለሚመጻደቁ የኢህአዴግ ደጋፊዎች ጭምር ይህንን ሃቅ እንዲያውቁት ማድረግ ያስፈልጋል።
እዚህ ላይ አንድ ነገር መጨመር ያስፈልጋል። እነዚህ ሰዎች በኢህአዴግ አስተዳደር የሚደረገውን በደል ስለተቃወሙ የተገደሉ ናቸው። ነገር ግን ሰው ሽፍታም ቢሆን፤ በውትድርና ላይ የተሰማራ ታጣቂም ቢሆን፤ የገደለም ቢሆን በህግ አግባብ ይዳኛል እንጂ፤ በአደባባይ ተደብድቦ አይገደልም። ስልጣኔም ቢሆን ሊለካ የሚገባው በፎቅ እና በመንገድ ብዛት ብቻ ሳይሆን ሰብአዊ ክብርን በመጠበቅ ጭምር ነው። ሰላማዊ ዜጋን መግደል ጀግና አያስብልም፤ በአጠቃላይ ህግን አለማክበር መሰልጠን ሊሆን አይችልም። መንገድ እና ፎቅ በመሆኑም ሌላው ኢትዮጵያዊ እንዲያውቀው ብቻ ሳይሆን፤ በኢትዮጵያ የሚገኙ የመንግስት ባለስልጣናት ጭምር ይህን ጉዳይ እንዲመለከቱት ማድረግ ያስፈልጋል። ምንም ማድረግ ባይችሉ እንኳን ይህን መልእክት Share በማድረግ ወንጀለኞችን ይቃወሙ፤ ሙታንንም ይታደጉ።

No comments:

Post a Comment