Translate

Tuesday, January 20, 2015

አቶ አንዳርጋቸው ፅጌን በጨረፍታ!

andargachew new picture
ግዛቸው አበበ
ከሁለት ሳምንት በፊት በዕለተ-እሁድ በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን የፖሊስ ፕሮግራም ላይ ቀርቦ፣ እንደገና ከአራት ቀናት በኋላ በእለተ ሐሙስ በድጋሚ የታየው፤ አቶ አንዳርጋቸው ፅጌን የሚመለከተው ፕሮግራም፤ ጃኬትና ሸሚዝ ሳይቀር እየተቀያየረ ተበጣጥሶ የተገጣጠመ መሆኑ በግልጽ የሚታይ ነበር፡፡
ይህ ፊልም የቀረበው፡- “በኢትዮጵያ እስር ቤቶች ውስጥ ሰቆቃ አይፈጸምም” ለማለት ተፈልጎ መሆኑ ይታወቃል። በእውነት በኢትዮጵያ እስር ቤቶች፣ የምርመራ ማዕከላትና በደህንነት ጽሕፈት ቤቶች ውስጥ ግፍና ሰቆቃዎች አይፈፀሙም ወይ? ለሚለው ጥያቄ እውነተኛውን መልስ መስጠቱ ነው። ሌላው ቢቀር በኢትዮጵያ ፍርድ ቤቶች ቀርበው በምርመራ ማእከላትና እስር ቤቶች ውስጥ ሰቆቃና ግፍ እየተፈጸመባቸው መሆኑን የገለጹ በጣም ብዙ ሰዎች ስላሉ መለስ ብሎ መመርመር ተገቢ ነው። በኢትዮጵያ ምድር አድራጊና ፈጣሪ የሆነው ሕወሓት፣ ለዓላማው ብሎ መሳሪያ አንግቦ የታገለ ድርጅት ነውና አቶ አንዳርጋቸውን በሚዛናዊ ዐይኑ እንደሚያይ ተስፋ አደርጋለሁ።

አቶ አንዳርጋቸው፣ ‘ምን አገባኝ’ ብለው ገዥው ቡድን በሰጣቸው ስልጣን የልባቸውን እየሰሩ የሕወሓት መራሹ ገዥ ቡድን አገልጋይ ሆነው መኖር ሲችሉ፣ ሕሊናቸው የማይፈቅደው ነገር ስላጋጠማቸው ስልጣናቸውን ጥለው መውጣታቸውን ማስታወስም ይገባል። በገዥው ቡድን ውስጥ ሆነው፣ በየሄዱበት በቡድናቸውን ላይ ሃሜትና ዘለፋ እየሰነዘሩ፣ ሲሾም ያልበላ ሲሻር ይቆጨዋል ብለው ስኳር በመቃም ላይ ከተሰማሩት፣ ጊዜ ሲያገኙ ደግሞ ሌላ ጥቃት ከማድረስ ወደ ኋላ ከማይሉት አስመሳይና ራስ-ወዳድ ባለስልጣናት ይልቅ አቶ አንዳርጋቸው ይሻላሉና ትክክለኛ ፍትሕ እና ክብር ይገባቸዋል።
ምንም እንኳ የተለያዩ ዓላማዎችን ያነገቡ ቢሆንም፣ የአቶ አንዳርጋቸው ጠብመንጃ ማንሳት፣ ከአቶ መለስ ጠብመንጃ ማንሳት ጋር ልዩነት የሌለው መሆኑ ግምት ውስጥ ገብቶ፤ ፍርዱ አሜሪካ-ሰራሽ ዘመናዊ የማጥቂያ ዘዴ ከሆነው ‘የሽብር ውንጀላ’ ተለይቶና በድጋሜ ታይቶ ለእስረኞች የተሰጠው መብት ሁሉ ለአቶ አንዳርጋቸውን እንዲሰጥ ማድረጉ ተገቢ ነው። እዚህ ላይ ሕወሓት እና የሕወሓት ባለስልጣናት፣ በአሜሪካ መንግት የሽብር መዝገብ ላይ እንደ ተቀመጡና ገና እንዳልተፋቁ ማስታወስ ተገቢ ይሆናል። የአቶ አንዳርጋቸው “አሸባሪ” መባል፣ ከኔልሰን ማንዴላ በአሸባሪነት መፈረጅ ጋር አንድ አይነት የሆነ የጉልበተኞች ስያሜ ነው፡፡
የአሜሪካ መንግስት፣ ትልቁ የሽብርና የሰቆቃ ተግባሩን የፈጸመው በጓንታናሞ-ኩባ፣ በአቡግሬቭ-ኢራቅ እና በባግራም-አፍጋኒስታን በመሳሰሉት የታወቁ እስር ቤቶች ውስጥ ብቻ አይደለም። የአሜሪካ መንግስትን ለትችትና ለውግዘት የዳረገው፣ በጆርጅ ቡሽ ዘመን በተቋቋሙት “Black prisons” በሚባሉት፣ ጥቂት የሲ.አይ.ኤ እና የኋይት ሃውስ ባለስልጣናት ብቻ በሚያውቋቸው እስር ቤቶች ውስጥ ያጎሯቸው በአስር ሺዎች የሚቆጠሩ “Ghost Prisoners” (የማይታዩ እስረኞች) እየተባሉ በሚጠሩ ታጋቾች ጉዳይ ጭምር ነው። በነዚህ እስር ቤቶች በብዙ ሺህ የሚቆጠሩ ሰዎች ሕይወት ተቀጥፏል። ቤተሰቦቻቸው የት እንዳሉ እንኳ ሳያውቁ ብዙዎቹ Ghost Prisoners እንደሞቱ ይቀራሉ፡፡ እንደ ማላላ የሱፍ፣ ድራማ አልተሰራላቸውም እንጂ በአስር ሺዎች የሚቆጠሩ ፓኪስታናውያን የነዚህ እስር ቤቶች ሰለባ ሆነዋል። ፓኪስታናውያን እናቶችና አባቶች፣ ልጆች፣ ሚስቶችና ባሎች፤ የተሰወሩባቸውን የቤተሰብ አባላቸውን ፎቶ እየያዙ በየዓመቱ ሰልፍ ይወጣሉ። ይህ ሁሉ ነው የአሜሪካን መንግስት ተጠያቂ ያደርገዋል፡፡
የአቶ አንዳርጋቸው አያያዝ ከአሜሪካዎቹ “Black prisons” ሁኔታ ጋር፣ ራሳቸው አቶ አንዳርጋቸውም ከአሜሪካዎቹ ከ “Ghost Prisoners” ጋር ይመሳሰላሉና በቤተሰቦቻቸው እንዲጎበኙ፣ በእምነት እና በጤንነት ረገድ ራሳቸው በሚያምኑበት ባለሙያ እንዲታዩ፣ ለቀሪ ቤተ-ዘመዶቻቸውና ወዳጆቻቸው ሲባል ደግሞ የቀይ መስቀልን ልዑካንን በመሳሰሉ ቡድኖች አልፎ አልፎ እንኳ እንዲታዩ ቢደረግ፣ ከአሜሪካ መንግስት ጋር አንድ አይደለንም ብሎ ለመሟገት ይቻል ይሆናል። ሾላ በድፍኑ ሙግት ግን ማንንም አያሳምንም።
የዚህን ቪዲዮ ነገር ካነሳን አይቀር አንድ ሌላ ነጥብ እንጨምር። አቶ አንዳርጋቸው፣ በውጭ ስለሚኖረው ወገን እና ስለ ተቃዋሚዎች የተናገሩት ነገር አለ። ተቃዋሚዎች የሰጡት አስተያየት ባይኖርም፣ በውጭ ያሉት ሰዎች ግን ቅሬታ -አዘል ጥያቄዎችን አንስተዋል። ‹አቶ አንዳርጋቸው ለምን ይህን ተናገረ?› ብለው ለመተቸት ዳር ዳር ሲሉም ታይተዋል።
ይህ የአቶ አንዳርጋቸው ንግግር የተሰማበት ጊዜ በራሱ ትኩረትን የሚስብ ነው። ኢሳት ላይ ሰሞኑን የሚንጸባረቀው ነገር፣ አገር ውስጥ መኖርና በአገር ቤት ለመኖር ሲባል የሚደረግ ድርጊትን ሁሉ በጅምላ የሚተች፣ አለፍ ካለም ዜጋውን ሁሉ በወያኔነት ፈርጆ የሚዘልፍ እየሆነ ነው። ይህ ደግሞ በውጭ መኖርን የጀግንነት፣ የታጋይነትና የአገር ወዳድነት ምልት አድርጎ እስከመስበክም የደረሰ እንዲሆን አድርጓል። አውሮፓና አሜሪካ መግባት ስደት ሊሆን ይችላል ወይም ምቾትን ፍለጋ መንከራተት። የሚወስነው የሰውየው ልብ ነው። አሜሪካና አውሮፓ የገባ ሰው፣ በረሀ የገባ ይመስል ‘ይህ ሕዝብ አንቀላፍቷል’ እያለ መወረፍ ሲጀምርና ለሕዝቡ የጀግንነት ግንዛቤ ካልሰጠሁ ብሎ ያዙኝ ልቀቁኝ ማለቱ ግን ትርጉም ያለው ነገር አይደለም። የዚህ ዓይነት ሰው አስተዋጽዖ ማድረግ የሚገባውም በዚህ መንገድ አይደለም። የወያኔና የሻእቢያ መሪዎችም ሆኑ ሚዲያዎቻቸው ስራቸውን ሲሰሩ የነበሩት፣ አውሮፓና አሜሪካ ቁጭ ብለው አይደለም። ትእዛዝ ከሚሰጡት ሰው መካከል በአካል ተገኝተው ነው። የኢሕአፓና የኦነግ መሪዎች ደግሞ እናዋጋለን፣ እንመራለን፣ እናስተምራለን የሚሉት በፈረንጅ አገር ውስጥ ሆነው ነው። እናም ውጤቱ እንደሚታየው ነው። እነሱ፣ ከአውሮፓና ከአሜሪካ መውጣቱን ስላልሞከሩት የነሱ ደጋፊና ሰራዊት ሁሉ ቀስ በቀስ ወደ እነሱ ይሄድ ዘንድ አብነት ሆነውት፤ አሁን አሁን ኦነግና ኢሕአፓ አውሮፓና አሜሪካ ውስጥ እያወራ፣ እየበላና እየጠጣ በምላሱ የሚዋጋ ጉጅለ ሆኖ ይታያሉ። የኢሳትና በውጭ (አውሮፓና አሜሪካ) ሆነው ስለ ነጻት የሚያወሩ ሰዎች መጨረሻም ከዚህ የዘለለ አይሆንም። አቶ አንዳርጋቸው፣ የተናገሩት ይህንን ነው ።
አንድ ኮሜዲያን ወይም ዘፋኝ ኢትዮጵያ ውስጥም ሆነ አውሮፓና አሜሪካ ቢኖር ልዩነት አያመጣ ይሆናል። በዘፈኑና በቀልዱን እታገላለሁ ካለ፣ ባለበት አገር አዘጋጅቶና አሳትሞ ለአድናቂዎቹ በማድረስ መቀስቀስ ወይም ማስተማር ይችል ይሆናል። ቀልደኛው ወይም ዘፋኙ፣ ዜግነቱን ሲቀይር ግን ነገሮች አንድ አይሆኑም። በተቃራኒው አንድን የህክምና ወይም የግብርና ባለሙያ ከወሰድነው፣ የትም ሄዶ መኖር መብቱ ቢሆንም ወገኔንና አገሬን እወዳለሁ፣ ለወገኔና ለአገሬ ስል እሰዋለሁ ለማለት ግን ቢያንስ ኢትዮጵያዊ መሆን ብቻ ሳይሆን ኢትዮጵያ ውስጥ ሆኖ ምቾቱንና ድሎቱን ችላ ብሎ በሙያው አገልግሎት መስጠቱ ወሳኝ ነው።
አቶ አንዳርጋቸው የታዩበት ቪዲዮ፣ በሰዓታት ብቻ ሳይሆን በቀናት ልዩነት ተቀርጾ ተቆራርጦና ተቀጣጥሎ የቀረበ መሆኑ የሚካድ አይደለም። የአቶ አንዳርጋቸው ልብስ መቀያየር ብቻ ሳይሆን የድምጻቸው ቃና እና ሃይልም ከፍተኛ ልዩነት ስለሚታይበት ይህን ማረጋገጥ ይቻላል። ነገር ግን አቶ አንዳርጋቸው፣ አእምሯቸውን ወይም ልቦናቸውን ስተዋል ማለት ግን እውነት አይመስለኝም።
ራሳቸውን እንደ ታጋይ፣ የትግል መሪና እንደ አገር ወዳድ አድርገው ሲያቀርቡ የከረሙ በውጭ የሚኖሩ ሰዎች፤ አቶ አንዳርጋቸውን ለመተቸት ሲወራጩ የታዩት ክብራችንን ነክቷል ለማለት ፈልገው መሆኑ ግልፅ ይመስለኛል።
‘የሚኒስትር ደሞዝ እያገኘሁ የምኖርበትን አሜሪካን ትቼ ወደ ኢትዮጵያ ልሄድልህ ነው?!’ የሚል ግለሰብ፣ ‘ዜግነታችንን የቀየርነው ከወረቀት ያለፈ ምንም ለውጥ ስለሌለው ነው’ እያለ ዜግነትን የሚያቃልል፣ “I’m Proud to be an American” እያለ የሚጎርር ኢትዮጵያዊነቱን የጣለ ስደተኛ፣ ማንችስተር አገሬ ናት ወደ ኢትዮጵያ የምመጣ የመሰላችሁ ሁሉ አይናችሁ ይፍሰስ እያለ የስደት ምቾቱን ለመስበክ የሚሞክር ግለሰብ ወዘተ የትግል መሪና ሕዝብን ፍርሃቱን እንዲሰብር አስተማሪ ነኝ እያለ መወዝወዙ በምናስተውልበት ጊዜ፤ የአቶ አንዳርጋቸው አነጋገር እንከን እንከን-አልባ እንደሆነ ይገባናል፡፡
ወያኔ አባርሮን (በፖለቲካ ልዩነት ወይም በድህነት ገረፈን የምንል ሁሉ)፣ መሰደዳችንን ጥሩ ወይም ተቢ ወይም እፎይታ አድርገን ማየታችን መብታችን ቢሆንም፤ አገሩ ውስጥ ያለውን ከ80 ሚሊዮን በላይ ሕዝብ ለማብጠልጠል ስንሞክር የመንቀዥቀዥ ፖለቲካ ውስጥ ያስገባናልና የአቶ አንዳርጋቸውን አነጋገር ወደልባችን አስገብተን ራሳችንን ማረም ይገባናል። ራስ ወዳድነታቸውንና እውነተኛ ማንነታቸውን በሚዲያዎች ላይ በሚፈጥሩት ሁካታ ለመሸፋፈን የሚሞክሩ ግለሰቦችን፣ የአቶ አንዳርጋቸው አነጋገር በደንብ አድርጎ ይገልፃዋቸዋል። አቶ አንዳርጋቸው፣ አሜሪካና አውሮፓ ውስጥ ሆነው ጎናቸውን እያደላደሉ ‘እኔም አንዳርጋቸው ነኝ’ የሚሉት አብዛኞቹ ሰዎች፤ ነገሩን ከአንገት በላይ እንጂ ከልባቸው አውጥተው እንደማይናገሩትና ሌላው ምሽግ ውስጥ ገብቶ እነሱ ዘፍነው ለውጥ እንዲመጣ የሚናፍቁ መሆናቸውን ነግረውናል፡፡ ታዲያ ይህ ሀቅ አይደለምን?
ሁላችንም፣ በውጭም ሆነ በአገር ቤት ሆነን፡- ‘እኔም አንዳርጋቸው ነኝ’ እያልን የምናወራው ሁሉ፣ ‹ጀግናው/ጀግኒት› እየተባባልን በየተራ የምንወዳደሰው ሁሉ ማን መሆናችን በግልጽ ተነግሮናል።

No comments:

Post a Comment