Translate

Monday, January 19, 2015

ኢትዮጵያና የካቲት 11 ቀን 1967 ዓ. ም (ገብረመድህን አርአያ፣ አውስትራሊያ)

ኢትዮጵያና የካቲት 11 ቀን 1967 በሚል ርእስ ለሁሉም ኢትዮጵያዊ ማቅረብ ተገቢ ነው ብዬ ተነሳሁ። የማቀርበውም ባጭሩ የሚከተሉትን በተመለከተ ይሆናል፤ የየካቲት 11 ቀን 1967 ዓላማ፤ ፖሊሲው፣ ለማን እና ለምን እንደተፈጠረ።
The Tigrayan People's Liberation Front (TPLF)
ቅድመ የካቲት 1967 ዋናው አስኳሉ የተፈጠረው፣ ማሕበር ገስገስቲ ብሄረ ትግራይ (ማገብት) በ1965 አካባቢ በቀ. ኃ. ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ ነው። በትምህርት ላይ የነበሩ የትግራይና የኤርትራ ተማሪዎች ተሰብስበው ያቋቋሙት ማህበር ነው። ይህ ማህበር እንደተፈጠረ የወሰድው አቋምና የሚከተለው ፖሊሲ፣ በረቀቀ መንገና ጥናት ጸረ ኢትዮጵያ አንድነትና ሉአላዊነት፣ የኢትዮጵያን ህዝብ አንድነት፣ ፍቅርና ስላም ለማፍረስ የወጠነ ነው። ኢትዮጵያ ውስጥ ኹከትና ብጥበጥ እንዲፈጠር የወሰነ በባእዳን የተፈጠረ ማህበር ነው። ማገብት ገና በረሃ ሳይወጣ ያዘጋጀው ፖሊሲው፣ ኤርትራና ትግራይ ነፃ የነበሩ ሃገራት ሲሆኑ በአማራው መንግሥት ቅኝ አገዛዝ ስር የወደቁ ናቸው የሚል ነው። አማራው የትግራይ ህዝብ ድመኛ ጠላት ስለሆነ ከሚኖርበት መሬት ዘሩን ማጥፋትና፣ በማንኛውም ጊዜ ህብረተሰብአዊ እረፍት እንዳያገኝ እናደርገዋልንም የሚል ፖሊሲ ነው።

በተጨማሪም፣ ማገብት ተስፋፊነቱን በመቀጠል ታላቋ የትግራይ ዲሞክራሲያዊ ሪፓብሊክ መንግሥት ለማቋቋም በማለም፣ ከሰሜን ጎንደር ወልቃይት፣ ፀገዴ፣ ፀለምት፣ ሁመራ፤ ከደቡብ ወሎ ደግሞ አሸንጌን ጨምሮ ወልዲያ፣ ራያና ቆቦን፣ አላማጣ፣ አፍላ ደራን ወዘተ ለም መሬቶችን በሙሉ ወደ ትግራይ ለማጠቃለል ያለመ ፖሊሲ ነው።
ሻእቢያ ማገብትን ለማጠናከር ብዙ ገንዘብ በማፍሰስና የተማሩ ኤርትራውያንን የሃሳብ ድጋፍ በማግኘታቸው ማህበሩም መሪዎቹም ተጠናክረው ወጡ። በቡድን የተሰባሰቡት የማገብት መሪዎች፣ አረጋዊ በርሄ፣ ግደይ ዘርአጽዮን፣ አባይ ፀሃየ፣ ስዩም መስፍን በዋናነት የሚጠቀሱ ናቸው። ዋናው መሪ ደግሞ አረጋዊ በርሄ ነበር። አባላቱ ደግሞ መለስ ዜናዊ፤ ስብሃት ነጋ፣ የማነ ኪዳነ፣ ቴዎድሮስ ሃጎስ፣ አስፍሃ ሃጎስ ወዘተ ሲሆኑ ዋናዎቹ አባላት ኤርትራውያን ነበሩ።
የማገብት መሪዎች ወደ ኤርትራ ጉዞ
የማገብት መሪዎች አዲስ አበባ ሆነው የሚፈልጉትን የፕሮግራም ዝግጅት ካጠናቀቁ በኋላ በጥር ወር 1967 አረጋዊ በርሄ የሚመራው ቡድን ሳህል በርሃ በመሄድ የአንድ ወር ወታደራዊ ትምህርትና ሥልጠና ከወሰደ በኋላ ወደ ደደቢት በረሃ አቀኑ። ቀደም በማለት ደደቢት በረሃ ይጠባበቁ የነበሩትም ተቀላቀሉ። የካቲት 11 ቀን 1967 የትጥቅ ትግሉ መጀመሩን በዋናው መሪ አረጋዊ በርሄ ታወጀ። የድርጅቱ ስምም፤ የዛሬው ህወሓት፣ ተጋድሎ ሓርነት ህዝባዊ ትግራይ (ተሓህት) ተብሎ ተሰየመ።
የፕሮግራሙ ዝግጅት
ቀደም ብሎ በረቂቅ የተዘጋጀው የፕሮግራም ፖሊሲ፣ ደደቢት በረሃ እንደገቡ በመጽሐፍ መልክ ሆኖ በእጅ ጽሑፍ እንዲዘጋጅ ተወሰነ። ለዚህ ሥራ አረጋዊ በርሄ፣ አባይ ፀሃየ፣ ስዩም መስፍን፣ ስብሃት ነጋ፣ መለስ ዜናዊ፣ ስየ አብርሃና አውአሎም ወልዱ በመተባበር እንዲያዘጋጁት ተወሰነ። በትብብር ካዘጋጁት በኋላ፣ ስዩም መስፍን ሱዳን ደረስ በመሄድ በመጽሐፍ መልክ ተዘጋጅቶና ተባዝቶ እንዲያመጣ ተላከ፣ አዘጋጅቶም ደደቢት በረሃ ተመለሰ። በጊዜው የተሓህት የድርጅቱ ሊቀመንበር አረጋዊ በርሄ ሲሆን፣ የአመራር ቡድኑ ደግሞ ግደይ ዘርአጽዮን፣ አባይ ፀሃየ፣ ሥዩም መስፍን፣ አግአዚ ገሰሰ፣ ገሰሰ አየለ፣ ሃይሉ መንገሻ (ነጠበ)፣ አስፍሃ ሃጎስ ነበሩ።
የዲማ ኮንፈረንስ
ዲማ በአጋሜ አውራጃ የሚገኝ የቦታ ስም ነው። የዲማ ኮንፈረንስ የተጠራበት ህወሓት ምክንያት የሚከተሉትን አንኳር አጀንዳ በመያዝ ነበር፣
1. የካቲት 11፣ 1967 የተሓህት አንደኛ ዓመት ስለነበር ለማክበር፣
2. የተሓህት/ህወሓትን ፕሮግራም ፖሊሲ/ማኒፌስቶን ለማጽደቅ፣
3. የተሓህት/ህወሓትን የድርጅት ውስጠ ደንብ (ሕግና ስነስርዓት) ለማጽደቅና፣
4. አመራር ለመምረጥ ነበር።

በዚህ መሰረት በአሉ ተከበረ። ተሓህት በዚህ ጊዜ የነበረው የሰው ሃይል አነስተኛ ነበር። ቢሆንም ግን ሁሉም የተማሩ ታጋዮች ነበሩ። ፕሮግራሙን ለማጽደቅ ውይይት ሲጀመር፣ በአብዛኛው ታጋይ ከባድ ውዝግብና ጭቅጭቅ ተነሳ። ፕሮግራሙ ሆን ተብሎ ፀረ-የኢትዮጵያ ሉአላዊነት፣ ጸረ ሕዝብ፣ በታኝና ጎጠኛ ነው ብሎ በማስቀመጥ አንቀበለውም አለ። የድርጅቱ ሊቀመንበር አረጋዊ በርሄና ጥቂት ደጋፊዎቹ ብዙሃኑን ትጋዮች በምስፈራራትና ከባድ ተጽእኖ በማሳረፍ ኮንፈረንሱ ፕሮግራሙን ተቀብሎ አሳልፎታል በማልት በተግባር ላይ እንዲውል አስደረገ። አብዛኛው ታጋይ የተቃወመውን ሕግና ስነስርዓት ሊቀመንበሩ ተቀብለነዋል ብሎ ደመደመ። አምባገነንነቱ የተጀመረው ብዚህ አይነት ሲሆ፣ ከጥቂት ወራት በኋላ ተሓህት ወደ ፋሽስትነት ተሸጋገረ።
ማ/ኮሚቴው ተመረጠ፣ ይሁን እና ለእነ አረጋዊ በርሄ ትልቅ የራስ ምታት የሆነባቸው መለስ ዜናዊ ሳይመራጥ መቅረቱ ነበር። በጊዜው የተመረጡት የማ/ኮሚቴ አባለት፣ አረጋዊ በርሄ የድርጅቱ ሊቀመንበር፣ ግደይ ዘርአጽዮን፣ አባይ ፀሃየ፣ ስዩም መስፍን፣ ስብሃት ነጋ፣ አግአዚ ገሰሰ፣ ሙሴ ተክለ ናቸው። “ዘንበል አለ እንጂ አልፈሰሰም” እንደሚባለው፣ ከጥቂት ወራት በኋላ ሙሴ ተክሉና አግአዚ ገሰሰ በተንኮልና በተዘዋዋሪ መንገድ አመራሩ ካስገደላቸው በኋላ፣ ማሟያ በማለት መለስ ዜናዊ፣ ስየ አብርሃ፣ አውአሎም ወልዱ፣ አጽብሃ ዳኘው ወደ ማ/ኮሚቴና ወደ አመራር ሃላፊነት ወጡ። አጽብሃ ዳኘው በነበረው ጸረ ተሓህት ፕሮግራም ምክንያት ሃለዋ ወያነ ገብቶ ተገደለ። በምትኩ ዶ/ር አታክልት ቀጸላ ተመረጠ። እርሱም እንድዚሁ በተሓህት ፕሮግራም ከፍተኛ ተቃውሞ ስለነበረው ገደሉት። ተሓህት ቀስ በቀስ ፍጹም ፋሽስት በመሆን ተቃዋሚ የሆኑትን ታጋዮችም ሆነ ሕዝቡን መፍጀት ጀመረ። አረጋዊ በርሄ፣ አባይ ፀሃየ፣ ስብሃት ነጋ፣ ግደይ ዘርአጽዮን፣ ስዩም መስፍን፣ መለስ ዜናዊ፣ ስየ አብርሃ፣ አውአሎም ወልዱ በመተባባር ህዝብ የጨረሱ አረመኔ መሪዎች ናቸው። አሁን በሥልጣናቸው ስር ቢደበቁም ነገ ለፍርድ መቅረባቸው አይቀሬ ነው።
የተሓህት ፕሮግራምና የትግራይ ህዝብ
ተሓህት የካቲት 11፣ 1968 በዲማ ኮንፈረንስ ባሳለፈው ውሳኔ መሰረት፣
1. የተሓህት የልደት በዓል የካቲት 11፣ 1967 የትግራይ ህዝብ በየዓመቱ በድምቀት እንዲያከብር፣
2. ፕሮግራሙ በአስቸኳይ ወደ ትግራይ ከተሞች እንዲሰራጭ፣
3. በህዝብ ግንኙነት በኩል ፕሮግራሙ በሚሰጠው መመሪያ መሰረት በገጠሩም እንዲያስተምሩ ተወሰነ።

የገጠሩን ነዋሪ ህዝብ በተመለከተ
በገጠሩ ለሚኖረው ህዝብ፣ በህዝብ ግንኙነት ታጋዮች በኩል በፕሮግራሙ የተጻፉትን በፕሮፓጋንዳው ጽ/ቤት በኩል ይዞ ወደ ህዝቡ ቀረበ። የፕሮፓጋንዳው ርእሶች፣ 1. የኤርትራ ቅኝ ግዛት በኢትዮጵያ፣ 2. የትግራይ ቅኝ ግዛት፣ 3. አማራ የትግራይ ህዝብ ደመኛ ጠላት መሆኑ፣ 4. ወደ ትግራይ የተካለሉ፣ ሰሜን ጎንደርና ደቡብ ወሎ፣ 5. የካቲት 11ድን ህዝቡ ምግብና መጠጥ በማዘጋጀት ቀኑን በዘፈን እና በጭፈራ የደመቀ በዓል እንዲደረግ የሚሉ ናቸው።
የተሓህት ህዝብ ግንኙነት እነዚህን ይዘው በየቦታው ተሰማሩ። የትግራይ ህዝብ ከተሓህት ጎን በመሰለፍ ኤርትራን እና ትግራይን ከአማራው ቅኝ ግዛት ነፃ ያውጣ፤ አማራውን ተባብረን ዘሩን እናጥፋ፤ ሰሜን ጎንደርና ደቡብ ወሎ የትግራይ ህዝብ መሬት ነው እያሉ ለህዝቡ ቢለፍፉም፣ የማይቀበለው መሆኑን በግልጽና በየቦታው ተናገረ። በተለይም አማራ የትግራይ ህዝብ ደመኛ ጠላት ስለሆነ እናጥፋው የሚለውን ህብረተሰቡ በምሬት ነበር ያወገዘው። በዚህ ጊዜ ነበር ቂመኛው የተሓህት አመራር የትግራይን ህዝብ እየገደለ ንብረቱን በመውረስ ተግባር ላይ የተሰማራው።
የትግራይ ህዝብ ተቃውሞ
ይህ ቅስቀሳና ትምህርት በተሓህት የህዝብ ግንኙነት ለገጠሩ የትግራይ ህዝብ ሲቀርብ፣ አናምንበትም፣ አንቀበለውም በማለቱና ከፍተኛ የህዝብ ተቃውሞ ገጠመው። በጊዜው የነበረው አምስቱ የፖሊት ቢሮ አባላትና ሶስቱ የማ/ኮሚቴ አባላት ግራ ተጋቡ። ለጥቂት ወራት እየተከታተሉ ቢጠብቁም፣ የህዝቡ ተቃውሞ እየበረታ ሄደ። መፈናፈኛ ሲያጡ አስቀድመው ባቋቋሙት ሃለዋ ወያነ (06)፣ ማለትም፣ አዲጨጓር፣ በለሳ ማይሃምቶ፣ ወርዲ፣ አዴት ቆሎ ምሽላ፣ አዲ በቕሎ፣ ጻኢ፣ ቡምበት (ሽራሮ ሱር የተዘዋወረው)፣ ባኽላ በማጋዝ የትግራይ ህዝብ በቀን እና በሌሊት ከየአለበት እየተለቀመ፣ “ትግራዋይ ሸዋዊ” የትግራይ ሸዋ እየተባለ፣ ሴት፣ ወንድ፣ ሽማግሌ ሳይለዩ ፈጁት። መገደላቸው ሳያንስ ያፈሩት ጥሪትና ሃበት በተሓህት ተዘረፈ። ቤት ፈረሰ፣ አባትና እናታቸውን ያጡት ህፃናት ተበትነው ቀሩ። ለዚህ ምስክሩ የትግራይ ህዝብ ነው።
ከተማውን በተመለከ፣ ከፍተኛ ፀረ ተሓህት ተቃውሞ ተነሳ። አመራሩ በምንም አይነት መልኩ ሊቋቋመው አልቻለም። የፖሊት ቢሮው አመራር ከሻእቢያ ጋር በመነጋገር፣ በብስራት አማረ የሚመራ 50 ታግዮች ተመርጠው ኤርትራ በመላክ፣ በፈዳያንነት እንዲሰለጥኑ ተላኩ። ፈዳያን ማለት የአረብኛ ቋንቋ ሲሆን፣ አጥፍቶ ጠፊ፣ ሽብርተኛ (Terrorist) ማለት ነው። ሰልጣኞቹ ኤርትራ እንደገቡ በሔዝቡላና በሃማስ አሸባሪዎች ሰልጥነው ወደትግራይ ተመለሱ። ከነሐሴ 1969 ጀምሮ በሰባቱ አውራጃዎች፣ ራያን በርቀቱ ምክንያት ትተው፣ አድዋ፣ አክሱም፣ ሽሬ፣ ሁለት አውላእሎ፣ አዲግራት፣ ተምቤን መቀሌ ውስጥ በቀን ተመሳስለው በመግባት
በተደጋጋሚ፣ አስተማሪዎችን፣ ነጋዴውችን፣ ሰላማዊውን የከተማ ህዝብ ደሙን በየቦታው አፈሰሱት። የዚህ አይነቱ ግድያ በሰፊው በየከተማው ቀጠለ። አጥፍቶ ጠፊዎቹ ከህዝቡ አጸፋዊ መልስ ብዙም ስላልደረሳባቸው ግድያውን አፋፋሙት። በዚህ የሽብር ተግባር ተባባሪ በመሆን ህዝብ ያስፈጁና የፈጁ አመራሮች፣ አባይ ፀሃየ፣
ስዩም መስፍን፣ አርከበ እቁባይ፣ ዘርአይ አስገዶም፣ ሳሞራ የኑስ፣ ስየ አብርሃ፣ ሃለቃ ጸጋይ በርሄ፣ አባይ ወልዱ፣ ቢተው በላይ፣ ሙሉጌታ አለምሰገድ፣ ብርሃነ ገብረክርስቶስ፣ ተክሉ ሃዋዝ፣ አበበ ተ/ሃይማኖት በዋናነት የሚታወቁ ናቸው። በዚህ ወቅት በመቶዎች የሚቆጠሩ የከተማ ኗሪዎች በየቦታው ተገድለዋል፣ እነዚህ ንጹህ
ኢትዮጵያውን ደማቸው የፈሰሰውና ሕይወታቸው በአጭር የተቀጨው በተሓህት ፀረ-ኢትዮጵያ ፕሮግራም ምክንያት ነው። የተገደሉበት ምክንያትና ጥፋታቸው የተህሓት ፕሮግራም ፀረ-ኢትዮጵያ ሉአላዊነትና ፀረ-ህዝብ ስለሆነ አንቀበለውም፣ ማንነታችሁን እናውቃለን፣ የባንዳ ስብስብ ናችሁ በማለታቸው ነው። በተጨማሪም፣
የትግራይ ህዝብ የካቲት 11፣ 1967 የኛ በዓል ሳይሆን የገዳዮችና የማፊያዎች ነው ብሎ ተሓህትን አጥብቆ ስለተቃወመ የሕይወት መስዋእትነት የከፈለ ሕዝብ ነው።

የካቲት 11፣ 1967 የተሓህት የልደት በዓልና የትግራይ ህዝብ
በገጠር ኗሪው የትግራይ ሕዝብ የተሓህትን የልደት በዓል የካቲት 11፣ 1967ን እንዲያከብር ወንዱም ሴቱም በህዝብ ግንኙነት በኩል በጥብቅ የታዘዘው በ1970 ዓ. ም. ነበር። ነገር ግን ከህዝቡ የተገኘ ምላሽ አልነበረም። ቀኑ ሲደርስ በታዘዘው ቦት አንድም ሰው አልተገኘም። ይህ ሪፖርት ለፖሊት ቢሮው ሲቀርብ ተበሳጨ። የሰጠው መልስም፣ አድማውን የሚያቀነባብሩት የደርግ ሰላዮች፣ ፀረ-ተሓህት፣ ፀረ-ኤርትራ ትግል ስለሆኑ በሰላዮች እየተያዙና እየተጋለጡ ሃለዋ ወያነ (06) እየገቡ በርካታ ንፁሃን ዜጎች እየተሰቃዩ ለሞት ተዳረጉ፣ ሃብት ንብረታቸው በተሓህት ተወረሰባቸው፣ ቤታቸው ፈርሶ ቤተሰባቸው ተበተነ። የ1972ቱ የተሓህት ልደት በዓል በድጋሚ ህዝቡ ሳያከብረው ቀረ። የ1973ቱን የልደት በዓል ደግሞ በፖሊት ቢሮው ትእዛዝ ህዝቡ እየተገደደና የሁለት ቀን ቀለቡን ይዞ እንዲመጣ በህዝብ ግንኙነት በኩል ተነገረው። ባይወጣና በዓሉን ባያከብር ግን ከባድ እርምጃ እንደሚወሰድበት ተነገረው። አሁንም በብዙ ቦታ ሳይወጣና ለህወሓት ሳይንበረከክ ቀረ። ተገዶ የወጣው የተምቤን አውራጃ ህዝብ ብቻ ነበር።
የ1973ቱን በዓል ህዝቡን በማስገደድ እንዲከበር ለማድረግ ሁለት ወር ቀድም ብሎ በስብሃት ነጋ፣ አባይ ፀሃየ፣ መለስ ዜናዊ፣ ስየ አብርሃና ጻድቃን ገብረተንሳይ ተውስኖ ነበር። የ1973 በዓል በአብይ አዲ ከተማ ውስጥ የካቲት 11 ቀን ከቀኑ 9 ሰዓት እንዲከበር የጊዜ ሰሌዳ ወጥቶ፣ ህዝቡ የክት ልብሱን እየለበሰ በቦታው እንዲገኝ
ታዞ ነበር። ውሳኔው ህዝቡን በምክንያት ለጥቃት ለመዳረግ ሲሆን፣ ሃላፊነቱ የተሰጠው የቦታው ሃላፊ ለነበረው ለሙሉ ሰንድቅ ነበር። ዝግጅቱን በበላይነት እንዲቆጣተር የታዘዘው ትክሉ ሃዋዝ ሲሆን፣ በህዝብ ግንኙነቱ አማካኝነት ለሁለት ወራት ከፍተኛ ቅስቀሳ ተካሄደ። በከተማዋ ደርግን የሚያወግዙ መፈክሮች ተጽፈው ተዘጋጁ። የኢትዮጵያ ምድር ጦርም በቅርብ ርቀት ሃገረ ሰላም ሆኖ የሚደረገውን ሁሉ ይከታተል ነበር። ቀኑ ሲደርስ ተገዶ የወጣው ህዝብ የሁለት ቀን ቀለቡን ተሸክሞ ወደ አብይ አዲ ገባ። በአጋጣሚ የዚህ ጽሑፍ አቅራቢ እዛው ቦታው ላይ ነበርኩ። ጥዋት ከላይ የተጠቀሱት አመራር ቡድን ተገኝተዋል። መለስ ዜናዊና ስብሃት ነጋ ብቻ አልነበሩም። እኔና አባይ ፀሃየ አብረን ውለናል። ሰዓቱ ሲቃራብ፣ አባይ ፀሃየና ጻድቃን ቀስ ብለው ሾልከው ጠፉ። ስየን በርቀት አይቸው ነበር፣ እሱም በተመሳሳይ መንገድ ሾልኮ ጠፋ። የዚህ ሁሉ አስታባባሪ ተክሉ ሃዋዝ ነበር። ህዝቡ በጣም ብዙ ስለሆነ ገበያውን አጣቦት ነበር። ልክ 10 ሰዓት ሲሆን ሁለት ሚግ አይሮፕላኖች እየተመሙ መጥተው ህዝቡን ጨፈጨፉት። በናፓልና በሚምዘገዘገው መትረየስ ህዝቡ በየቦታው ተገደለ። 100 ሲሞት ከ300 ሰዎች በላይ ቆሰሉ። ሕዝቡ ሬሳውን ይዞ በሌሊት ከተማዋን ለቆ ወጣ። የኢትዮጵያ ህዝብ ሆይ የራስህ ወገን ኢትዮጵያዊው የትግራይ ህዝብ በተህሓት/ህወሓት እንዴት አንድርጎ እንዳጠቃህ ፍርድህን ስጥ። እኔ በበኩሌ የነበረውን ክፉ ጭፍጨፋና ግድያ ብትክክል አቅርቤዋለሁ።

ኢትዮጵያና የካቲት 11፣ 1967 ዓ. ም.
የተሓህት ልደት በዓል የካቲት 11፣ 1967 ዓ. ም. የተሓህት/ህወሓት ባንዳዎችና ማፊያዎች በዓል እንጂ የኢትዮጵያ ህዝብ በዓል አይደለም። ይህ ቀን ለኢትዮጵያና ለህዝቧ ክፉ ዘመን የወረደበት የህዝብ መቅጸፍትና ታሪካዊ ሃገር በማፍረስ፣ ህዝብ የመበታተን ክፉ አደጋ ይዛ የመጣች ዘመን ናት። ተሓህትን መስርተውና ህወሓት ብለው የሰየሙት፣ ከየካቲት 1967 ጀምሮ ለአስር ዓመታት ህወሓትን የመሩትና የትግራይን ህዝብ ያሰቃዩና ለሞት የዳረጉ ግለሰቦች ዛሬ በውጭ ሃገር ይኖራሉ። እነዚህ ግለሰቦች ከድረጅቱ የተባረሩት በሥልጣን ሽኩቻ ነው። በሥልጣን ባሉበት ጊዜ በሃገር ህዝብ ላይ ከፍተኛ ወንጄል ፈጽመዋል። በ1993 ዓ. ም. በተመሳሳይ መንገድ የተባረሩት እነ ስየ አብርሃም በሥልጣን ሽኩቻ ከመባረራቸው በፊት ሃገርና ህዝብ አውድመዋል። እነዚህም በወንጀል ከሚጠየቁት መካከል ናቸው። ስለ ከፍተኛ ወንጀል ካነሳሁ፣ አቶ ገብሩ አስራት ከፍተኛ የህወሓት መሪ በነበረበት ጊዜ ሃገር እንድትፈርስ፣ ህዝብ እንዲሰቃይና እንዲገደል፣ ሃገር እንድትቆራረስ በሚደረገው ተግባር ተሳታፊ መሆኑን በማመን ፣ “ሉዓላዊነትና ዲሞክራሲ” በሚለው መጽሐፉ እራሱን ማጋለጡና ጥፋቱን አምኖና ወደ ህዝቡ ቀርቦ በፈጸምኩት ወንጀል ተጠያቂ ነኝ፣ ህዝብ ይቅር ይበለኝ በማለቱ አድንቄዋለሁ። በሃገርና በህዝብ ላይ የተፈጸሙትን እና ያላነሳቸውን ከፍተኛ ወንጄሎች በሚቀጥለው መጽሓፉ ውስጥ እንደሚጠቅሳቸው በተስፋ እጠባበቃለሁ። እኔና ገብሩ አብረን ሠርተናል። ዋና አለቃዬ ሆኖ የፋይናንስ ሃላፊ በመሆን ድርጅቱን ማገልገላችን የማይካድ ሃቅ ነው። በዚህም ምክንያት ባህሪውን አውቀዋለሁ። የጀመረውን እቅድ ዳር ሳያደርስ አይመለስም። አቶ ገብሩ አስራት፤ የኢትዮጵያን ህዝብ ለጠየቅኸው ይቅርታ፣ ይቅር ባዩ የኢትዮጵያ ህዝብ ይቅር እንደሚልህ እምነት ይኑርህ። በሥለጣን ላይ ያላችሁ የህወሓት ፋሽስቱ ስርዓት አመራር ሆይ፣ የኢትዮጵያ ህዝብ ፍርዱን የሚሰጥበት ጊዜ ደርሷል።
ወደ ዋናው ሃሳቤ ስመለስ፤ የካቲት 11፣ 1967 የተሓህት/ህወሓት ልደት በዓል ፀረ-ሃገርና ጸረ-ህዝብ እንዲሁም ኢትዮጵያን ያፈረሰ፤ ህዝብ የበተነ የፋሽስት በዓል ነው።
ተሓህት/ህወሓት ያማራውን ህዝብ ዘር ለማጥፋት የተንቀሳቀሰው ከ1969 ጀምሮ ሲሆን፤ የሰሜን ጎንደር ህዝብ አማራ በመሆኑ ብቻ በአሰቃቂ ሁኔታ ጨፍጭፎታል፤ ገድሎታል፣ አሰባስቦ በቤቶች ውስጥ በማጎር በእሳት አጋይቶታል። በግንቦት ወር 1983 ሥልጣን ከያዘም በኋላ የጀመረውን ዓላማ ከግቡ ለማድረስ እስከ አሁኗ ጊዜ ድረስ ወደ 5 ሚሊዮን የሚጠጉ አማራዎችን ሕይወት አጥፍቷል። በተጨማሪም ህወሓት ሥልጣን ላይ ከወጣ በኋላ ኦሮሞው፣ ጋምቤላው፣ አኝዋኩ፣ ኦጋዴኑ፣ አፋሩ፣ መዠንገሩ ወዘተ ላይ ከባድ የዘር ማጥፋት ፈጽሟል። ሃገር ሽጧል፣ ህዝቡ ከየቦታው ተፈናቅሎ ሃገር አልባ ሆኗል።
ነፃነት
ውድ የኢትዮጵያ ህዝብ ሆይ!! ነፃነትህን የምትቀዳጀው በራስህ ህዝባዊ ማእበል ነው። እምቢ፣ በቃኝ፣ ለፋሽስቱና ሽብርተኛው የህወሓት ባንዳዎች አልገዛም ብለህ ተነሰተሃልና ትግሉን አፋፍመው። ይህ ፀረ-ህዝብና የባእዳን ቅጥረኛ ህወሓትና አጋሮቹ ብአዴን፣ ኦህዴድ፣ የደቡብ ህዝቦች በመባል የሚጠሩት ባንዳዎችና ሌሎቹም የሃገር ጠላቶች በሃይልህ ተወግደው መቃብር የሚገቡት ባንተ ሃይለኛ ክንድና ህዝባዊ አመጽ ብቻ ነው። ኢትዮጵያዊ ወገኔ ሆይ ተነሳ። መስዋእትነት የነፃነት ዋጋ ነው። የህዝብ ማእበል ምንም ሃይል አይመክተውም። የህወሓት ሽብርተኛው ስርዓት ኢትዮጵያን እና ህዝቧን ወሮ በቅኝ አገዛዙ ስር ካደራጋት 24 ዓመት ሆነ። ኢትዮጵያችንን አፈረሷት፣ ታሪኳን አጠፉ፣ ሕዝቧ ከመሬቱ እየተፋናቀለ ተበታተነ። ጊዜው አሁን ስለሆነ፣ በቃኝ በል፣ ፀረ-ወያኔ ህዝባዊ አመጹን እናቀጣጥለው። በጎጃም፣ በጎንደር፣ አምቦና አፋር ወዘተ እሳቱ ተለኩሷል፤ በርካታ ወጣቶች መስዋእት ሆነዋል። ኢትዮጵያችን አድኑኝ እያለች ነው። ወጣቶቻችን እንደ ልማዳችሁና እንደታሪክ ትግሉን ምሩልን፣ እኛም ከጀርባችሁ ነን እላለሁ
ድል ለኢትዮጵያና ህዝቧ!!

No comments:

Post a Comment