Translate

Wednesday, March 27, 2013

“ሀገሬ ገመናሽ” በፕ/ር መስፍን ወ/ማርያም (ክፍል ሁለት)


በየፍርድ ቤቶችሽ የፍትህ ውርጃ ሲፈፀም ዝም አልሽ።

በፕ/ር መስፍን ወ/ማርያም (ክፍል ሁለት)
በቀደም ሳት ብሎኝ፣
ለመጀመሪያ ልጄ ብቻ የፈረንጅ ሸራ ጫማ ገዝቼ ገባሁ። ያለወትሮዬ ማለቴ ለወትሮው ገበያ የምወጣው ሁለቱንም ልጆቼን ይዤ ስለነበረ ነው። ታዲያ ያን እለታ ማታ ትልቅዋ ልጄProfessor Mesfin Woldemariam is one of Ethiopia's well-known intellectuals ጫማውን ስትለካ፣ የታናሽ እህትዋ አይን ከሚለካው ጫማ ጋር ሲንከራተት ተመለከትኩ፤ ወይም የተመለከትኩ መሰለኝ። ‹‹ከወደድሽው ላንቺም ይገዛልሻል››አልኳት፤ የትንሽዋን ልጄን አይን እየሸሸሁ። በውስጤ አድሏዊነት ተላወሰ። በልጅትዋ ህሊና ውስጥ ይህ ስሜት እንደማያድር ባውቅም፣ የእኔን ሃሳብ ግን ቶሎ ላስወግደው አልቻልኩም። አየሽ ሀገሬ? እንኳን ህዝበ አዳምና ሔዋንን በእኩልነት ቤት ሆኜ አኖራለሁ የሚል ሀገር፣ አንድ ተራ ምስኪን ወላጅ እንኳን በጎጆው አድሏዊነት እንዳይሰፍን ይጥራል። አንቺ ግን ሀገሬ! … አንቺ ግን ዝሆንና ጥንቸል እያፋለምሽ ለአሸናፊው ታጨበጭቢያለሽ፤ ትሸልሚያለሽ።

መቼም ማንም ቢሆን፣ የአደባባይ ውበቱን እንጂ የጓዳ – ጎድጓዳ ገመናውን ሲነግሩት አይወድምና አንቺም ከአደባባይሽ ጀርባ መዝለቄ እንደማይጥምሽ አውቃለሁ። አደባባዮችሽማ ለዜጎችሽ የጋራ ፍትሀዊ መኖሪያነትሽን ይመሰክሩልሻል። መቼም የዜጋ ሁሉ እኩልነት የሚረጋገጠው በህግ ፊት ባለው እኩል መብት አይደል? ይህ ደግሞ ከገጠር ቀበሌሽ አንስቶ እስከ መዲናሽ ባሉ አደባባዮችሽ የሚታይ ነው። የወረዳ ፍርድ ቤት፣ የዞን ፍርድ ቤት፣ የክልል ፍርድ ቤት፣ የፌደራል ፍርድ ቤት፣ ከዚህ በተጨማሪ ደግሞ ጠቅላይ ፍርድ ቤት፣ ሰበር ሰሚ ችሎት… የፍትህ ቢሮ… ይህ ሁሉ አደባባይሽን ያደመቅሽበት የዜጎችን እኩልነት ማስጠበቂያ ተቋም ነው። ሀገሬ! ለመሆኑ በእነዚህ ተቋማት ምን እያደረግሽ እንዳለሽ ታውቂያለሽ?
አንዳንዴ ሳስበው ፍርድ ቤቶችሽና የፍትህ ተቋማቶችሽ ለዜጎች እኩል ያለመሆናቸውን የምታስታውቂበት ስፍራ ይመስለኛል። ይህን ስትሰሚ እንደምትቆጪ አውቃለሁ። ገመናው ሲሸፈንለት እንጂ ሲገለጥበት የሚወድ ማን አለ! አሁን እስቲ አንቺ ህግ አቁሜያለሁ፣ ዳኛ ሰይሜያለሁ ትያለሽ? ሀገሬ ሙች አፍሽን ሞልተሸ አትይም። ምነው ብትይ እማኝ ጠቅሼ እሞግትበት ሞልቶኛል።
አንድ አትዮጵያዊ ለትምህርት ውጭ ሄዶ ሳለ፣ በፈቀድሽው ከታክስ ነፃ መብቱ ተጠቀመና አውቶሞቢል ገዝቶ መጣ። አንቺንና ያቆምሽውን መንግስት እያሞገሰ አራት አመት በአውቶሞቢሉ ተጠቀመና ተመልሶ ለትምህርት ሄደ።
ባለቤቱ ደግሞ አሁንም አንቺንና መንግስቷን እያመሰገነች ስትነዳ፣ አንድ ቀን በጉምሩክ አሳሽ ጓዶች ተያዘች። መቼም ‹‹ለምን?›› ማለትሽ አይቀርም። የመኪናው ሊብሬ በባለቤትዋ ስም ስለነበር፣ አንቺ በአውቶሞቢሉ መገልገል አትችይም ተብላ፣ ተያዘች። መኪናው ታሰረ። አጣሪ ተቋቋመ። አጣሪው አጣርቶ ‹‹ባለመብቱ ባለቤትዋ በመሆኑ፣ በአውቶሞቢሉ መጠቀም መብትዋ ነው›› ብሎ ሪፖርት አቀረበ። ኮፒው ደግሞ ለሴትየዋ ደረሰ። ታዲያ ሀገሬ ጉዳዩ የቀረበለት የጉምሩክ ባለስልጣን፣ ቀረጡን ትከፍያለሽ አላት። ተያይዞ የቀረበውን ሪፖርት ተመልክቶት እንደሁ ጠየቀችው። አለመመልከቱን፣ ቢመለከተውም እንኳን ሪፖርቱ እግዚአብሔርም ቢመጣ ከመክፈል እንደማያስጥላት፤ ካልከፈለች መኪናዋ ጉምሩክ ውስጥ እንደሚታሸግበት ነገራት።  ሀገሬ፣ ሴትየዋና ባለስልጣኑ ሁለቱም ያንቺ ዜጎች፣ ሁለቱም ኢትዮጵያዊ ናቸው። ቆይ ህግሽ ላይ ‹‹አንድ ኢትዮጵያዊ›› የሚለው ሀረግ ማንን አስበሽ ያሰፈርሽው ነው? እና ሴትዮዋ ሃምሳ አራት ሺህ ብር ከፈለች። ከመክፈልዋ በፊት ግን ሀገሬ ሙች አልቅሳ ለምናዋለች። ከእግዚአብሔር በላይ ያስቀመጥሽውን ዜጋ መለመን እንጂ ምን መፍትሔ አለ! ባለቤትዋ ይህን ሲሰማ መጀመሪያ ያዘነው ባንቺ አይደለም። ባስቀመጥሽው ባለስልጣን ትእቢትና ድንቁርና ተደነቀ። ህግ ፊት አቅርቦ፣ ባለቤቱ በህግ የተሰጣትን መብት የሚጥስበት ከህግ የከበረ መብት እንደሌለው ሊያሳየው፣ ባለስልጣኑን ህግ ፊት ሊገትረው ከአውሮፓ ሲበር መጣ፤ ጠበቃ ቀጠረ።
በቀጠሮው ቀን እሱና ጠበቃው ማልደው ፍርድ ቤት ደረሱ። ተከሳሽ አልቀረበም። የመስሪያ ቤቱ ጠበቃ እንኳን አልቀረበም። ዳኛዋ ሌላ ቀጠሮ ሰጡ። በቀጠሮውም ቀን የቀረበ የለም። ዳኛዋ ባለስልጣኑ ፍርድ ቤቱን ማዋረዱን፣ ከአንዴም ሁለቴ በቀጠሮ አለመቅረቡን ከምንም ሳይቆጥሩ ፍርዱን ገመደሉት። ባለስልጣኑ ትክክል መሆኑን፣ ሴትየዋ መያዛቸው፣ ገንዘቡንም መክፈላቸው አግባብ መሆኑን ፈረዱ።
ሀገሬ፣ ያ ከአውሮፓ የፍትህ ጥማት ሲያበር ያመጣው ሰው፣ በፍትህ መዶሻሽ የተጨፈለቀ ዜግነቱን ይዞ ወደአውሮፓ ተመለሰ። አየሽ ሀገሬ! ለዚህ ነው የምሞግትሽ፤ እኛን ዜጎችሽን ከወባ፣ ከተስቦ ብትፈልጊም ከኤች.አይ.ቪ በላይ የጎዳን በየፍርድ ቤትሽ በህግ የበላይነት ለማያምን  ዳኛ ያስጨበጥሽው መዶሻ ነው።
እንዴ እውነቴን እኮ ነው! ሀገሬ ሙች እውነቴን ነው። ለወባው፣ ለተስቦውና ለኤች.አይ.ቪ.ው እድሜ ለቱጃሮቹ ጓደኞችሽ እንጂ፣ መች መድሀኒት ይገደናል- መርከብ ሞልተው ይልኩልናል። ደግሞ ብንሞትስ! እድር አለን እንቀበራለን። ቆይ እድር ባይኖረንስ! ደግሞ ለመቅበር! አበሻ እንኳን ሞተሽለት ገና በጣር ተይዘሽ፣ ላይ ላዩን መተንፈስ ስትጀምሪ ነው ጉድጓድ መቆፈር የሚጀምረው። ግን ሀገሬ እንዲህ በቁማችን በፍትህ መዶሻሽ ስንሰባበር፣ እነዚህ የወባና የተስቦ መድሀኒት በመርከብ ሞልተው የሚልኩልን ጓደኞችሽ አንቺንም ሆነ መንግስትሽን ሀይ አላሉልንም። እና ሀገሬ፣ ይህ የአንቺ ብቻ ሳይሆን የነሱም ገመና ነው።
ቆይ እኔ የምለው መንግስት ከህግ በላይ ነው እንዴ!? እስቲ ንገሪኝ ሀገሬ- መንግስት የሆኑት ከእኛው መሀከል፣ እንደኛው ዜጋ የነበሩት አይደሉም እንዴ! ዜጎችሽ አይደሉም እንዴ ‹‹መርጣችሁናል›› ብለው መንግስት የሆኑት! ታዲያ ለምንድነው የፍትህ መዶሻሽ እነሱ ላይ ቄጠማ የሚሆነው? ይኽው በአንቺ ውስጥ ከልጅነት እስከ እውቀት ስኖር መንግስት ከሳሽም ተከሳሽም ሆኖ ሲረታ እንጂ ሲፈረድበት አይቼም፣ ሰምቼም አላውቅም። ምን ያስቃል ሀገሬ! በእርግጥ ገንዘብን፣ ወይም ደግሞ ሌሎች ቀለል ያሉ ጉዳዮችን በተመለከተ አንድ ሁለት ፋይሎች በመንግስት ካሳ ከፋይነት እንዲዘጉ አድርገሽ ሊሆን ይችላል። ይህን ተይና እውነት ሀገር ከሆንሽ፣ እስቲ በሰብአዊና በዜግነት መብት ጉዳይ መንግስትን ከስሶ ያሸነፈ አንድ ዜጋ ጥሪ! እረ ጉደኛ ነሽ፣ ሀገሬ!
እኔ የምልሽ የህግ ትምህርት ቤት፣ ምናምን ምን ያደርግልሻል? ለምን አምስትና ስድስት ዓመት ህግ ታስተምሪያለሽ? ለእኛ ለዜጎችሽ ያቆምሽው፣ ህግ እንዳይዛነፍ፣ በየፍርድ ቤቱ ያስቀመጥሽው መዶሻ አናት አናታችንን እያለ ቅስማችንን እየሰበረ፣ ከዜግነት ተራ እንዳያስወጣን አይደለም እንዴ! በአንቺ በሀገሬ ህግ፣ እንኳን መርጠኽኛል፣ ያለ ባለስልጣንና መንግስት ቀርቶ፣ እየሱስ ክርስቶስም ቢሆን፣ ኢትዮጵያዊ ነኝ ብሎ አብሮኝ ቢኖር፣ በህግ ፊት እኩል ነን። አቦ ሀገሬ በፍትህ ስም የምትሰሪው ግፍ በዛ! የምር በዛ። ወይ በቃ የህግ ትምህርት ቤቶችሽን ዝጊና ዳኛ ለምታደርጊያቸው ዜጎች እንዴት የባለስልጣንንና የመንግስትን የስልክ ትእዛዝ ተቀብለው ተግባራዊ ማድረግ እንዳለባቸው አንድ ሁለት ሳምንት አሰልጥነሽ … በቃ!
አንዳንዴ ሳስበው ያ ታከለ የሚመኘውን ምኞት እኮ ሁላችንም ልንመኘው ነው! ሀገሬ መቼም ታከለን ታውቂዋለሽ። ለነገሩ አንዳንዶቹን አውቀሽ ችላ ትያቸዋለሽ እንጂ፣ አንቺ ዜጋሽ መቼ ይጠፋሻል። እሱም አንዱ ፍትህ መከበር አለበት፤ ያለ ህግ የበላይነት ሀገርና ህዝብ አይቆምም፣ ባይ ነው። ታዲያ የውልሽ፣ ከአመት ተመንፈቅ በፊት የቢ.ፒ.አር አሰራሩን ተቃውመሀል ተብሎ ከስራ ታገደ። ሁለት ወር ያለ ስራ ደመወዝ በላ። በሶስተኛው ወር ደመወዙ ቆመ። ሀላፊውን ሊያነጋግር ሄዶ የስራ መልቀቂያ ደብዳቤውን ተቀብሎ መጣ። ታዲያ ያን ሰሞን እቤቴ መጣና፣ ‹‹ገንዘብ አበድረኝ›› ሲለኝ፣ ያው እንደወትሮው ወር መዳረሻ ገዶት ይሆናል፣ ብዬ ‹‹ስንት መቶ?›› ስለው ‹‹ሰባት ሺህ›› አይለኝ መሰለሽ!? መስሪያ ቤቱን ሊከስ እንደሆነም ነገረኝ። ገንዘቡን ለጠበቃና ለአንዳንድ ተጨማሪ ወጪ ፈልጎ ነው። ባንክ በቆጠብኩት ሁለት ሺህ ብር ላይ ከባለቤቴ ቤተሰቦች አምስት ሺህ ብር ተበድሬ ጨምሬ ስሰጠው ‹‹ተው! ይቅርብህ! የመስሪያ ቤቱን ባለስልጣን የሾመው መንግስት ነው። መንግስት ደግሞ ከሶም ተከሶም ይረታል። ሰማይ አይታረስ ንጉስ አይከሰስን አስብ። ቃሉ ቢለወጥም ያው መንግስት ማለት ንጉስ ነው። ቀበሌ፣ ወረዳ፣ ዞን፣ ክልል፣ መስሪያ ቤቶችና መንግስት ያላቸው ልዩነት የተዋረድ ብቻ ነው›› አልኩት። ሀገሬ ሙች አልሰማኝም። እንዲያውም አልሰማ ቢለኝ በየመስሪያ ቤቶቻቸው የተሰየሙ ትንንሽ መንግስታትን ከሰው አቅላቸውን የሳቱ፣ ‹‹ቂጣቸውን በሳንጃ የተወጉ›› ዜጎችን በየዘመኑ ማየቴን፣ ገመናሽን ገልጬ ነገርኩት። አልሰማ ብሎ ፋይሉን በወረዳ ፍርድቤት ከፈተ።
በወረዳ ፍ/ቤትሽ የክስ ፋይል በከፈተ በአራት ወሩ የውሳኔውን ወረቀት አምጥቶ አሳየኝ ሀገሬ ሙች እልሻለሁ ገረመኝ! አንቺ እኮ ትገርሚያለሽ! የፍርድ ቤቱ የፍርድ ውሳኔ ከማህተሙና ከፊርማው ልዩነት በስተቀር፣ ያው የተባረረበት ደብዳቤ ግልባጭ ነው። አዘነ። ሀገሬ ሙች አዘነ። የፍትህ መዶሻሸ ያረፈበትን አናቱን ቀና አድርጎ መመልከት አቃተው።
ታከለ ግን የዋዛ ዜጋ አይደለም። ‹‹እውነትና ንጋት እያደር ይጠራል››ን እየተረተ ይግባኝ አለ። ይኽው ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ሰው ሰርቶ በየወሩ ደመወዝ ሲቀበል፣ እሱ በየደረጃው በሚገኙ ፍርድ ቤቶች፣ የተባረረበትን ደብዳቤ እያፀደቀ ይመጣል።
እና ታከለ ምን ተመኘ መሰለሽ! ሀገሬ ሙች እንደገመናሽ ዝግናኔ የግል ፍርድ ቤት ቢመኝ አይፈረድበትም። አንድ እሁድ ቀን አንድ ካፌ በረንዳ ላይ ተቀምጠን ማኪያቶ ስንጠጣ፣ ከመንገዱ ባሻገር ያለውን የግል ሆስፒታል እየተመለከተ‹‹በህይወት ዘመኔ ማየት የምመኘው ምን እንደሆነ ታውቃለህ?›› አለኝ። ‹‹ምን››አልኩት፤ ቁብ አልሰጠሁትም። ‹‹እዚያ ህንፃ አናት ላይ በግል ሆስፒታሉ ስያሜ ምትክ ‹‹ብርሃን ከፍተኛ የግል ፍርድ ቤት፣ መለያችን ይግባኝ አልባ ፍርዳችን ነው!›› የሚል ተጽፎ ማየት። ሀገሬ ሙች አያስቅም! ደግሞ ሰው እንጂ ሀገር ሲስቅም ሲያለቅስም አያምርበትም።
እውነቱን እኮ ነው! በመንግስት ፍርድ ቤት መንግስትን መርታት ካልተቻለ፣ ለምን በግል ፍርድ ቤት አይሞከርም። በቃ ሀገሬ አንቺም የፍትህ ገመናሽን መክላት ካማረሽ፣ በቃ የግል ፍርድ ቤት ክፈቺ። እና የመንግስት ፍ/ቤቶች በዜጎችሽ መካከል ያለን ክስ ይመልከቱ። በማንኛውም ሁኔታ በመንግስትና በዜጋ መካከል ያለን ክስ ደግሞ በግል ፍርድ ቤት እንዲታይ አድርጊ። ያኔ የዜጎችሽ አናት መንግስት ለዳኞችሽ ባስጨበጣቸው መዶሻ አይነደልም። ዜጎችሽ ቀና ብለው ይሄዳሉ፤ ስለፍትህ ስርአትሽም መልካሙን አብዝተው ይናገራሉ። ከሁሉም በላይ ደግሞ አንቺ ደስ ይልሻል። አንቺ ደስ ሲልሽ ደግሞ እኛም መልሶ ደስ ይለናል።
ስለፍትህ ገመናሽ ስናገር የሰሙ አንዳንድ ዜጎችሽ፣ ‹‹እንዴት ሰው፣ ከሰው ገመና አልፎ የሀገርን ገመና አንድ — ሁለት — እያለ ያብጠለጥላል!›› እያሉ ያብጠለጥሉኛል። እኔ ምን ተዳዬ! ሀገሬ አንቺ ራስሽ ገመናሽን መች ሸፈንሽውና እኔ እኮነናለሁ? እንዴ! የምር እኮ ነው የምልሽ! ገመናሽን እንደጋለሞታ ደጃፍ ገልጠሽዋል እኮ! አንቺ ራስሽ አይደለሽ እንዴ ተቃዋሚ፣ አሸባሪ፣ አክራሪ ብለሽ ዜጎችሽን ባሰርሽ ማግስት አኬልዳማ፣ ጀሀዳዊ ሐረካት– ምናምን የሚል ፊልም እየሰራሽ የፍትህ – ገመናሽን ቲቪ ያስገባሽው! እውነት ሀገሬ ያሳፍራል።
ለዚህ እኮ ነው መንግስት የገባበት ክስ የዝሆንና የጥንቸል ፍልሚያ ነው የምልሽ። ያውም ሮጣ የማታመልጥ እግርዋ የተሰበረ ጥንቸል! ሲጀመር ለመንግስት ዝሆንነትን ሰጥተሻል። ጠመንጃ አለው፤ እስር ቤት አለው፤ ቲቪ አለው፤ ራዲዮ አለው፤ ዳኛ አለው፤ አቃቤ ህግ አለው። ይህ ሁሉ ካለኝ ደግሞ እኔም ብሆን፣ ዝሆን መሆን አያቅተኝም። ተቃዋሚ፣ ሽብርተኛ፣ አክራሪ ተብሎ የተመረጠው ደግሞ ጥንቸል ነው። ጥንቸል ከዝሆን ቢፋለም እድሉ አንድ ነው- ሮጦ ማምለጥ። አንቺ ግን ሀገሬ! ጥንቸሎችሽ በፍትህ ስርአትሽ ሮጠው ነፃ የሚወጡበት የመርፌ ቀዳዳ የምታህል ቀዳዳ እንኳን እንዳትኖር፤ ክሳቸው እንኳን ወጉ ተነቦላቸው የእምነት – ክህደት ቃላቸው ሳይሰማ፣ እንዴት እንዳከረሩ፣ እንዴት እንዳሸበሩ ፊልም ሰርተሽ በቲቪ ትለቂዋለሽ። በፍትህ አደባባይ ሮጠው እንዳያመልጡ የጥንቸሎቹን እግር ስብርብር አደርገሽ ማለት ያኔ ነው! .. ኧረ በእውነት ይዘገንናል! አባቶቻቸው ተጠርጥረው ከተከሰሱበት ወንጀል ነፃ የሚወጡበትን ቀን የሚናፍቁ ልጆችን … እናቶቻቸውን.. ጎረቤቶቻቸውን… አስቢ እስቲ! አንቺ በእነሱ ቦታ ብትሆኚና ፍትህን ያስከብርልኛል ያልሽው መንግስት በተጠረጠሩብሽ ላይ፣ እንደዚያ ያለ ፊልም እያቀረበ የፍትህን ጽንስ ለውርጃ ሲዳርግ ብትመለከቺ ምን ትያለሽ! ምንስ ታደርጊያለሽ! ዳሩ አንቺ ሀገር እንጂ ዜጋ አይደለሽም። ዜጋስ ብትሆኚ እግሮችዋ የተሰበሩ ጥንቸል ሆነሽ መታገል ከማይሰለቸው ዝሆን ፊት ብትቆሚ እጣሽ ምንድነው? አቦ ሀገሬ ተይኝ! ገልጠው የማይጨርሱት ገመና አድሎሻል!
(ይቀጥላል)

1 comment:

  1. በ MESFINWOLDEMARIAM.WORDPRESS.COM ላይ በግልጽ እንደተቀመጠው ይህ ጽሑፍ የ ፕሮፌሰር መስፍን ሥራ ሳይሆን ዶክተር በድሉ ዋቅጅራ በ ልዕልና ጋዜጣ ያቀረቡት ነው። MESFINWOLDEMARIAM.WORDPRESS.COM ም ያሰተናገደችው በልዩ ዓምድ መሆኑን እናመለክታለን።

    ReplyDelete