Translate

Saturday, January 24, 2015

“የአንድነት በር ለመዝጋት በሚታትሩት ልክ፣ ሌላ ትልቅ ይህችን ሀገር ወደ አደጋ የሚወስድ በር ይከፍታሉ” አቶ ግርማ ሰይፉ /የአንድነት ም/ፕሬዝደንት/


udj_udj12አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትሕ ፓርቲ ጥር 8 ቀን 2007 ዓ.ም ቀበና በሚገኘው ጽ/ቤቱ የመድብለ ፓርቲ ሥርዓት እንዳይፈጠር ምርጫ ቦርድ ታሪካዊ ስህተት እየፈፀመ ነው ሲል መግለጫ ሰጥቷል።
ፓርቲው እንዳለው፤ ቦርዱ በሕግ የተሰጠውን ኃላፊነት በብቃት ከመወጣት ይልቅ ለገዢው ፓርቲ ያለውን ወገንተኝነት በምርጫው ሂደት ዋዜማ በይፋ እያረጋገጠ ይገኛል። አሁንም ቦርዱ ወሰነ ተብሎ በሚዲያ የተገለፀው እንዲሁም ለፓርቲያችን በጽሁፍ የተሰጠው “በአስራ አምስት ቀን ውስጥ በጋራ ጉባዔ አድርጉ” የሚል ትዕዛዝ፤ ቦርዱ በተደጋጋሚ ፓርቲያችንን ደንብ እንዲያከብር እየጠየኩ ነው በማለት ከደንብ ውጭ እንድንሰራ የአዛኝ ቂቤ አንጓች ሆኗል ሲል ከሷል። የአንድነት ፓርቲ ጠቅላላ ጉባዔ የመጥራት ኃላፊነት ያለበት የአንድነት ብሔራዊ ምክር ቤት ወይም ደግሞ በአባላት ጥያቄ የጠቅላላ ጉባዔ አባላትን አንድ ሦስተኛ ፊርማ አሰባስበው በኦዲትና ኢንስፔክሽን ትዕዛዝ መሆኑ በግልፅ እየታወቀ ከፓርቲያችን መተዳደሪያ ደንብ ውጭ በ15 ቀን ውስጥ ጉባዔ ጥሩ የሚል ትዕዛዝ፤ ቦርዱ ከገዢው ፓርቲ ጎን ተሰልፎ እየተጫወተ አንድነትን ከጨዋታ ለማስወጣት ካልሆነ ሌላ ምንም ትርጉም ልንሰጠው አንችልም። ይህ ደግሞ ቦርዱ እየሰራ ያለውን ታሪካዊ ወንጀል ይፋ የሚያደርግ ነው ብሏል።

ይህ በማንአለብኝነት ስሜት የተሰጠ ውሳኔ ሳይታረም ቢቀርና ገዢው ፓርቲ ያለምንም ጠንካራ ተቀናቃኝ ብቻውን ሮጦ ብቻውን እንዲያሸንፍ የሚያደርግ ተቋማዊ ሴራ ቦርዱን በታሪክ ተጠያቂ ማድረግ ብቻ ሳይሆን በዚህች ሀገር ዘላቂ ሰላም ላይ ለሚፈጠረው አደጋ ቦርዱ ከተጠያቂነት እንደማይድን ለማስታወስ እንወዳለን።
በዚህ አጋጣሚ አንድነት ፓርቲ የሰላማዊ ትግሉን ወደላቀ ደረጃ ከፍ ለማድረግ እና ህዝቡን የስልጣን ባለቤት የማድረግ እንቅስቃሴውን አጠናክሮ እነደሚቀጥልና በቀጣይ ሳምንታትም በመንግስትና በቦርዱ ላይ ጫና ማሳደሩን እንደሚቀጥልበት እያረጋገጥን አንድነት ወደ ሕገወጥነት የሚወስደውን “የጋራ ጉባዔ” አካሂዱ የሚለውን የምርጫ ቦርድ ውሳኔ የማንቀበለው መሆኑን ለመላው አባላትና ደጋፊዎች ማረጋገጥ እንወዳለን ሲል በመግለጫው ጠቅሷል።
ከዚህ ጋር በተያያዘ የፓርቲው ምክትል ፕሬዝደንት አቶ ግርማ ሰይፉ ከጋዜጠኞች ለቀረቡላቸው ጥያቄ የሰጡትን ምላሽ በዚህ ዓምድ አስተጋግደናል።
ጥያቄ፡- ምርጫ ቦርድ በጋራ ጠቅላላ ጉባኤ ካላካሄዳችሁ የራሱን እርምጃ እንደሚወስድ ገልጿል። አሁን በሰጣችሁት ምላሽ ደግሞ ጠቅላላ ጉባኤ ዳግም እንደማትጠሩ አስታውቃችኋል። ስለዚህ በዚህ ሁኔታ መካከል ሊፈጠሩ የሚችሉ ነገሮችን ለማስተናገድ ፕላን ኤ..ፕላን ቢ..የያዛችሁት አለ?
አቶ ግርማ፡-አንድነት ፖለቲካ ትግል ውስጥ የገባው በሰላማዊ መንገድ ለመታገል ነው። ለኢትዮጵያ ሕዝብም የሚበጀው ሰላማዊ ትግል ብቻ ነው። ስለዚህ ከፕላን ኤ..ቢ.. እስከ ፕላን ዜድ ድረስ በሰላማዊ ትግል ማዕቀፍ ውስጥ ነው የሚወድቀው። ደረጃቸው ግን ይለያያል። መታወቅ ያለበት ምርጫ ቦርድ የቀረበለት ሰነድ አለ፣ በዚሁ ሰነድ ላይ ውሳኔ እንዲሰጥ ነው የተጠየቀው። ከዚህ በፊት የነበሩ ጠቅላላ ጉባኤ ሰነዶችም በእጁ ይገኛሉ። እነዚህን ሰነዶች መርምሮ ውሳኔ መስጠት ሲገባው፣ ይህን ስራውን ወደጎን አድርጎ በመሰለኝና በደስአለኝ ውሳኔ እየሰጠ ይገኛል። ቦርዱ ደብዳቤ ወጪ ሲያርግ በጥልቀትና በዝርዝር መርምረን ውሳኔ ሰጠን ይላል እንጂ ስብሰባ ሲገቡ በር ላይ ሆነው እንኳን የምናቀርበውን ነገሮች እንደማይመለከቷቸው ያስታውቃል። ይህን የሚያደርጉበት የራሳቸው ምክንያቶች ግን አሏቸው።
በደረስንበት መደምደሚያ የቦርዱ ጽ/ቤት ከአንድነት ፓርቲ ጋር ልዩነት አለን የሚሉትን ሰዎች በማደራጀት ጭምር ነው እገዛ የሚያደርጉላቸው። የቦርዱም ውሳኔ ከዚሁ መንፈስ ጋር የተያያዘ ነው። እኛ በበኩላችን የቦርዱን ውሳኔ አንቀበለውም። ይህም ሲባል፣ ጥያቄያችን አንድና አንድን ብቻ ነው። ይሄውም፣ ያቀረብነው ሪፖርት አለ፣ መርምረህ ውሳኔ ስጠን ነው ያልነው፤ ቦርዱን።ከዚህ ውጪ ተጣልታችኋል ታረቁ የሚል ከሕግ አግባብ ውጪ የሆነ ጥያቄውን አንቀበለውም።
ጥያቄ፡- ቦርዱ ለእናንተ በላከው ደብዳቤ ላይ ግልባጭ “ለእነአየለ” ቡድን የሚል አስፍሯል። ከዚህ አንፃር ቦርዱ “ለእነአየለ” ቡድን እውቅና መስጠቱን ያሳያል። ይህ ሆኖ ሳለ ጠቅላላ ጉባኤ ጠርታችኋል። አሁን በድጋሚ ጠቅላላ ጉባኤ አናደርግም የሚል አቋም መውሰዳችሁ፣ ካለፈው የቦርዱ ጥያቄ በምን ስለሚለይ ነው?
አቶ ግርማ፡- በግልባጭ “ለእነአየለ” ቡድን በማለት ቦርዱ ግልባጭ ማድረጉ እውቅና መስጠቱን ያሳያል ለተባለው እውቅና መስጠት ብቻ ሳይሆን አውቆ እያደራጃቸው ነው። ስለዚህ ቦርዱ አያውቃቸውም አንልም። ከዚህ በፊት ቦርዱ በሚጽፍልን ደብዳቤ ላይ ግን “ለእነአየለ” የሚል ግልባጭ አልደረሰንም። የመጨረሻውን ጉባኤ ተገኙ ብለን ጥሪ ስናስተላልፍላቸው፣ እሁድ ጠቅላላ ጉባኤ ልናካሂድ ቅዳሜ ጠርተው ደብዳቤውን የሰጡን። ይሄ የሚያሳየው የተሟላ ጠቅላላ ጉባኤ ማን ሊያካሂድ እንደሚችል ስለሚያውቁ ነው። በነገራችን ላይ ከአንድነት አኩርፈን ሄደናል የሚሉት ወገኖች ጠቅላላ ጉባኤ አድርገናል አላሉም። ምርጫ ቦርድ ነው፣ እነሱ ጠቅላላ ጉባኤ ማድረጋቸውን የሚገልጸው። በሚዲያዎች ማረጋገጥ ይቻላል። እንደውም ጥያቄ አቶ ትዕግስቱን ፕሬዝደንት አለው እንጂ እሱ እኔ ፕሬዝደንት ነኝ አላለም። ለጥያቄ ግን ፕሬዝደንት ነኝ ብሏቸው ከሆነ ሶስት ቦታ ሲሄድ ሶስት ነገር ያወራል ማለት ነው፣ ስለዚህም ተምታቶባቸዋል። አንዳንድ ቦታ ቅሬታችንን ለማሰማት አስተባባሪ ነን ነው የሚሉት። እነዚህን ሁኔታዎች ስንመለከት የዕውቅናው ጉዳይ በዋናነት የሚመጣው ከምርጫ ቦርድ በኩል መሆኑን ነው።
ይህም ስለመሆኑ ምንም ጥርጥር የለውም። የምርጫ ቦርድ ቢሮ ኃላፊው በአጋጣሚ የፓርቲያችን ፕሬዝደንት አቶ በላይ ፍቃዱ ስለማይደውልላቸው በደንብ ለይተው አላወቁትም። ሲደውል ከአኩራፊዎች አንዱ መስሏቸው “አምስት ተኩል ላይ ቀጥረናችኋል። ኑና የምንረዳችሁ ነገር ካለ እንረዳችኋለን” ብለውታል። This is really surprised! ከዚህ መነሻ ነው እኔና ስዩም ካለንበት ሮጠን ስንሄድ፣ የቦርዱን የጽ/ቤት ኃላፊን እጅ ከፍንጅ ነው ከአኩራፊዎቹ ጋር ሲወያይ የያዝነው። በምን መሰረት እንደሚያነጋግሯቸው አይታወቅም። በእሁድ ዕለት እንኳን ጠርተናቸው ምን ምን ማድረግ እንዳለባቸው መመሪያ የሚሰጧቸው ከጽ/ቤት ነው። ይህን ደግሞ ስብሰባ ውስጥ የነበሩ ልጆች ከቦርዱ ጋር እየተደዋወሉ መረጃ ሲቀባበሉ እያየን ነው። ይህ ተራ ውንጀላ አይደለም። መሬት ላይ ያለ እውነት ነው። ስለዚህ ቦርዱ “ለእነአየለ” ቡድን ብሎ በመጨረሻ ሰዓት ላይ መፃፉ፣ የቦርዱን የመጨረሻ ነገር ገልጦ ከማሳየት ውጪ እያደረገ ያለውን ነገር የሚደበቅ አይደለም። ይህንን ሁሉ ነው በትዕግስት ያለፍነው።
ጥያቄ፡- ምርጫ ቦርድ የአመራር ክፍፍል አለ ብሏል። በዚህ ላይ የእናንተ ምላሽ ምንድን ነው?
አቶ ግርማ፡- አንድነት ቤት ውስጥ የአመራር ክፍፍል የለም። ቦርዱ የአመራር ክፍፍል አለ እያለ በተደጋጋሚ ይገልፃል፣ ሬዲዮ ፋና በበኩሉ በተደጋጋሚ የአንድነት ቢሮ ያሉ እና ከቢሮ ውጪ ያሉ አመራሮች እያለ ይገልፃል። ይህ አገላለፃቸው መሬት ላይ የሌለ ቅጥፈት ነው። ይህን ለማረጋገጥ በእጃችሁ ላይ የገባውን ሰነድ ተመልከቱት። በዚህ ሰነድ ላይ የአንድነት አመራሮች ከ2004 ዓ.ም ጀምሮ በዝርዝር ተቀምጠዋል። በዚህ ዝርዝር ውስጥ አየለ ስሜነህ የሚል ስም የለም። ወይም አመራሩ ተከፋፍሏል የሚባለው ከዚህ ዝርዝር ውስጥ ማን እና ማን ሲወጡ ነው? ነገ በላይ አኩርፎ ቢሄድ አመራሩ ተከፋፈለ የሚያስብል አንዳች ነገር የለም። እኔ ነገ አኩርፌ ብሄድ አመራሩ ተከፋፈለ የሚባል ነገር የለም። ለእኩል መሰንጠቅ ቢከሰት እንኳን አመራሩ ተከፋፈለ ማለት የሚችለው ጠቅላላ ጉባኤው ብቻ ነው። አኩራፊው ቡድን ውስጥ አመራር የሆነ የለም። ከአኮረፈው ቡድን መካከል ለአንድ ሳምንት በቆየው በኢንጅነር ግዛቸው ካብኔ ውስጥ አቶ ትዕግስቱ አወልና የማነ ነበሩበት። እነዚህ ሰዎች ብዙውን ጊዜ ሥራ አስፈፃሚ አልተመረጥንም ብለው አኩርፈው ይሆናል ወይም በአዲሱ ካቢኔ ውስጥ አንካተትም የሚል ፍርሃት አድሮባቸውም ሊሆን ይችላል። አቶ ትዕግስቱ እስከ ትላንት ድረስ ም/የፖለቲካ ኃላፊ ሆኖ ሲሰራ የነበረነው ዛሬ ተጭበርብሯል እያለ የሚያወራው። ከዚህ መረዳት የሚቻለው በአንድነት አመራር ውስጥ ክፍፍል አለ የሚሉት ምርጫ ቦርድና ሬዲዮ ፋና ናቸው።
የምርጫ ቦርድ ተግባር በጣም ያሳዝነኛል፤ ያሳፍረኛል። የሬዲዮ ፋና ግን አይገርመኝም። ፋና የኢሕአዴግ ተቋም ነው። ስለዚህም ለእናት ድርጅቱ ወገቡን ይዞ ፋና እስክስታ ቢወርድ ስህተቱ አይታየኝም። ነገር ግን የምርጫ ቦርድና የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን ግን በጣም ያስገርማል። ምክንያቱም ኢብኮ በሕዝብ ግብር የሚተዳደርና ለሁላችንም እኩል ቦታ መስጠት የሚጠበቅበት ተቋም በመሆኑ ነው። ምርጫ ቦርድ ልንፈትነው እንደምንገባ እየነገርነው፣ ገለልተኝነቱን እንዲያረጋግጥ ፈተና እንደምንሰጠውም እየነገርነው ፈተናውን ለማለፍ ተግቶ ማጥናት የሚገባው ተቋም፣ ብንሳሳት እንኳን ስህተታችን እያረመ በኢትዮጵያ ብዘሃ ፓርቲ እንዲያብብ መስራት ያለበት ተቋም፣ ተንደርድሮ ወደላይ የወጣ ተቋም፣ በራሱ ጊዜ ወደታች እየወረደ ነው። ምንም ልንረዳቸው አንችልም። እናክብራችሁ ብለን ስናከብራቸው ለመከበር ዝግጁ ሳይሆኑ ቀርተዋል። ተቋሙ ሳይሆን ተቋሙን እየመሩት ያሉት ሰዎች ተቋሙን አይመጥኑትም። በቃ አይመጥኑትም። ሌላ ምንም ልንላቸው አንችልም።
ጥያቄ፡- በቦርዱ ላይ ጫና ማሳደር እንቀጥላለን ሲባል ምን ማለት ነው? አደጋዎቹስ ምንድን ናቸው?
አቶ ግርማ፡- ጫና ማሳደር ስንል ዝርዝር ነገሮች አሉ። ይህን የሚከታተል ምርጫ ቦርድ በአስራ ዘጠኝ ውሳኔ ከመስጠቱ በፊት የአንድነት አመራሮች፣ ብሔራዊ ምክር ቤት፣ ጠቅላላ አባላት የሚሳተፉበት ሁሉን አቀፍ እንቅስቃሴዎች እናደርጋለን። የተለያዩ ዝርዝሮቹን ኮሚቴው አውጥቶ ያሳውቀናል። በዚያን ጊዜ በሚዲያ ይፋ እናደርጋለን። ግን በፍጹም ቁጭ ብለን አስራ ዘጠኝን አንጠብቅም። አንድነት አባላት እንዳሉት እናሳያቸዋለን። የአንድነት አባላት ዲያፍሪክ የተሰበሰቡት አስር ሃያ ሰዎች ናቸው ወይም መቶ ወይንስ በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ የአንድነት አባላት መሆናቸውን በተግባር እናሳያቸዋለን።
አደጋው ምንድን ነው ለተባለው ግልፅ ነው። አንደኛ፣ የሚፈሩትን አብዮት ሊጠሩ ይችላሉ። ይህን አብዮት የሚጠሩት ደግሞ ሕዝቡ በሰላም በፈለገው መንገድ ለመንቀሳቀስ ሲዘጉበት ሊሄድበት የሚችለው አማራጭ ምን ሊሆን እንደሚችል ማወቅ አለባቸው። ይህን የአንድነት ቤት ለመዝጋት ሲያሴሩ ሌላ በጉልበት የሚከፈት በር እንዳለ ማወቅ አለባቸው። ይህ ስለመሆኑ ምንም ጥርጥር የለውም። አንዳንዱ …ተከዜ በረሃ መሄድ ሊመርጥ ይችላል። ተከዜ አልሄድም የሚለው ደግሞ የበደሉትን ሰዎች እዚሁ የሚፈትንም ይኖራል። ይህንን እኔ መወሰን የምችለው ሳይሆን እያንዳንዱ ሰው የሚወስነው ነው የሚሆነው። ይህን ምርጫ እያስገደዱ ያሉት ግን ገዢው ፓርቲና ምርጫ ቦርድ መሆናቸው ማወቅ አለባቸው። እደግመዋለሁ፣ የአንድነት በር ለመዝጋት በሚታትሩት ልክ ሌላ ትልቅ ይህችን ሀገር ወደ አደጋ ሊወስድ የሚችል በር ይከፍታሉ። ይህ እንዲሆን ምኞታችን አይደለም። በስርዓት ተከፍቶ በስርዓት በሚዘጋ በር ውስጥ መጠቀም አለባቸው ብዬ አስባለሁ።
ጥያቄ፡- ምርጫ ቦርድ በአንድነት ፓርቲ ውስጥ አሁን ያለው ሂደት ምርጫውን አስቸጋሪ ያደርገዋል ብሏል። በዚህ ላይ ምን ትላላችሁ?
አቶ ግርማ፡- ምርጫ ቦርድ በሚዲያ እየወጣ የሚገልጸውን አይታችሁት ከሆነ፣ በመጀመሪያ ጉዳዩ የሚመለከተን አካሎች ሳናውቅ ነው ለእናንተ የሚነግራችሁ። ይህ ነውር ነው። የፊደል ግድፈት እንኳን ቢኖረው ተነጋግረን መግለጫ ቢሰጡ ጥሩ ይሆን ነበር። ግን ውሳኔያቸውን በአደባባይ ይገልፃሉ። የሚገልጹበት ደግሞ ምክንያት አላቸው። አንደኛ፣ ብዥታ መፍጠር ነው። ብዥታ የሚፈጥሩት ደግሞ አንድነት ላይ ነው፣ ጥቅሙ ደግሞ ለገዢው ፓርቲ ነው። ምክንያቱም የአንድነት ሰዎች ለምርጫ እንዳይመዘገቡ ማድረግ ነው፤ ትልቁ አላማቸውም። እጅና እግራችንን አስረው ወደምርጫ እንድንገባ ነው፤ የሚፈልጉት። ሲያምራቸው ይቀራል እንጂ እንደዚህ አይነት ምርጫ እንደማንሳተፍ ማወቅ አለባቸው። እኛ ምርጫ የምንገባው ለማሯሯጥ አይደለም፣ ኢሕአዴግ የመጨረሻው እናደርጋለን ብለን ነው። ኢሕአዴግ ከሚያቀርበው በላይ ነው እጩ የምናቀርበው። ይህን ነግረናቸዋል። ይህን ማድረግ የሚችለው አንድነት ብቻ መሆኑንም ነግረናቸዋል። ይህን ውድድር ነው ለማጫወት ያልቻሉት። ምርጫ ቦርድ እንደጎበዝ ዳኛ ትንፋሹን ሰብስቦ ሊያጫውት አልቻለም። ኢሕአዴግ ብቻውን ከሮጠ ለመደመርም አይቸገሩም። ከኢሕአዴግ በላይ ነው የምናቀርበው። ኢሕአዴግ 547 ወንበር የሚያቀርበው ከአጋሮቹ ጋር ሆኖ ነው። እኛ ግን አራቱ ግንባር ድርጅቶች ከሚያቀርቡት በላይ እናቀርባለን ስንላቸው ነው ሽብርክ እያሉ ያሉት።
አላማቸው ይሄ ነው እንጂ ምርጫው ላይ ምንም ችግር ሊያመጣ አይችልም። በመጀመሪያ ደረጃ የምርጫ ምልክት ያስገባነው እኛ ነን። አንድነት ፓርቲ ነው የምርጫ ምልከት ያስገባው እንጂ አየለ ስሜ አይደለም ምልክት ያስገባው። አየለ ስሜነህ እጩ እየመለመለ አይደለም።
ሌላው ደግሞ በምርጫ ቦርድ አልሳካ ሲላቸው የገንዘብ ምንጫችሁ ምንድን ነው የሚል ሌላ ፈተና ይዘው መጥተዋል። ይህንንም በተለመደው መልኩ እናልፈዋለን። እጩዎች ወደ ምርጫ ሲገቡ ምን ያህል ገንዘብ እንደሚመድቡ መስፈርት አስቀምጠን ነው ወደ ምርጫ ውስጥ የገባነው። ህይወቱን ሊሰጥ የመጣ የአንድነት አባል ገንዘቡን የጓደኞቹን የአባላቱን ሰብስቦ ነው ምርጫ ውስጥ ለውድድር የገባነው እንጂ በማንም ተላላኪነት አይደለም ምርጫ ውስጥ የገባነው። ይህን ደግሞ የስማቸው ያህል ያውቁታል። ስለዚህ ምርጫውን እያደናቀፉ ያሉት ምርጫ ቦርዶች እንጂ እኛ አይደለንም። አየለ ስሜነህ አንድነት ውስጥ ገብቶ ካልፈተፈተ ምርጫው ትክክል አይሆነም የሚለው፣ የምርጫ ቦርድ ግምገማና የብዥታ መፍጠር ስራቸው ካልሆነ በስተቀር አንድም ከምርጫው ጋር የተያያዘ በቂ ምክንያት የላቸውም።
ጥያቄ፡- ምርጫ ቦርድ እንደአንድ የሕግ ሰውነት ያላው አካል መከሰስ መክሰስ፣ የሚችል ነው። አሁን ምርጫ ቦርድ የሚሰራው ከሕግ ውጪ ነው ብላችሁ የምታምኑ ከሆነ፣ ምርጫ ቦርድን በሕግ አግባብ ለምን አትከሱትም?
አቶ ግርማ፡- ወደፍርድ ቤት ለመሄድ ዝግጅታችን ጨርሰናል። ፍርድ ቤትም ፋይል አልከፍትም እንዳይለን ስጋት አለን። ይሄንንም መልሰን እንነግራችኋለን። በእኛ በኩል ግን አጠናቀናል። ፍርድ ቤት እናቆማቸዋለን። በኢትዮጵያ ውስጥ ያሉትን የዴሞክራሲ ተቋማት የሚባሉትን በሙሉ ፈትሸን ነው ገበናቸውን የምናስወልቃቸው። ከዚህ አንፃር ሁሉንም ነገሮች ነው የምንሞክረው።
ጥያቄ፡- ምርጫ ቦርድ የሚሰራውን አውቀናል ካለችሁ ሌሎች አማራጮችን ለማየት ለምን አትሞክሩም? ምርጫ ቦርድ በራሱ አዳራሽ ሁለታችሁንም ለጠቅላላ ጉባኤ ስብሰባ እንዲጠራችሁ ጥያቄ አቅርባችሁ፣ አሁን የምትተማመኑበትን ድጋፍ ይዛችሁ አሸንፋችሁ ለምን አትውጡም? ወይንስ እነዚህን አማራጮች ለመጠቀም የሚከለክል ሕግ ወይም ሁኔታዎች ይኖሩ ይሆኑ?
አቶ ግርማ፡- በጣም ጥሩ አማራጭ ነው። ስለእውነት ምርጫ ቦርድ የተፈጠረውን ችግር ወደሌላ አቅጣጫ ለመውሰድ ካልፈለገ በስተቀር፣ ለኢትዮጵያ ሰላም በቀናነት በራሱ አዳራሽ በራሱ ወጪ 320 የጠቅላላ ጉባኤ አባላትን አስጠርቶ፣ በሕጉ መሰረት ምርጫ ማድረግ ይችላል። ይህ ግን የግል አመለካከቴ ነው። የአንድነት አመራር ይቀበለው፣ አይቀበለው እርግጠኛ አይደለሁም።
መታወቅ ያለበት ግን በእኛ በኩል የጠቅላላ ጉባኤ ስብሰባ ሲደረግ ለሁሉም የጠቅላላ ጉባኤ አባላት ጥሪ አቅርበናል። ካኮረፉት መካከል የሚገኙትን የጠቅላላ ጉባኤ አባላት ለሁሉም ጥሪ አድርገንላቸው ሊገኙ አልቻሉም። የማይገኙበትን ምክንያትቸውን በሬዲዮ ፋና ላይ ቀርበው ተናግረዋል። ይሄውም ጠቅላላ ጉባኤው ላይ ብንሳተፍ በድምጽ ብልጫ ያሸንፉናል ብለዋል። ለማንኛውም ግን የጠቅላላ ጉባኤ ስብሰባውና ምርጫውን በተመለከተ በቪዲዮ ቀርጸን አስቀምጠንላቸዋል። አላየነም አልሰማንም እንዳይሉ። ፍርድ ቤትም ስንሄድ ስለሚጠቅመንም ጭምር ነው።

No comments:

Post a Comment